- ለዕርዳታ የተላከ ዱቄት በኩንታል አሥር ሺሕ ብር እየተሸጠ ነው
በአፋር ክልል በአብአላ ዙሪያ በትግራይና አፋር አዋሳኝ ድንበሮ ‹‹በሽፍቶች›› ጥቃት ምክንያት ተፈናቃዮች ወደ ቀዬአቸው መመለስ እንዳልቻሉ ተናገሩ፡፡ ከ550 በላይ አባዎራዎች ያለ ዕርዳታ በመጠለያ ውስጥ መሆናቸውን ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
በሰሜን ኢትዮጵያ በነበሩት የመጀመርያና ሁለተኛ ዙር ጦርነቶች፣ የሕወሓት ታጣቂዎች ዋነኛ መተላለፊያ በነበረችው የሙርጋ ቀበሌና ሌሎች የአባላ አካባቢዎች የተፈናቀሉት እነዚህ ዜጎች እስካሁን በአካባቢው ‹‹ሽፍቶች›› ስላሉ ወደ ቀዬአቸው መመለስ እንዳልቻሉ ገልጸዋል፡፡
‹‹ቤቶች በሙሉ በጦርነቱ ጊዜ በታጣቂዎች ተቃጥለዋል፡፡ ወደዚያም እንዳንመለስ በአፋርና ትግራይ አዋሳኝ አካባቢዎች እስከ አምስት ኪሎ ሜትር ድረስ ሽፍቶች ስላሉ ሕዝባችን በፍርኃት ነው በመጠለያ ያለው፤›› ሲሉ አቶ አሊ ዳማ የተፈናቃዮች አስተባባሪና የግብርና ሠራተኛ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ ተፈናቃዮቹ በጦርነቱ ጊዜ እስከ ኤርታሌ ድረስ ተሰዶ የነበረ ሲሆን፣ ጦርነቱ ለጥቂት ወራት ሲቆም ለመመለስ ቢሞክሩም እስካሁን ከአባላ ከተማ በቅርብ በሚገኙ መጠለያ ቦታዎች ተሰብስበው እንዳሉ ገልጸዋል፡፡ ይህም ወደ ቀደመው ቀዬአቸው ለመመለስ አሁንም የፀጥታ ሥጋት በመኖሩ ነው ብለዋል፡፡ ተፈናቃዮች እስካሁንም የሰብዓዊ ዕርዳታ ማግኘት እንዳልቻሉና በከፍተኛ ችግር ውስጥ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡
‹‹መንግሥት ምንም እያደረገልን አይደለም፡፡ ሌሎች አካባቢዎች የዕርዳታ ድርጅቶችና መንግሥት ዕርዳታ እያቀረቡ ነው፡፡ ግን ዕርዳታ የሚደርሰው የክልልና የዞን እስከ ወረዳ ያሉት አስተዳዳሪዎች ለራሳቸው ጎሳና ቤተሰብ ብቻ ነው የሚያቀርቡት፡፡ ለእኛ ዕርዳታ አንድ ጊዜ ብቻ ነው የደረሰው፡፡ ሕዝቡ ፍየልና ግመል ሸጦ ጨርሶ የሚቀምሰው አጥቷል፡፡ ውኃ ለማግኘት ከሦስት ሰዓታት በላይ እንሄዳለን፡፡ ለሌሎች ግን በሶላር ውኃ ማቅረብ ከጀመሩ ቆይቷል፤›› ብለዋል አቶ አሊ፡፡
በሌላ በኩል ለዕርዳታ የሚላኩ መሠረታዊ የአፋጣኝ ዕርዳታ ምግቦችና ብርድ ልብሶች በገበያ ውስጥ በኮንትሮባንድ እየተሸጡ መሆንን ሪፖርተር አረጋግጧል፡፡ ለአብነትም የዕርዳታ ዱቄት በኩንታል አሥር ሺሕ ብር የሚሸጥ ሲሆን፣ ለሕፃናት የተላከ አልሚ ምግብም በኮንትሮባንድ ገበያ ይሸጣል፡፡ በተለይ በወረዳና ዞን ደረጃ ያሉ አስተዳዳሪዎች በስፋት ተሳታፊ መሆናቸው ተነስቷል፡፡ ይሁን እንጂ አስተዳዳሪዎች ለሪፖርተር ተደጋጋሚ ጥረት ምላሽ ከመስጠት ተቆጥበዋል፡፡
አቶ ሲራጅ ሙሳ የአፋር ክልል የሰብዓዊ ዕርዳታዎች አስተባባሪ እንደሚሉት ግን በክልሉ ዕርዳታ ያልደረሰው አንድም ተፈናቃይ የለም፡፡ ‹‹በመንግሥት፣ በዓለም ምግብ ፕሮግራምና ሌሎች የዕርዳታ ሰጪ ድርጀቶች የወጣ ሁሉም ዕርዳታ ከማከማቻ ወጥቶ እየተሰጠ ነው፡፡ እስካሁን ለአምስተኛ ዙር አስተላልፈናል፡፡ በኮታው መሠረት ያልደረሰው የለም፡፡ ችግርም ካለ የሚኖረው በዞን ወይም በወረዳ ደረጃ ሊሆን ይችላል፤›› ብለዋል አቶ ሲራጅ፡፡