በኢትዮጵያ ለተጎጂ ዜጎች ፍትሕ ለመስጠትና እየታዩ ያሉ ቁርሾዎችን ለመፍታት ታስቦ በዝግጅት ሒደት ላይ ባለው የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ፣ ሒደቱ በየትኛው ዘመን ይጀምር ለሚለውና በሌሎች ጉዳዮች ላይ ዜጎች አስተያየታቸውን እንዲሰጡ ተጠየቀ፡፡
በታኅሳስ 2015 ዓ.ም. መጀመርያ አካባቢ የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ አቅጣጫ አማራጮችን የያዘ ሰነድ ተዘጋጅቶ፣ ለሕዝብ ይፋ አስተያየትና ውይይት ክፍት የተደረገ ሲሆን፣ የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ አዘጋጅ ባለሙያዎች ዜጎች አስተያየት እንዲሰጡ ዓርብ ጥር 26 ቀን 2015 ዓ.ም. ለሚዲያዎች በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ጥሪ አቅርበዋል።
ባለፉት ጊዜያት የተፈጸሙ ኢፍትሐዊነት፣ በደሎች፣ እንዲሁም የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን በተመለከተ በአግባቡ ምላሽ ለመስጠት እንዲያስችልና በተሰጠው ምላሽ የነበረውን ምዕራፍ ዘግቶ ዘላቂ ዕርቅ፣ ሰላም፣ አንድነትና ዴሞክራሲያዊ ሽግግር ማድረግ ዓላማ የያዘ የፖሊሲ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን፣ የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ አዘጋጅ ባለሙያዎች ቡድን አባል የሆኑት ወ/ሮ ቃልኪዳን ደረጀ ተናግረዋል፡፡
በሽግግር ፍትሕ ሒደት እርስ በርስ የተጠላለፉና ወደፊትና ወደኋላ የሚመለከቱ ሒደቶችን የመፍትሔ አቅጣጫ የያዘ ስለመሆኑም አክለው ተናግረዋል፡፡
የፖሊሲ ግብዓት ለመሰብሰብ በተዘጋጀውና የአማራጭ አቅጣጫዎቾን በያዘው የዚህ ሰነድ የመጨረሻ ክፍል ላይ፣ የሽግግር ፍትሕ ሒደት ከየትኛው ጊዜ ይጀምር የሚል የተለያዩ አማራጭ ሐሳቦችን ይዟል። ይህ ክፍል ሒደቱ የሚሸፍናቸውን የጊዜ መነሻና መድረሻ ስለመወሰን ያብራራል፡፡ በዚህም ከ1983 ዓ.ም. በፊት፣ ከ1983 ዓ.ም. ጀምሮ፣ ከ1987 ዓ.ም. ጀምሮ ያለው፣ ከ2010 ዓ.ም. ጀምሮ በሚል ከፋፍሏቸዋል፡፡
በእያንዳንዱ የተቀመጠ የጊዜ ገደብ ውስጥ የራሱ የሆነ ጠንካራና ደካማ ጎን የተቀመጠለት ሲሆን፣ በሁሉም የአገሪቱ አካባቢዎች ትርጉም ያለው ውይይት ይካሄድበታል ተብሏል፡፡ በውይይቱ ተጨማሪ ምክክር ያስፈልጋል የሚል ሐሳብ ከመጣ ሊታይ እንደሚችል የተናገሩት የባለሙያዎች ቡድን አባል የሆኑት አቶ ምሥጋናው ሙሉጌታ ናቸው፡፡
በቀጣይ ግብዓት ሲሰበሰብ በፖሊሲ መካተት ያለባቸውና ያልተካተቱ ሐሳቦች ተጨምረውበት ወደ ሥራ እንዲገባ፣ ሁሉም ኢትዮጵያውያን ድምፃቸውን እንዲያሰሙ ሐሳባቸውን እንዲሰነዝሩ አቶ ምሥጋናው አሳስበዋል፡፡