ላለፉት ሁለት አሥርት ዓመታት በከፍተኛ ዕድገት ውስጥ ሲጓዝ የነበረው የኢትዮጵያ ኢኮኖሚና በዚያው ልክ እያደገ የመጣውን የሕዝብ ብዛት የግብርና ዘርፉ መሸከም እንዳልቻለ ከበቂ በላይ ምልክቶች ፍንትው ብለው መታየት ከጀመሩ ሰነባብተዋል።
በሁሉም ዓይነት ሸቀጦች ላይ የሚታየው ከፍተኛ የዋጋ ንረት፣ በምግብ እህል አቅርቦትና ፍላጎት መካከል የሚታየው አለመጣጣምና ይህንን የአቅርቦት ጉድለት በውጭ ምንዛሪ ከውጭ በማስገባት ለመቅረፍ የመረጠው የአጭር ጊዜ መፍትሔና ከፍተኛ የሥራ አጥነት ችግር ጎልተው የወጡ የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ህመም ምልክቶች ናቸው።
የሚታዩትን የኢኮኖሚው ህመም ምልክቶች ለማከም ብቻ ሳይሆን በግብርና ላይ የተመሠረተውን የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ መዋቅር በሒደት ለመቀየር የተለያዩ የፖሊሲ መፍትሔዎች ተቀርፀው መተግበር ከጀመሩም ዓመታት ተቆጥረዋል።
ከፖሊሳ መፍትሔዎቹ በግንባር ቀደምነት የሚጠቀሰውም የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ ከግብር ጥገኝነት አላቆ ወደ ኢንዱስትሪ የሚያሻገር መዋቅራዊ ለውጥ መፍጠር አንዱ ነው። ይህንን መዋቅራዊ ሽግግር ለማምጣት የቅድሚያ ትኩረት ከተሰጣቸው መካከል ደግሞ የማኑፋክቸሪንግ ዘርፉ ተጠቃሽ ነው። ይሁን እንጂ ለማኑፋክቸሪንግ ዘርፉ ይሰጣል የተባለው ትኩረት በልኩ ባለመሆኑ ውጤቱን ማየት ያልተቻለ ከመሆኑም በላይ ዘርፉ ላለፉት በርካታ ዓመታት በዘርፈ ብዙ ችግሮ ውስጥ እየተንገዳገደ ይታያል።
በኢትዮጵያ በማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ የተሰማሩ አካላት ከተፈተኑባቸው በርካታ ማነቆዎች መካከል የፋይናንስ ድጋፍ አናሳ መሆን በቀዳሚነት ይጠቀሳል፡፡
በተለይም በአገር አቀፍ ደረጃ የሚመደበው በጀትና የብድር አገልግሎት አናሳ መሆን ብዙዎች ዘርፉን እንዲተው እያስገደዳቸው እንደሆነ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡
የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር በማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ እያጋጠመው ያሉ የፋይናንስ ችግሮችን ለመፍታት የካቲት 15 ቀን 2015 ዓ.ም. ከተለያዩ የፋይናንስ ተቋማት ጋር ውይይት አድርጓል፡፡ በዕለቱም የማኑፋክቸሪንግ ዘርፉ ያጋጠመውን የፋይናንስ እጥረት በተመለከተ ጥናት ቀርቧል፡፡ ጥናቱን ያቀረቡት ወ/ሮ ያኔት ሽፈራው ሲሆኑ፣ የማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ ለአገር ውስጥ ምርት ከ20 ዓመታት በፊት 20 ቢሊዮን ብር ያነሰ አስተዋጽኦ እንደነበረው ገልጸዋል፡፡
