የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትሕ (ኢዜማ) በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ላይ የሚስተዋሉ ጣልቃ ገብነቶች መዘዛቸው ከባድ መሆኑን አስታወቀ፡?r”
ኢዜማ ማክሰኞ ጥር 23 ቀን 2015 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ፣ በቤተ ክርስቲያኗ ውስጥ የተፈጠረውን ችግር በአንክሮ ሲከታተል መቆየቱን አስታውቋል፡፡
ይሁን እንጂ ኢትዮጵያ አሁን እየተዳደረችበት ባለው ሕገ መንግሥት አንቀጽ 11 ላይ በግልጽ እንደሰፈረው መንግሥትና ሃይማኖት የተለያዩ ናቸው ቢባልም፣ መንግሥት በሃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ አይገባም፣ ሃይማኖትም በመንግሥት ጉዳይ ጣልቃ አይገባም ብሎ ከደነገገው በተቃራኒ የፀጥታ ኃይሎች ምንም ዓይነት ዕርምጃ እንዳይወስዱ ኢዜማ አስጠንቅቋል፡፡
ፓርቲው በኢትዮጵያ የሚገኙ የእምነት ተቋማት የማኅበረሰቡን እሴት በመገንባት የሚጫወቱት ሚና ከፍተኛ እንደሆነ፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህሕዶ ቤተ ክርስቲያንም በዚህ ረገድ ተጠቃሽ መሆኗን አክሏል፡፡
በመሆኑም መንግሥት በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የውስጥ ጉዳይ ከተለያዩ አቅጣጫዎች እየተስተዋሉ ያሉ ጣልቃ ገብነቶች መዘዛቸው ከባድ መሆኑን ተረድቶ፣ በአስቸኳይ ሕግና ሥርዓት አክብሮ እንዲያስከብር ኢዜማ በመግለጫው ጠይቋል፡፡
የተለያዩ የፖለቲካ ዓላማ ያነገቡ ግለሰቦችም ሆኑ ሌሎች ቡድኖች በተፈጠረው ችግር ውስጥ የሚያደርጉት ተሳትፎ ችግሩን በማባባስ ደም አፋሳሽ ግጭት ሊያስከትሉ የሚችሉ አዝማሚያዎች እየተስተዋሉ በመሆናቸው፣ መንግሥት ራሱን ጨምሮ ሌሎች የአደጋ ሥጋት ምንጮችን ገምግሞ አፋጣኝ ዕርምጃ እንዲወስድ አሳስቧል፡፡
የፓርቲው መግለጫ አክሎም በሃይማኖት ተቋማት ላይ በማናቸውም ወገን የሚደረግ ጣልቃ ገብነት መዘዙ ብዙ መሆኑን በመጥቀስ፣ የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ከፍተኛ ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርቧል፡፡
ፖለቲካ በዘር፣ በሃይማኖትና ሌሎች ልዩነቶች ላይ ሳይሆን ሕዝቡን በእኩልነት በሚያስተሳስረው ዜግነት ላይ ሊሆን እንደሚገባ አሁንም በፅኑ እንደሚያምን ኢዜማ በመግለጫ አትቷል፡፡