በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የተፈጠረውን ችግር ምክንያት በማድረግና ኢመደበኛ የሆነ አደረጃጀት በመፍጠር፣ ሕገ መንግሥቱንና ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን በኃይል ለመናድ የሽብር ተግባር ለመፈጸም ተንቀሳቅሰዋል በሚል ተጠርጥረው የታሰሩት እነ መምህር ምሕረት አብ አሰፋና እነ ፌቨን ታሪኩ ፍርድ ቤት ቀርበው ጊዜ ቀጠሮ ተጠየቀባቸው፡፡
በመምህር ምሕረትአብ መዝገብ 12 ተጠርጣሪዎች የተካተቱ ሲሆን፣ በቁጥጥር ሥር ውለው የታሰሩት የካቲት 4 ቀን 2015 ዓ.ም. ነው፡፡ በእነ ወ/ሪት ፌቨን መዝገብ ደግሞ ሰባት ተጠርጣሪዎች የቀረቡ ሲሆን፣ የታሰሩት የካቲት 3 ቀን 2015 ዓ.ም. ነው፡፡
ተጠርጣዎቹ ከትናንት በስቲያ የካቲት 6 ቀን 2015 ዓ.ም. በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ አንደኛ ጊዜ ቀጠሮ ችሎት ቀርበዋል፡፡
ፖሊስ ተጠርጣሪዎቹን ለምን እንዳሰራቸው ለፍርድ ቤቱ እንዳስረዳው፣ ግለሰቦቹ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የተፈጠረውን ጉዳይ እንደ ክፍተት በመጠቀም፣ ከሃይማኖት አስተምህሮት ውጭ የራሳቸውን አጀንዳ በተለያዩ ሕገወጥ በሆኑ ማኅበራዊ ሚዲያዎች በማስተላለፍና ከውጭ ኃይሎች ጋር በመሆን ሕገ መንግሥቱን በኃይል ለማፍረስና የሽብር ተግባር ለመፈጸም የሚያስችል እንቅስቃሴ ሲያደርጉ በቁጥጥር ሥር ማዋሉን አስረድቷል፡፡ በተጠርጣሪዎቹ ላይ የሰነድና የሰው ምስክሮችን ለማሰባሰብም 14 ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ እንዲፈቀድለት ጠይቋል፡፡
ተጠርጣሪዎቹን ወክለው ፍርድ ቤት የቀረቡ 12 የሕግ ባለሙያዎች (ጠበቆች)ም ፖሊስ ላቀረበው ክስ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያኗ ‹‹ከአስተምህሮቴ ውጭ ተንቀሳቅሰዋል›› ብላ ሳታመለክት (ሳትከስ) ፖሊስ በምን ሁኔታ ጥያቄውን ሊያነሳ እንደቻለ፣ ሕገወጥ ማኅበራዊ ሚዲያ ያላቸውን ፌስቡክ፣ ቲክቶክና ሌሎችም ማኅበራዊ ሚዲያዎች ሕገወጥ መሆናቸውን እንዲያስረዳ ጥያቄ አቅርበዋል፡፡
ፍርድ ቤቱም የግራ ቀኙን ክርክር ከሰማ በኋላ ከሁለቱም መዝገብ ለሰባት ተጠርጣሪዎች ዋስትና ፈቅዶ፣ መምህር ምሕረት አብና ወ/ሪት ፌቨንን ጨምሮ አምስት ተጠርጣሪዎች ላይ ፖሊስ የጀመረውን ምርመራ እስከሚያጠናቅቅ ከጠየቀው 14 ቀናት ውስጥ ስምንት ቀናት በመፍቀድ ለየካቲት 14 ቀን 2015 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