የ2014 ዓ.ም. ደግም 145 ቢሊዮን ብር ለአገር ውስጥ ምርት አስተዋጽኦ ማድረጉን በዘርፉ ከሁለት አሥር ዓመታት በፊት የነበረው አራት በመቶ ዕድገት ወደ 6.7 በመቶ ማደግ መቻሉን በጥናቱ ተገልጿል፡፡
ለውጭ ንግድና ለኤክስፖርት ማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ ያለው አስተዋጽኦ ከፍተኛ መሆኑን፣ ከ2013 እስከ 2014 ድረስ የ100 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ማስገኘቱም ተገልጿል፡፡ ይህም በዋናነት በጨርቃ ጨርቃ፣ ምግብና መጠጥ፣ እንዲሁም ከሌሎች ንዑስ ዘርፎች የተገኘ ገቢ ነው፡፡ በቅርቡ መንግሥት ትኩረት ካደረገባቸው ጉዳዮች መካከል አንዱ ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በአገር ውስጥ ምርት መተካት ሲሆን፣ በዚህም በ2014 ዓ.ም. ሁለት ቢሊዮን ዶላር ማዳን መቻሉ ተጠቁሟል፡፡
የ2015 በጀት ዓመት የስድስት ወራት የዕቅድ አፈጻጸም ሲታይ ደግሞ የማኑፋክቸሪንግ ዘርፉ ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በአገር ውስጥ ምርት በመተካት አንድ ቢሊዮን ዶላር የውጭ ምንዛሪ ማዳኑን ጥናቱ ያመለክታል፡፡ በማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ አሁን ካለባት 50 በመቶ የማምረት አቅም እ.ኤ.አ. በ2030 ወደ 85 በመቶ የማምረት ዕቅድ ቢኖርም፣ በብዙ ችግሮች የተተበተበ በመሆኑ የታሰበው ዕቅድ ላይሳካ ይችላል የሚል ሥጋት ፈጥሯል፡፡
ለአምራች ኢንዱስትሪ የሚቀርበው የፋይናንስ አቅርቦት በተመለከተ የልማት ባንክን ጨምሮ አምስት የግል ባንኮች አስተዋጽኦ በጥናቱ ተመላክተዋል፡፡ በዚህም ባንኮቹ ለሌሎች ዘርፎች የሚያቀርቡት ብድር ከማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ ጋር ሲነፃፀር ዝቅተኛ መሆኑ በጥናቱ ተለይቷል፡፡ አጠቃላይ በፋይናንስ ተቋማት ከሚያቀርቡት አጠቃላይ ብድር ውስጥ ለአምራች ዘርፍ የሚቀርበው 15 በመቶ ብቻ መሆኑንም ጥናቱ አመልክቷል፡፡
ከአምራች ዘርፍ ከሚሰጠው ፋይናንስ ይልቅ፣ ለአገልግሎትና ለሌሎች ዘርፎች የሚቀርበው እንደሚልቅ ተነግሯል፡፡ የግል ባንኮች በአጠቃላይ ከሚያቀርቡት ብድር ውሽጥ አምራች ዘርፉ የሚያገኘው 14 በመቶ ሲሆን፣ የመንግሥት የፖሊሲ ባንክ የሆነው የኢትዮጵያ ልማት ባንክ ግን ከአጠቃላይ ብድሩ እስከ 90 በመቶ የሚሆነውን ለማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ እንደሚያቀርቡ በጥናቱ ተመላክቷል። ይህም የንግድ ባንኮች በአጭር ጊዜ ብድርና ለሥጋት በማያጋልጧቸው ሌሎች ዘርፎች ብቻ ብድር እንደሚቀርቡ በጥናቱ ተጠቁሟል፡፡ የልማት ባንክ ከሌሎች በተሻለ ሁኔታ ለዘርፉ ገንዘብ እንደሚያቀርብ ባለፉት አምስት ዓመታት ብቻ እስከ 90 በመቶ የሚደርስ ፋይናንስ አቅርቧል፡፡
