Thursday, March 23, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ስፖርትበፀጥታ ችግር በአዳማ መካሄድ ያልቻለው የሊጉ ውድድር በድሬዳዋ እንደሚቀጥል ተገለጸ

በፀጥታ ችግር በአዳማ መካሄድ ያልቻለው የሊጉ ውድድር በድሬዳዋ እንደሚቀጥል ተገለጸ

ቀን:

  • ባህር ዳር ከተማ ውድድሩን ማከናወን እንደማይችል አሳውቋል

የቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ2015 ዓ.ም የ12ኛ ሳምንት ሁለት ተስተካካይ ጨዋታ፣ እንዲሁም ከ14ኛ ሳምንት በኋላ ያሉትን ውድድሮች ለማስተናገድ ዝግጅቱን አጠናቆ የነበረው የአዳማ ሳይንስ ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ፣ በፀጥታ ምክንያት ማከናወን ባለመቻሉ መርሐ ግብሩ በድሬዳዋ ከተማ እንዲቀጥል መወሰኑን የኢትዮጵያ ፕሪሚየም ሊግ አክሲዮን ማኅበር አስታውቋል፡፡

አክሲዮን ማኅበሩ ከ14ኛ እስከ 19ኛ ሳምንታት፣ እንዲሁም ሁለት ተስተካካይ ቤትኪንግ ፕሪሚየር ሊግ ጨዋታዎችን በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ለማካሄድ ከአዘጋጅ ከተማው ፀጥታ ክፍል ጋር ከሦስት ወራት በፊት ተነጋግሮ መስማማቱ አስታውሷል፡፡

ሆኖም የውድድር መርሐ ግብር ከወጣ በኋላ ተሳታፊ ክለቦች፣ አወዳዳሪው ክፍልና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ወደ ቦታው ቀደም ብለው ቢገቡም፣ በፀጥታ ችግር ምክንያት ውድድሩን ማስተናገድ እንደማይቻል መገለጹ ተብራርቷል፡፡

አክሲዮን ማኅብሩ በመግለጫው የመክፈቻ ፕሮግራም ዝግጅት በማሰናዳት፣ የተለያዩ ስፖንሰሮችን አነጋግሮ፣ እንዲሁም የክብር እንግዶችና ደጋፊዎችም ወደ ከተማው አቅንተው እንደነበር አውስቷል፡፡

በአንፃሩ ቅዳሜ ጥር 27 ቀን 2015 ዓ.ም. የከተማው አመራሮች ከበላይ አካል በተሰጣቸው አቅጣጫ መሠረት፣ ውድድሩን በመርሐ ግብሩ ለማካሄድ የሚቸገሩ መሆኑን ለአክሲዮን ማኅበሩ መግለጻቸውን በመግለጫው ጠቅሰዋል፡፡

የሊጉን የ2015 ዓ.ም. ውድድርን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ ጨዋታ የሚጠናቀቅበትን ጊዜ ታሳቢ በማድረግ በጊዜ ለማጠናቀቅ ፈጣን አማራጭ ለመውሰድ አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ ፊቱን ወደ ሌሎች ከተሞች ማዞሩን አክሲዮን ማኅበሩ አንስቷል፡፡

 በዚህ መሠረትም የሊጉ አክሲዮን የቦርድ አመራር ጥር 28 ቀን ባደረገው አስቸኳይ ስብሰባ፣ በቀጣይ ውድድሩ ላይ ሁለት ስታዲየሞችን (የባህር ዳር ዓለም አቀፍ ስታዲየምና የድሬዳዋ ዓለም አቀፍ ስታዲየም) በአማራጭነት ለውሳኔ ማስቀመጡን ጠቅሷል፡፡

