Friday, March 24, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ማኅበራዊየተቀየረው የትምህርት ፖሊሲ መምህራን የሚቀጠሩበትን መሥፈርትንና ሌሎችንም አሻሻለ

የተቀየረው የትምህርት ፖሊሲ መምህራን የሚቀጠሩበትን መሥፈርትንና ሌሎችንም አሻሻለ

ቀን:

  • ትምህርትና የልጠና ርከኖች ላይ ዋና ዋና ለውጦች አድርጓል
  • ተማሪዎች ቢያንስ ስት ቋንቋዎች እንዲማሩ ይደረጋል
  • ትምህርት እስከ 8ኛ ክፍል በነና በግዴታ ይሆናል

ለ28 ዓመታት ሲተገበር የቆየውን የትምህርትና ሥልጠና ፖሊሲን የሚተካና አዲስ የመምህራንን የሙያ ደረጃን፣ የተማሪዎችን የክፍል ዕርከኖችን፣ በሥርዓተ ትምህርት የሚካተቱ ቋቋዎችን፣ እንዲሁም በርካታ የትምህርት ሂደቶችንና አሰራሮችን የሚቀይር ፖሊሲ በሚኒስትሮች ምክር ቤት ፀደቀ።

በትምህርት ሚኒስቴርና በሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ሃሳብ አመንጭነት ተዘጋጅቶ፣ ለሚኒስትሮች ምክር ቤት የቀረበው አዲሱ የትምህርት ፖሊሲ፣ በትምህርት ሥርዓቱ ላይ ዋና ዋና ማሻሻያዎችን በማድረግ፣ ባለፈው ሰኞ የካቲት 20 ቀን 2015 ዓ.ም. ምክር ቤቱ ባካሄደው 17ኛ መደበኛ ስብሰባ ማስተካከያ ተደርጎበት ሥራ ላይ እንዲውል ተወስኗል፡፡

ሪፖርተር የተመለከተው ለሚኒስትሮች ምክር ቤት ቀርቦ የነበረው ረቂቅ ፖሊሲ እንደሚያሳየው፣ ከተደረጉት ማሻሽያዎች መካከል የመምህራን የትምህርት ዝግጁነትና ደረጃዎች አንደኛው ሲሆን፣ ከአንደኛ ደረጃ ቀደም ላሉና ዕድሜያቸው አምስትና ስድስት ዓመት የሆኑትን የቅድመ-አንደኛ የትምህርት ደረጃ ተማሪዎች ለማስተማር አነስተኛው የትምህርት ደረጃ ‹‹ሰርተፊኬት›› እንዲሆን ያዛል።

ከአንደኛ እስከ ስድስተኛ ክፍል ያሉትን ተማሪዎች ለማስተማር ደግሞ አነስተኛው የትምህርት ዝግጁነት ‹‹ዲፕሎማ›› እንደሚሆን በፖሊሲው ተቀምጧል። በማስቀጠልም ከሰባተኛ ክፍል እስከ 12ኛ ክፍሎች ድረስ ለማስተማር፣ አነስተኛው መምህራን ሊኖራቸው የሚገባው የትምህርት ዝግጁነት የመጀመርያ ዲግሪ እዲሆን በረቂቅ ፖሊሲው ተቀምጧል።

የትምህርት አመራሮችን በሚመለከት እስከ ስምንተኛ ክፍል ላሉ አመራሮች አነስተኛው የትምህርት ዝግጁነት የመጀመርያ ዲግሪ ሲሆን፣ ለሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ደግሞ አመራሮቹ አነስተኛው ሁለተኛ ዲግሪ የትምህርት ዝግጁነት እንዲኖራቸው ተደንግጓል። በተመሳሳይም የቴክኒክና ሙያ ሥልጠና ተቋማት አመራሮች ከቴክኒክ ክህሎት ባሻገር ቢያንስ ሁለተኛ ዲግሪ እንዲኖራቸው ረቂቅ ፖሊሲው ያዛል።