ለአነስተኛና መካከለኛ የሊዝ ፋይናንስ አቅርቦት ደግሞ ከዓመት ዓመት እየተሻሻለ መሆኑን፣ በዚህም በ2014 ዓ.ም. 1.6 ቢሊዮን ብር ለማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ ማቅረቡ ተጠቁሟል።
የብድርና የውጭ ምንዛሪ አቅርቦት ማነቆ
በ2015 የበጀት ዓመት ለማኑፋክቸሪንግ ዘርፉ በግብዓትነት የሚውል ጥሬ ዕቃ ለማስገባት 881 ሚሊዮን ዶላር የተጠየቀ ቢሆንም፣ ከዚህ ውስጥ የተገኘው ግን 128 ሚሊዮን ዶላር ብቻ መሆኑን ጥናቱ ያመለክታል፡፡ ይህም ቢሆን ለተመረጡ ክትትልና ድጋፍ ለሚሰጣቸው አምራች ዘርፎች የቀረበ ነው። ከብድር ጋር ተያይዞ ያለው የፋይናንስ አቅርቦትን በተመለከተ በበጀት ዓመቱ አጋማሽ ከተጠየቀው 14 ቢሊዮን ብር ውስጥ የተፈቀደው 3.5 ቢሊዮን ብር ብቻ መሆኑ ጥናቱ ያሳያል፡፡ ይህም ቢሆን በዋናነት በአነስተኛና መካከለኛ የሊዝ ፋይናንስ አገልግሎት የቀረበ መሆኑ ተገልጿል፡፡ በዚህም ምክንያት የማኑፋክቸሪንግ ንዑስ ዘርፍ ከሚፈልገው የፋይናንስ ፍላጎት አኳያ አቅርቦቱ እጅግ አናሳ እንደሆነ የጥናቱ ድምዳሜ ያመለክታል።
የኢንዱስትሪዎች የማምረት አቅም በየስድስት ወሩ የሚመዘን ሲሆን፣ የጨርቃ ጨርቅ 61.7 በመቶ፣ የኬሚካልና ኬሚካል ግብዓቶች 59 በመቶ፣ የቆዳ ውጤት 57 በመቶ፣ ምግብና መጠጥ 57 በመቶ ሲሆን፣ በአጠቃላይ የኢንዱስትሪ ዘርፉ በአማካይ 57.8 በመቶ የማምረት አቅም እየሠራ መሆኑ የቀረበው ጥናት ይጠቁማል፡፡
በ2014 በጀት ከተቀመጠው ግብ አኳያ ዘርፉ የተሻለ ቢሆንም፣ ከእቅድ አፈጻጸም አኳያ ወደ ኋላ መቅረቱ ተገልጿል፡፡ በዚህ ምዘና መሠረት ዝቅ ያለበት ምክንያት ሲፈተሽ ከተስተዋሉ ችግሮች አንዱና ዋነኛው የፋይናንስ አቅርቦት መሆኑን ጥናቱ ያሳያል፡፡
ጥናቱ የፋይናንሰ አቅርቦት ችግሮችን በሦስት ከፍሎ ተመልክቷቸዋል፡፡ ከነዚህም የመጀመሪያው ከአገልግሎት አኳያ ያለ ክፍተት ሲሆን፣ በፋይናንስ ተቋማት የብድርና የውጭ ምንዛሪ አቅርቦት የአሠራር ሒደት ግልጽ አለመሆኑ በጉድለትነት የሚነሳ ነው።
አብዛኞቹ አምራች ኢንዱስትሪዎች የብድርና የውጭ ምንዛሪ እንዴት ማግኘት እንዳለባቸው መረጃ እንደሌላቸው ተገልጿል፡፡ ብድር ለማግኘትም ቢሆን እስከ 200 በመቶ የሚደርስ ዋስትና እንዲያቀርቡ የሚጠየቁ መሆኑ፣ በዚህም ምክንያት አነስተኛና መካከለኛ ኢንዱስትሪዎች የወሰዱትን ብድር ለመመለስ አስቸጋሪ እንደሆነባቸው ተመላክቷል፡፡ ከባንኮች ብድር ለመውሰድ የሚጠይቁት መስፈርቶች በርካታ መሆናቸው ሌላኛው የፋይናንስ ዘርፍ ፈተና እንደሆነ ተጠቁሟል፡፡
