- የባንዲራና የዋና መቀመጫን ጉዳይ የሚያጠና የፕሮጀክት ቢሮና ኮሚቴ ተቋቁሟል
ባለፈው ሳምንት ጥር 29 ቀን 2015 ዓ.ም. የሕዝብ ውሳኔ ያካሄዱ 11 ዞኖችና ወረዳዎች በተደረገው ሕዝበ ውሳኔ ካሸነፉ ይመሠርቱታል ተብሎ የሚጠበቀው ‹‹የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል›› ከሁለት በላይ ዋና ከተሞች እንደሚኖሩት ተገለጸ፡፡
በቀጣይ ጥቂት ቀናት በብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ውጤቱ በሚታወቀው የሕዝበ ውሳኔ ምርጫ፣ ክልሉ የሚመሠረት ከሆነ በቀጣይ ከሌሎች አገሮች ተሞክሮ በሚወሰድ ልምድ ሁለትና ከሁለት በላይ ዋና ከተሞች እንደሚኖሩት የጋሞ ዞን አስተዳደሪ አቶ ብርሃኑ ጌጡ ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡
በዚህም የመንግሥት አካላት የሚባሉትን ሕግ አውጪ፣ የሕግ ተርጓሚና የሕግ አስፈጻሚዎች መቀመጫ ታሳቢ ያደረገ የከተሞች አወቃቀር እንደሚዘጋጅ የገለጹት አስተዳዳሪው፣ አሁን ላይ ኮሚቴ እየተከናወነ ካለው የሕግ ማሻሻያ ጋር የሚገናኙ ሌሎች ጉዳዮችን አስመልክተው የሚወጡ ሰነዶች ላይ አስፈላጊው ምክከር ተደርጎ ውሳኔ ይሰጥበታል ብለዋል፡፡
ከባንዲራ፣ ከዋና መቀመጫ፣ ከክልሉ አርማና ሌሎች ክልል ለመመሥረት የሚያስፈልጉ መሰል ጉዳዮች ጋር የሚገናኙ አሠራሮች ላይ የሚሠራው ኮሚቴ ተቋቁሞ፣ ለቀጣይ ውይይት የሚቀርቡ ሥራዎች እያከናወነ መሆኑ ተብራቷል፡፡
በቀጣይ በኮሚቴው ጥናት መሠረት በሚመጣው ሐሳብ ላይ ውይይት ተደርጎ የትና እንዴት ይደረጋል በሚለው ጉዳይ 11ዱም ዞኖችና ወረዳዎች ተሳትፈውበት እንደሚወሰን አቶ ብርሃኑ ተናግረዋል፡፡
በቀድሞው የደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልላዊ መንግሥት ሥር ተካተው የነበሩት አምስት ክልሎች የተወሰኑ ፖለቲከኞችና የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች በነበራቸው መግባባት አንድ ክልል በማድረግ መቀመጫውን ወደ ሐዋሳ ሲወስዱት ከጅምሩ ተቃውሞ እንደነበር አስተዳዳሪው አብራርተዋል፡፡
በመሆኑም ጨፍልቆ ወደ አንድ ክልል እንዲመጣ የተደረገው አደረጃጀት ምንም እንኳ ኅብረ ብሔራዊነቱና ሕዝብ ለሕዝብ ጋር ያለው መቀራረብ ትልቅ ፋይዳ ቢኖረውም ከፍትሐዊነት የተነሳ በተደጋጋሚ ቅሬታ ሲነሳ የነበረበት ሁሉንም ሕዝብ እኩል የሚያይ አይደለም የሚሉ ተደጋጋሚ የሆኑ አቤቱታዎች ሲደመጡ እንደነበር አቶ ብርሃኑ አስረድተዋል፡፡
በተጨማሪም በኢኮኖሚና በፖለቲካው ዘርፍ የመንግሥት የልማት ፕሮጀክቶች ሲመደቡ ፍትሐዊ ባልሆነና ቅሬታ በሚፈጥር መልኩ ሕዝብን እኩል በማያይ አሠራር እንዲሁም በፖለቲከኞች ፍላጎት እንጂ ሁሉም ሕዝብ በእኩል የመልማት ዕድል እንዲያገኝ የሚሠራ ክልል አለመሆኑ አብራርተዋል፡፡
አቶ ብርሃኑ እንደሚሉት የቀድሞው ደቡብ ክልል በፖለቲካው ዘርፍም ቢሆን ለሁሉም አካባቢዎች የነበረው ተሳትፎ እኩል አለመሆኑንና ‹‹አንዳንዱን ያገነነ ሌላውን ያገለለ›› የፖለቲካ ተሳትፎ ያለበት ክልል ነው፤ የሚል ለረዥም ጊዜ ቅሬታ ይሰማና ጥያቄም በስፋት ከሕዝቡ ይነሳ እንደነበር አውስተዋል፡፡
የአደረጃጀት መዋቅር ሲባዛ የሚኖረው የአስተዳደር ወጭ በከፍተኛ ደረጃ እንደሚጨምርና ጫናውም ከባድ ሊሆን እንደሚችል ቢታወቅም ነገር ግን ሕዝቡ ይበጀኛል የሚለውን አማራጭ ወስዶ ወደዚህ ሕዝበ ውሳኔ የገባ በመሆኑ፣ በቀጣይ መሠረታዊ ችግር ተብለው የቀረቡት የኢኮኖሚና የልማት ኢፍትሐዊነት ለማስተካከል ሕጎችን በማሻሸል ለሁሉም የሚሠራና የሚጨነቅ ክልል መፍጠር እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል፡፡
በአጠቃላይ ግን ወደ አንድ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልልነት ለመጠቃለል የጠየቁት እነዚህ አካባቢዎች ከዚህ ቀደም በጠቅላይ ግዛትና በክፍለ አገር ሥር አብረው እንደነበር ገልጸዋል፡፡ በመሆኑም አሁንም በመልክዓ ምድርና በሥነ ልቦና ከዚያም አልፎ በመልካም ፈቃድ የመጣ ውሳኔ በመሆኑ እብሮ በመልማት በሒደት አዳጊ ፍላጎቶች ሲመጡ ችግሮችን በመመካካር መፍታት ያስፈልጋል ብለዋል፡፡
ሕዝቡ አመራሩ ካገዘው አብሮ ለመኖር ዕድሉ ሰፊ መሆኑን አቶ ብርሃኑ ተናግረዋል፡፡