የመምህራንን የትምህርት ዝግጁነት በሚመለከት ቀደም ብለው ረቂቅ ፖሊሲው ላይ በማኅበራቸው በኩል ሐሳብ ሰጥተውበት እንደነበረ የሚናገሩት የኢትዮጵያ መምህራን ማኅበር ፕሬዚዳንት ዮሐንስ በንቲ (ዶ/ር) እንደሚናገሩት፣ ከዚህ በፊት የትምህርት ፍኖተ ካርታው ሲዘጋጅ ተካሂዶ ከነበረው ጥናት ጋር ተመሳሳይ እንደሆነ ገልጸዋል።

የተቀመጡት የትምህርት ዝግጅቶች አስፈላጊ እንደሆኑ፣ እንዲያውም የመጀመርያ ዲግሪ የትምህርት ዝግጁነት መሥፈርት ከሰባተኛ ክፍል ከሚጀምር ለሙሉ አንደኛ ደረጃ መምህራን ቢሆን የሚል ዕይታ እንዳላቸው ፕሬዚዳንቱ ተናግረዋል። ‹‹አንደኛ ደረጃ ብቻም ሳይሆን ከዚያ በላይም ካለ ዲግሪ የሚያስተምሩ አሉ፤›› ያሉት ዮሐንስ (ዶ/ር)፣ በኢትዮጵያ ውስጥ ባለፉት ዓመታት ተግባራዊ ሲደረግ በነበረው የትምህርት ፖሊሲ ሙሉ ለሙሉ ደረጃውን አሟልቶ የሚያስተምር መምህር እንደሌለ ተናግረዋል።

የፖሊሲውን ተግባራዊነት በሚመለከት እንደ መሥፈርት ይውጣ እንጂ ተግባራዊነቱ በተወሰኑ ዓመታት ውስጥ በሒደት ሊታይ እንደሚችል ዮሐንስ (ዶ/ር) ያስረዳሉ። ‹‹የተሟላ ደረጃ ያለው እስኪገኝ ድረስ ዝቅተኛ ደረጃ ያላቸው እያስተማሩ መቀጠላቸው ላይቀር ይችላል። አሁን ባለው የመምህራን እጥረት አይደለም ያለውን ማስወጣት ተጨማሪ መቀጠር አለበት፣ ስለዚህ በአንድ በኩል ወይ ደረጃቸውን እንዲያሻሽሉ አልያም ባላቸው የትምህርት ደረጃ መቀጠል ይኖርባቸዋል፤›› ሲሉ ተናግረዋል።

ሌላው ረቂቅ ፖሊሲው የለወጠው ቋንቋን በሚመለከት ሲሆን፣ ተማሪዎች በትንሹ ሦስት ቋንቋዎችን እንዲማሩ ይደነግጋል። ተማሪዎች የአፍ መፍቻ ቋንቋን እንደ ማስተማሪያና እንደ የትምህርት ዓይነት ከታች ጀምሮ ሲማሩ ቆይተው፣ የሚኖሩባቸው ክልሎች በሚወስኑት መሠረት ቋንቋዎቹ መሰጠት የሚኖርባቸው የክፍል ደረጃ ይታወቃል። እንግሊዘኛ ግን ከአንደኛ ክፍል ጀምሮ እንደ ትምህርት ዓይነት ይሰጥና እንደ ማስተማርያ ቋንቋ ደግሞ በአስገዳጅነት ከዘጠነኛ ክፍል ጀምሮ ይሰጣል።

ተማሪዎችና ወላጆቻቸው መርጠው ከፌዴራል የሥራ ቋንቋዎች ውስጥ አንድ ተጨማሪ የአገር ውስጥ ቋንቋ ከሦስተኛ ክፍል እስከ አስረኛ ክፍል እንዲማሩ የሚደረግ ሲሆን፣ አንድ ሌላ ተጨማሪ የውጭ አገር ቋንቋ ደግሞ ከዘጠነኛ ክፍል ጀምሮ እንደ አማራጭ ትምህርት ይሰጣል፡፡  