ዘርፉን ያላገናዘበ የተመጣጠነ የወለድ ምጣኔ አለመኖር በፋይናንስ ተቋማት ከታዩ ችግሮች አንዱ ሲሆን፣ የማኑፋክቸሪንግ ዘርፉ እስከ 18 በመቶ የሚደርስ ወለድ እንደሚጠየቅ ተገልጿል፡፡ በተጨማሪም የብድር ዘመንና የመመለሻ ጊዜው አነስተኛ እንደሆነ፣ በዚህም ምንክንያት አምራቾች ወደ ትርፍ ሳይገቡ ብድር ወደ መመለስ ግዴታ እንዲገቡና በዚህም ለኪሳራ መጋለጣቸው ተጠቅሷል፡፡ የውጭ ምንዛሪ ለማግኘት አስቸጋሪ በመሆኑም አምራቾች በሚገጥማቸው የግብዓት አቅርቦት ውስንነት የኤክስፖርት አፈጻጸማቸው ዝቅ እንዲል ምክንያት ሆኗል ተብሏል፡፡
አገር ውስጥ ያለው አምራች ኢንዱስትሪ በፋይናንስ እጥረት ሳቢያ የማምረት አቅሙን ያህል ማምረት እንዳልቻለ ተገልጿል፡፡ በቀረበው ጥናት ላይ ተንተርሶ የፋይናንስ ተቋማት በዕለቱ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡ የኢትዮጵያ ልማት ባንክ በፕሬዚዳንት ዮሐንስ አያሌው (ዶ/ር)፣ ጥናቱን ተመሥርተው ምላሽ ከሰጡት መካከል ይገኙበታል፡፡ ጥናቱ ዘርፉ ምን ያህል ፋይናንስ እጥረት እንዳጋጠመው ያመለክታል ያሉት ዮሐንስ (ዶ/ር)፣ በዚህ ጉዳይ ሁሉም የፋይናንስ ሴክተር ትኩረት ማድረግ እንዳለበት ተናግረዋል፡፡ በልማት ባንክ በኩል ለማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ በቂ ፋይናንስ መቅረቡን ገልጸው፣ ፍላጎት ያለውን አሁንም እንደሚያስተናግዱ ጠቁመዋል፡፡ ነገር ግን በስፋት እየቀረበ ያለው የሥራ ማስኬጃ ብድር ጥያቄ መሆኑን የጠቀሱት ዮሐንስ (ዶ/ር)፣ ልማት ባንክ የሥራ ማስኬጃ ብድር ሊያቀርብ እንደማይችል ለማኑፋክሪንግ ልማት የሚውል የካፒታል ብድር ለሚፈልጉትን ግን እንደሚያስተናግድ ገልጸዋል።
የውጭ ምንዛሪ አቅርቦት የልማት ባንክም ችግር መሆኑን ፕሬዚዳንቱ ገልጸው፣ ባንኩ የውጭ ምንዛሪ የሚሰጠው በአምራቹ የብድር አመለላስ (Performance) ላይ ተመስርቶ መሆኑን አስረድተዋል፡፡
የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ምክትል ፕሬዚዳንትና ሆልሴል ባንኪንግ ኃላፊ አቶ ሙሉነህ ለማ፣ ባንኩ ከፍተኛ የፋይናንስ ከሚያቀርብባቸው ዘርፎች ውስጥ የማኑፋክቸሪንግ ይገኝበታል ብለዋል፡፡
