በዋልያዎቹ የቻን ተሳትፎ ምክንያት ተቋርጦ የነበረው ቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ውድድር ከሳምንት በኋላ ይጀመራል።
በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አክሲዮን ማኅበር የሚተዳደረው የቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ መርሐ ግብር ከብሔራዊ ቡድን የቻን ተሳትፎ አምስት ቀናት በኋላ ውድድሩ እንደሚቀጥል ታውቋል።
ብሔራዊ ቡድኑ በውድድሩ ሁለት የምድብ ጨዋታዎችን አድርጎ በአንድ ነጥብ ሦስተኛ ደረጃ ላይ የተቀመጠ ሲሆን፣ የመጨረሻ የምድብ ፍልሚያውን አከናውኖ ወደ ቀጣይ ዙር ማለፍና አለማለፉን ይለያል።
የፕሪሚየር ሊጉ መርሐ ግብር ከ12ኛ ሳምንት ጨዋታዎች በኋላ እንደሚቋረጥ፣ የሊጉ አክሲዮን ማኅበር ቢያሳውቅም፣ እስከ 14 ሳምንት ድረስ እንዲቀጥል መደረጉ ይታወሳል። ከጥቅምት 25 ቀን 2015 ዓ.ም. ስድስተኛ ሳምንታት ጀምሮ በድሬዳዋ ሲከናወን ቆይቷል።
የሊጉን ሁለተኛ ዙር ውድድር ከስድስተኛ እስከ አሥረኛ ሳምንታት ድረስ ያሉትን መርሐ ግብሮች ለማከናወን ከባህር ዳር ተረክቦ ውድድሮችን ሲያከናውን የቆየው ድሬዳዋ ከተማ፣ እስከ 13ኛ ሳምንት ያሉትን ጨዋታዎች አስተናግዶ ከታኅሣሥ 17 በኋላ እንዲቋረጥ ተደርጓል።
በዚህም የሦስተኛ ዙር ጨዋታዎች ከ11ኛ ሳምንት ጀምሮ ማስተናገድ የነበረበት የአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ የነበረ ቢሆንም፣ ጨዋታዎቹ እንዳይቆራረጡ በሚል ሐሳብ በድሬዳዋ እንዲቀጥል መደረጉን የሊጉ አክሲዮን ማኅበር ሥራ አስኪያጅ አቶ ክፍሌ ሰይፈ ለሪፖርተር ማስረዳታቸው ይታወሳል።
የሦስተኛውን ዙር የቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ውድድርን የሚያስተናግደው የአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ የመጫወቻ ሜዳውና፣ ተያያዥ ነገሮች ላይ ዕድሳትና ማሻሻያ እንዲያደርግ በአክሲዮን ማኅበሩ መታዘዙ ይታወቃል፡፡ አክሲዮን ማኅበሩም ስታዲየሙ በሚፈለገው መጠን ማሻሻያና ዕድሳት ማድረጉን የአጣሪ ቡድኑ ክትትል ሲያደርግ መቆየቱ የተጠቀሰ ሲሆን፣ ስታዲየሙም ውድድሩን ለማዘጋጀት በሚያስችለው ደረጃ ላይ መድረሱን ማረጋገጡን አቶ ክፍሌ ገልጸዋል፡፡
ሥራ አስኪያጁ፣ ውድድሩን ለማስቀጠል ምቹ የሆነ የመጫወቻ ሜዳ ማግኘት ፈታኝ እንደሆነ ገልጸው፣ ሊጉን ሳይቆራረጥ እንዲቀጥል አዘጋጁ ከተሞች ደረጃውን የጠበቀ ስታዲየም ለማሰናዳት አስፈላጊውን ጥረት ማድረግ ይገባቸዋል ብለዋል፡፡
በሌላ በኩል የሊጉ ውድድሮች በዙር ሲከናወኑ፣ በተመልካች ዕጦት ሲመቱ መክረማቸው የተገለጸ ሲሆን፣ በተለይ ውድድሮቹ የሚከናወኑባቸው ከተሞች ለተመልካች ቅርብ አለመሆናቸው ዋነኛ መንስዔ መሆኑ ተጠቅሶ ነበር፡፡ በዚህም መሠረት አዲስ አበባ ለበርካታ ተመልካቾች አማካይ ከተማ በመሆኗ የተመልካች እጥረት ችግርን ሊቀርፍ ስለሚችል፣ የስታዲየሙ ግንባታ በታቀደለት ጊዜ የሚጠናቀቅ ከሆነ አብዛኛውን የሊጉን ጨዋታ በአዲስ አበባ ለማድረግ ሐሳብ መኖሩን አክሲዮን ማኅበሩ ጠቁሞ ነበር፡፡
ከአዲስ አበባ ባሻገር የአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ስታዲየም ሌላው ለተመልካች አማካይ የውድድር ቦታ በመሆኑ፣ የተወሰኑ ጨዋታዎች ላይ ሽግሽግ መደረጉ ይታወሳል፡፡ በዚህም መሠረት በ12ኛ ሳምንት ሊከናወኑ የነበሩ የቅዱስ ጊዮርጊስና ኢትዮጵያ ቡና ደርቢ እንዲሁም የ11ኛ ሳምንት የወላይታ ድቻና ሲዳማ ቡና ጨዋታዎች ወደ አዳማ መዘዋወራቸውን አክሲዮን ማኅበሩ አስታውቋል፡፡