በውሳኔ መሠረት በአዳማ መካሄድ የነበረባቸው የፕሪሚየር ሊጉ የዘንድሮ ተስተካካይ ጨዋታዎች እንዲሁም ከ14ኛ ሳምንት በኋላ ያሉ ጨዋታዎችን አስተናጋጅ ከተማና ስታዲየም በተመለከተ ሦስት፣ ሦስት አባላት የያዙ፣ ሁለት ኮሚቴዎች (ከሥራ አስፈጻሚውና ውድድርና ሥነ ሥርዓት ኮሚቴ የተውጣጣ) በማዋቀር ሰኞ ጥር 29 ቀን ሜዳዎቹንና የከተሞቹን ሁኔታ ከሚመለከታቸው የሥራ ኃላፊዎች ጋር በመሆን የጋራ ግምገማ ማድረጉን በመግለጫው አብራርቷል፡፡

ቦርዱ የሁለቱንም ተጓዥ ኮሚቴዎች ሪፖርት ማክሰኞ ጥር 30 ቀን ከተመለከተ በኋላ፣ ባህር ዳር ዓለም አቀፍ ስታዲየም ምንም እንኳን መጫወቻ ሜዳው የተስተካከለ ቢሆንም፣ ስታዲየሙ ለተጨማሪ ሥራ ኮንትራት የተሰጠ ስለሆነ፣ ይህንን የግንባታ ሥራ ማስቆም እንደሚቸግራቸው በቃል ደረጃ ገልጸዋል፡፡

 በአንፃሩ የድሬዳዋ ዓለም አቀፍ ስታዲየም የሜዳውን ሁኔታ በመመልከት እንዲሁም የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደርና የከተማው ፀጥታ ክፍል ውድድሩን ለማካሄድ ሙሉ ዝግጅት ማድረጉን በደብዳቤ ጭምር ማረጋገጡን አክሲዮን ማኅበሩ አብራርቷል፡፡

በዚህም መሠረት የሊግ ጨዋታ ከተቋረጠበት የ12ኛ ሳምንታት ተስተካካይ ጨዋታ፣ በተጠባቂው ቅዱስ ጊዮርጊስ ከኢትዮጵያ ቡና በሚያደርጉት የሸገር ደርቢ ቅዳሜ የካቲት 4 ቀን ከቀኑ 11፡00 ሰዓት በድሬዳዋ ዓለም አቀፍ ስታዲየም የሚጀምር መሆኑን አክስዮን ማኅበሩ አስታውቋል፡፡

የሊጉ ውድድሮች በተለያዩ ከተሞች በዙር መከናወን ከጀመሩበት ጊዜ አንስቶ የተለያዩ ጥያቄዎች ሲነሱ መክረማቸው ይታወሳል፡፡ ክለቦች ‹‹በዙር የሚደረገው ውድድር ለከፍተኛ ወጪ እየዳረገን ነው›› የሚል ቅሬታ ሲያቀርቡ የነበረ ሲሆን፣ በሌላ በኩል የአስተናጋጅ ከተሞች ርቀት ምክንያት ተመልካቾች የክለቦቻቸውን ጨዋታ መመልከት እንደተሳናቸው ሲያነሱ ከርመዋል፡፡

በተለይ የወላይታ ድቻ፣ ሲዳማ ቡና፣ አርባ ምንጭ ከተማና ሐዲያ ሆሳዕና ደጋፊዎች ላለፉት ሁለት ዓመታት ጨዋታ መመልከት አለመቻላቸውንና የሊጉ ጨዋታ አማካይ ከተማ ላይ እንዲከናወን አስተያየት ሲሰነዝሩ ነበር፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

[ክቡር ሚኒስትሩ ከሚያከብሯቸው አንድ የቀድሞ ጉምቱ ፖለቲከኛ ስልክ ተደውሎላቸው እያወሩ ነው]

አንዳንድ ነገሮች ቢያሳስቡኝ ነው ቀጠሮ ሳልይዝ ላወራህ የፈለኩት ክቡር...

የትግራይ ክልል የሽግግር አስተዳደር ምሥረታና የሰላም ስምምነቱ ሒደት

በትግራይ ክልል ጊዜያዊ የሽግግር መንግሥት ለመመሥረት ደፋ ቀና እየተባለ...

ጥራዝ ነጠቅነት!

ከሜክሲኮ ወደ ጀሞ እየሄድን ነው፡፡ የተሳፈርንበት አሮጌ ሚኒባስ ታክሲ...