በጥናቱ እንደ ችግር የተቀመጠው ለዘርፉ የቀረበው ፋይናንስ ሦስት ቢሊዮን እንደሆነ መገለጹን የተናገሩት አቶ ሙሉነህ፣ ባንኩ ለዚህ ዘርፍ ያቀረበው ወደ 6.2 ቢሊዮን ብር መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በፋይናንስ አቅርቦት ችግሮች መኖራቸውን እንደሚገነዘቡ ምክትል ፕሬዚዳንቱ ገልጸው፣ ንግድ ባንክ ብዙ ብድር የፈቀደ ቢሆንም የሁሉንም የብድር ፍላጎቱን መመለስ እንዳልቻለ ገልጸዋል።
የውጭ ምንዛሪ እጥረት አገራዊ በመሆኑ ለማኑፋክቸሪንግ ዘርፉም ሆነ ለሌሎች ዘርፎች በበቂ ሁኔታ ማቅረብ እንዳልተቻለ ገልጸዋል።
ባንኮች በፀጥታ መደፍረስን የኮሮና ቫይረስ መከሰት ምክንያት የተበላሹ ብድሮቻቸው መጠን እንደጨመረ ገልጸዋል። ከፍተኛ የተበላሸ ብድር ከተከማቸባቸው ዘርፎች አንዱና ዋነኛው የማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በተጨማሪም በማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ የሚሠሩ ፕሮጀክቶች መዘግየት ወይም በጊዜው አለመጠናቀቅ ሌላኛው የዘርፉ ፈተና መሆኑን የጠቆሙት አቶ ሙሉኑህ፣ በዚህም ባንኮች ጭምር ተጎጂዎች እንደሆኑ አስረድተዋል፡፡
ለዚህ ሁሉ ችግሮች ምክንያት የሚሆነው ውጫዊ ፈተናዎች ብቻ ሳይሆኑ፣ አስተዳደራዊ (ውስጣዊ) ችግሮችም እንደሆኑ ተናግረዋል፡፡ የብድር ዋስትናን አስመልክቶ ጥናቱ ባነሳቸው ክፍተቶች ላይ በሰጡት አስተያየት የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ደኅንነቱ ያልተጠበቀ ብድር ጭምር እንደሚያቀርብ በመግለጽ ባንኩ ዘርፉን ለመደገፍ ትኩረት እንደሚያደርግ ተናግረዋል፡፡
አብዛኛው የብድር ጥያቄዎች ሲፈተሹ የሥራ ማስኬጃና ለሰባት ዓመት የሚከፈል መሆኑን፣ ይህም ባንኩ ካለው አሠራር ጋር የማይጣጣም ነው ብለዋል፡፡ እንደ አቶ ሙሉነህ ገለጻ፣ ደንበኞች የሥራ ማስኬጃ ሲጠይቁ በአንድና ሁለት ዓመት ጊዜ ውስጥ የሚመለስ ብድር ቢጠይቁ ብድር ለመስጠት አስቸጋሪ አይሆንም፡፡
የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ደኤታ አቶ ታረቀኝ ቡሉልታ በበኩላቸው፣ ለአምራች ዘርፍ የፋይናንስ አቅርቦት ምን እንደሚመስል ሲታይ፣ በቂ አቅርቦት አለመኖሩ አከራካሪ እንዳልሆነ ገልጸዋል።
የተሻለና ተወዳዳሪ ምርት ለማቅረብ የፋይናንስ እጥረት ማነቆ እንደሆነ፣ እንደ አገር ተወዳዳሪ ዘርፍ ሆኖ በቂ የፋይናንስ አቅርቦት አለማግኘቱ ተገቢ እንዳልሆነና በዚህ አካሄድ የፋይናንስ ተቋማትም ትርፋማ መሆን እንደማይችሉ አቶ ታረቀኝ አስረድተዋል፡፡
በአሁን ጊዜ ባንኮች ትርፋማ መሆናቸውን፣ ነገር ግን ያሉትን ዘርፈ ብዙ ችግሮች ለመቋቋም ትኩረት መሰጠት ያለባቸው ለአምራች ኢንዱስትሪ ነው ሲሉ ሚኒስትር ደኤታው አሳስበዋል፡፡ ለዘርፉ ፋይናንስ ለማቅረብ የሚደረደሩ ምክንያቶች ተቀባይነት እንደሌላቸውም ጠቁመዋል፡፡ የባንኮች የፋይናንስ አቅርቦት ሥርዓት ግልጽነት እንደሚጎድለውና በቢሮክራሲ የታጀበ መሆኑን አቶ ሙሉነህ አስረድተዋል፡፡