በተጨማሪም ረቂቅ ፖሊሲው ላይ እንደተደነገገው የትምህርት ዕርከኖች ቅድመ አንደኛ ደረጃ፣ አንደኛ ደረጃ፣ መካከለኛ ደረጃና ሁለተኛ ደረጃ በማለት በአራት ይከፋፈላሉ። በቅድመ አንደኛ ደረጃ የሚማሩት የአምስትና የስድስት ዓመታት ዕድሜ ያላቸው ልጆች ሲሆኑ፣ የሰባት ዓመት ልጆች መማር የሚጀምሩት የአንደኛ ደረጃ ደግሞ ከአንደኛ እስከ ስድስተኛ ክፍልን ያጠቃልላል።

መካከለኛ ደረጃ ሰባተኛና ስምንተኛ ክፍልን የሚያካትት ሲሆን፣ ሁለተኛ ደረጃ ደግሞ ከዘጠነኛ እስከ 12ኛ ክፍል ድረስ ያሉትን ነው። የከፍተኛ ትምህርትን በሚመለከት በአሁን ጊዜ እንዳለው አሠራር ቅድመ ምረቃ በትንሹ አራት ዓመታትን እንደሚፈጅ፣ ሁለተኛ ዲግሪ ደግሞ ሁለት ዓመታትን እንደሚፈጅና የሦስተኛ ዶክትሬት ዲግሪ ደግሞ አራት ዓመታትን እንደሚፈጅ ፖሊሲው ይጠቅሳል።

ቴክኒክና ሙያ ሥልጠናዎች ስምንት ደረጃዎች እንደሚኖራቸውም፣ አሠልጣኞቻቸውም የሙያ ብቃት ወይም የኢንዱስትሪው ልምድን ጨምሮ ከመጀመርያ ዲግሪ ጀምሮ እስከ ሦስተኛ ዲግሪ ድረስ የትምህርት ዝግጁነት እንዲኖራቸው ተደንግጓል። ለደረጃ አንድና ሁለት በአነስተኛ የመጀመርያ ዲግሪ፣ ከደረጃ ሦስት እስከ ስድስት የሁለተኛ ዲግሪ፣ እንዲሁም ለደረጃ ሰባትና ስምንት ደግሞ ሦስተኛ ዲግሪ እንደመስፈርት ተቀምጧል።

የቅድመ አንደኛ ደረጃ ትምህርት፣ የአንደኛ ደረጃ ትምህርትና የመካከለኛ ደረጃ ትምህርቶች (ማለትም ከአንደኛ ክፍል በታች ያለውን ጨምሮ እስከ ስምንተኛ ክፍል ያለ ትምህርት) በግዴታና በነፃ እንደሚሰጥ ረቂቅ ፖሊሲው አስቀምጧል። ከዘጠነኛ ክፍል የሚጀምረው የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ግን በነፃ ሊሰጥ እንደሚችል ብቻ ነው የሚያስቀምጠው።

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

[ክቡር ሚኒስትሩ ከሚያከብሯቸው አንድ የቀድሞ ጉምቱ ፖለቲከኛ ስልክ ተደውሎላቸው እያወሩ ነው]

አንዳንድ ነገሮች ቢያሳስቡኝ ነው ቀጠሮ ሳልይዝ ላወራህ የፈለኩት ክቡር...

የትግራይ ክልል የሽግግር አስተዳደር ምሥረታና የሰላም ስምምነቱ ሒደት

በትግራይ ክልል ጊዜያዊ የሽግግር መንግሥት ለመመሥረት ደፋ ቀና እየተባለ...

ጥራዝ ነጠቅነት!

ከሜክሲኮ ወደ ጀሞ እየሄድን ነው፡፡ የተሳፈርንበት አሮጌ ሚኒባስ ታክሲ...