ሦስት ባልንጀሮች
ያውም ዘመዳሞች
ክፉ፣ ደጉን ዘመን ሁሉንም ሲጋሩ
በአንዲት ጐጆ ነበር አብረው የሚኖሩ
ኋላ ግን ሰይጣን መልዐክ ተመስሎ
ገባ ወደ ጐጆው ክፉ ስንቁን አዝሎ
በተባ ምላሱም ቢወሰውሳቸው
በአንድ እግሯ ቀጥ አለች የጋራ ጐጇቸው
ታላቁ ተነሳ በቁጣ በንዴት
‹‹ገሀነም ነው!›› አለ ይሄ የጋራ ቤት
‹‹በዚህ አጉል ጐጆ ሳዝንና ስከፋ
ኖሬያለሁ በስቃይ መከራ ስገፋ
ጎበዝ ይሄ ጎጆ በቃ ይፍረስ! ይጥፋ!››
ይህንን ተናግሮ ብሶቱን ሊወጣ
ቤንዚንና ክብሪት ይዞ ከደጅ ወጣ
ሌላው ግን አጥብቆ ይህን ተቃወመ
‹‹ቤቱ እንዳይነካ!›› ብሎ ደመደመ
‹‹ማነው የእኛን ጐጆ እናፍርስ የሚለው?
እጅግ ተስማምቶናል ምንም እንከን የለው››
እያለ እያቅራራ ሸለለ፣ ተቆጣ
መጥረቢያውን ይዞ ከቤቱ እየወጣ
ደግሞም ሦስተኛው ነገሩን ሰማና
እንደዚህ አላቸው እሱም ተነሳና
‹‹›ጐጇችን አይፈርስም፣ እንዲሁም አንኖርም
ግን ይሄንን ጐጆ ሳናድስ አንቀርም
በአሮጌው አንኑር – ቤቱም አይቃጠል
ግን ትንሽ ታድሶ ይረጭበት ፀበል!››
ብሎ እየፎከረ ወጣ በበኩሉ
እሱም ጦሩን መዞ አይሆንም ለሚሉ
ነገር ተበጥብጦ ከውስጥም – ከላይዋ
የዚህች ጐጆ ነገር ምን ይሆን እጣዋ?
- ሰሎሞን ሞገስ ‹‹ከፀሐይ በታች›› (2004)