እንደ አቶ ታረቀኝ ገለጻ፣ የፋይናንስ ተቋማት ማኑፋክቸሪንግ የተጠየቀውን ብድር ከስድስት ወር እስከ አንድ ዓመት ምላሽ ለመስጠት ይዘገያሉ፡፡ አንዳንድ ባንኮች ብድር ሳይሰጡ ወለድ የሚቀበሉ መኖራቸውን ጠቅሰው፣ በዚህም ምክንያት በዘርፉ የተሰማሩ ባለሀብቶች የተፈቀደላቸው ብድር እጃቸው ላይ ሳይደርስ የሚከስሩ መኖራቸውን አብራርተዋል፡፡
ባንኮች በአጠቃላይ ፋይናንስ አቅርቦት ላይ ያላቸውን የውስጥ አሠራር መፈተሽ እንዳለባቸው ጠቁመዋል፡፡ ‹‹አምራች ኢንዱስትሪ ተወዳዳሪ እንዳይሆኑ የሚያደርጉ ችግሮችን እንዴት እንቀንሳለን? የሚለውን ሐሳብ የፋይናንስ ተቋማትና የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር በጋራ የምንመልሰው ነው፤›› ሲሉ አቶ ታረቀኝ ተናግረዋል፡፡
የኢንዱስትሪ ሚኒስትር አቶ መላኩ አለበል በበኩላቸው፣ ‹‹በዚህ ጥናት ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር በዝርዝር የፋይናንስ ተቋማትን እንዳየ፣ ተጨማሪ ጥናት ቢደረግም ይህንኑ የሚደግም ነው፤›› ብለዋል። በመሆኑም መስተካከል ያለባቸው ችግሮች ላይ ትኩረት ማድረግ ይገባል ያሉት አቶ መላኩ፣ ጥናቱን የሚያስቀይር የፋይናንስ አቅርቦት የለም ብለዋል፡፡
የዳሸን ባንክ ፕሬዚዳንት አቶ አስፋው ዓለሙ በበኩላቸው፣ ዳሸን ባንክ ከፍተኛ መዋለነዋይኑን ያፈሰሰው ለአምራች ኢንዱስትሪ መሆኑን፣ ከአጠቃላይ የብድር አቅርቦቱ 21 በመቶ የሚፈቀደው ለማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ ነው ብለዋል።
ማኑፋክቸሪንግ ሴክተር ትልቅ አስተዋጽኦ ያለው በመሆኑ፣ ዳሸን ባንክ ይህን ዘርፍ ለመደገፍ ፍላጎት እንዳለው ገልጸዋል፡፡ ከዳሽን ባንክ የረዥም ጊዜ ብድር ካገኙት ዘርፎች መካከል የማኑፋክቸሪንግ ዘርፉ 43 በመቶው ድርሻ እንዳለው ተናግረዋል፡፡ ባንኮች አጭር ጊዜ ብድር እንጂ ሥጋት ያለው የብድር አይደፈርም የተባለው ነገር ትክክል አይደለም ብለዋል፡፡
ለዚህም እንደ ማሳያ ያነሱት 24.4 በመቶ ለአጭር ጊዜ ብድር ባንኩ መስጠቱን የረዥም ጊዜ ብድር የተሰጠው ደግሞ 31 በመቶውን እንደሚሸፍን ፕሬዚዳንቱ አስረድተዋል፡፡
የንግድ ባንኮች ሀብት የአጭር ጊዜ ተቀማጭ ገንዘብ በመሆኑ የረዥም ጊዜ ብድር ለመስጠት እንደሚቸገሩ ግንዛቤ መወሰድ አለበት ብለዋል። በተለይ የባንክ ኢንዱስትሪውን ከተቀላቀሉ አጭር ዓመታትን ብቻ ያስቆጠሩ ባንኮች የረዥም ጊዜ ብድር ለመስጠት እንደሚቸገሩ ጠቁመው፣ ይህም ችግር ውስጥ ሊከታቸው እንደሚችል አስረድተዋል፡፡
|
|