በኢትዮጵያ ባለፉት ሁለት ዓመታት ሕጉ ከሚፈቅደው አሠራር ባፈነገጠ ሁኔታ 63 ጋዜጠኖች እንደታሰሩ፣ የመብቶችና ዴሞክራሲ ዕድገት ማዕከል በጥናት ማረጋገጡን አስታወቀ፡፡ 63 ጋዜጠኞች ከሕግ ሥርዓት ሒደት ውጭ ታፍነው ከመታሰራቸው ባሻገር ሁለት ጋዜጠኞች መገደላቸው በጥናቱ ተመላክቷል፡፡
ጋዜጠኞች ከሕግ አግባብ ውጭ ታፍነው መታሰራቸው፣ ከታሰሩ በኋላም ያሉበት ሳይታወቅ ቆይተው መለቀቃቸው አሳሳቢ ጉዳይ በመሆኑ፣ መንግሥት በጉዳዩ ላይ ትኩረት እንዲያደርግና ችግር ሲደርስባቸው ለመሟገት ያመች ዘንድ ጋዜጠኞች ማኅበራትን እንዲቀላቀሉ ተጠይቋል፡፡
ከዚህም ባሻገር በኦሮሚያ ክልል በተለይም ወለጋ ካለፉት አራት ዓመታት ጀምሮ የሚፈጸመውን የንጹሐን ዜጎች ሞት ጋዜጠኞች በአካል ተገኝተው አለመዘገባቸው በጋዜጠኞች ማኅበር ቅሬታ አስነስቷል፡፡ በወለጋ ንጹሐን ዜጎች ላይ የሚፈጸመውን ሞት ለመዘገብ ጋዜጠኞች ግፊት አለማድረጋቸው ከተጠያቂነትና ወቀሳ የማያድን መሆኑን የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኅን ማኅበር ፕሬዚዳንት ጋዜጠኛ ጥበቡ በለጠ ተናግሯል፡፡
ጋዜጠኞች በወለጋ ያለውን የንጹሐን ሰዎች ሞትና መፈናቀል በአካል ተገኝው እንዲዘግቡ ማኅበሩ ለምን ሁኔታዎችን እንዳላመቻቸ ከሪፖርተር ለቀረበላቸው ጥያቄ፣ በሚገኘው አጋጣሚ ሁሉ ለሚመለከታቸው አካላት ከመናገር ለጋዜጠኞችም ከማሳሰብ እንዳልተቆጠቡ ገልጸዋል፡፡
‹‹ድኅረ -2010 ዓ.ም. የኢትዮጵያ መገናኘ ብዙኃን ሁኔታ፣ የኢትዮጵያ የመገናኛ ብዙኅን የግጭት አገናዛቢ አርትኦት ፖሊሲዎችና አተገባበራቸው መነሻ ጥናት፣ እንዲሁም የግጭት አገናዛቢ አዘጋገብ ዳሰሳ በኢትዮጵያ፤›› በሚል ርዕሰ ጉዳይ ማዕከሉ የካቲት 15 ቀን 2015 ያቀረበው ጥናት ፋና ብሮድ ካስቲንግ ኮርፖሬሽን የግጭት ዘገባዎችን አገናዝቦ በመጻፍ ከሁሉም ሚዲያዎች የተሻለ እንደሆነ፣ ከፋና ቀጥሎም አሻም ቴሌቪዥን የግጭት ዘገባን በተመለከተ ኤዲቶሪያል ፖሊሲው የተሻለ መሆኑን እንዲሁም የኢቢሲ ሚዲያ ደግሞ የማያስፈልጉ ጥቃቅን ነገሮች ላይ እንደሚያተኩር በጥናት መረጋገጡ ተመላክቷል፡፡
ግጭት አገናዛቢ ዘገባን ግምት ውስጥ በማስገባት፣ ግጭት እንዳይባባስ ከማድረግ አኳያ የሚዲያ ተቋማት ከእውነታው እየሸሹ መሆናቸውን ያነሱት ጋዜጠኛ ጥበቡ፣ ሳይዘግቡ ከመቅረት ይልቅ ሁሉንም ወገን በማካተት እውነታውን መዘገብ ለውጥ እንደሚያመጣ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡
በመርሐ ግብሩ የተገኙ የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች፣ ፖሊስ ጋዜጠኞችን በመውሰድ ከሕግ አግባብ ውጭ የሚፈጽመውን ድርጊት መንግሥት እንዲያስቆም ጠይቀዋል፡፡ ጋዜጠኞች የጋዜጠኝነት ማኅበርን የማይቀላቀሉት ማኅበሩ ጥቅማጥቅም የለውም በሚል ምክንያት መሆኑ የተነሳ ሲሆን፣ ይህ እሳቤ መቀረፍ እንዳለበትም ተነግሯል፡፡
በሌላ በኩል በኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ የሚሳተፉ ሴት ጋዜጠኞች ብዛት አነስተኛ መሆኑ በጥናት መረጋገጡን ሙላቱ (ፒኤችዲ) በመርሐ ግብሩ ተናግረዋል፡፡
የሴት ጋዜጠኞች በአርትኦት ውሳኔ አሰጣጥና በኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ውስጥ ያላቸው የመሪነት ሚና ከወንድ አቻወቻቸው ጋር ሲነጻጸር ዝቅተኛ መሆኑም በጥናቱ ተቀምጧል፡፡ ጥናቱ እንደሚያሳየው፣ በቴሌቪንና በሬዲዮ የሥራ ዘርፍ ከተሰማሩ 2,400 ጋዜጠኞች መካከል ከፍተኛ ቁጥር የሚይዙት ወንዶች 1,516 ሲሆኑ፣ የሴቶች ቁጥር ደግሞ ዝቅተኛ 526 መሆኑ ተነግሯል፡፡
ከ22 በላይ የጋዜጠኝነት ማኅበራት ቢኖሩም፣ በኢትዮጵያ 65 በመቶ የሚሆኑት ጋዜጠኞች የተለያዩ የጋዜጠኝነት ማኅበርን እንዳልተቀላቀሉ የማዕከሉ ጥናት ተረጋግጧል ተብሏል፡፡ ጥናቱ ይፋ የተደረገው የካቲት 15 ቀን 2015 ዓ.ም. በማዶ ሆቴል ነው፡፡