አማራ ባንክ ወደፊት ይጠብቀኛል ላለው ውድድር የባንኩ ካፒታል ወደ 20 ቢሊዮን ብር እንዲያድግ ያቀረበውን የውሳኔ ሐሳብን የባንኩ ለባለአክሲዮኖች ተቀብለው አፀደቁ፡፡
ባንኩ ባለፈው ሐሙስ ባካሄደው ጠቅላላ ጉባዔው ላይ የባንኩን ካፒታል ማሳደግ አስፈላጊነትን በተመለከተ ሰፊ ማብራሪያ ተሰጥቷል፡፡ በተለይ የባንኩ የዳይሬክተሮች ቦርድ ሊቀመንበር አቶ መላኩ ፈንታ፣ በኢትዮጵያ የባንክ ዘርፍ ከዚህ ቀደም ያልነበሩ አዳዲስ ለውጦች እየተከሰቱ በመሆኑ በተለይም ዘርፉ ለውጭ ባንኮች ውድድር ክፍት እንዲሆን በመወሰኑ መጪውን ውድድር ተቋቁሞ ለመቀጠል የባንኩን ካፒታል ማሳደግ አስፈላጊ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡
በተለይ የውጭ ባንኮች ወደ ኢትዮጵያ የባንክ ዘርፍ እንዲገቡ መንግሥት መወሰኑ የአገር ውስጥ ባንኮችን ወደ ውህደትና መቀላቀል እንዲሁም አንዱ ሌላውን የመግዛት ሁኔታን ሊያስከትል እንደሚችል አቶ መላኩ ጠቅሰው፣ ከወዲሁም ነባርና አዳዲስ የአገር ውስጥ ባንኮች በተስፋና በሥጋት ውስጥ ሆነው ሁኔታውን እንዲከታተሉ አድርጓቸዋል ብለዋል።
አንዳንዶችም ሥጋታቸውን ለመቀነስና ለመጪው ሁኔታ ራሳቸውን ዝግጁ ለማድረግ የተለያዩ ዕርምጃዎችን እየወሰዱ መሆኑን፣ ከእነዚህ ዕርምጃዎች መካከልም ካፒታላቸውን ማሳደግ ዋና ተግባር እንደሆነ በማንሳት አማራ ባንክም ካፒታሉን ማሳደግ ግድ እንደሚለው አስረድተዋል፡፡
‹‹ምንም እንኳን አማራ ባንክ ከፍተኛ የተፈረመና የተከፈለ ካፒታል መጠን ይዞ ዘርፉን ቢቀላቀልም ከነባር ባንኮች የካፒታል ምጣኔና ከሚመጣው ውድድር አንፃር አሁን ያለው ካፒታል በቂ አይደለም፤›› ያሉት አቶ መላኩ፣ ባንኩ ሁነኛ ተወዳዳሪ ብሎም አሸናፊ ሆኖ እንዲቀጥል ከተፈለገ የባንኩን የካፒታል መጠን ማሳደግ እንደሚገባ አመልክተዋል፡፡ ለውህደት ወይም ለመግዛት እንዲሁም ከውጭ ባንኮች ጋር አብሮ በጋራ ለመሥራት የባንኩን ካፒታል ማሳደግ አስፈላጊ መሆኑን ከቀረበላቸው ማብራሪያ የተረዱት የባንኩ ባለአክሲዮኖችም የባንኩን ካፒታል ለማሳደግ የቀረበውን የውሳኔ ሐሳብ ተቀብለው አፅድቀዋል። በዚህም መሠረት የቀረበውን ተጨማሪ ካፒታል በሦስት ዓመት ጊዜ ውስጥ ሙሉ ለሙሉ ከፍሎ ለማጠናቀቅ ወስነዋል፡፡
የባንኩን ካፒታል ወደ 20 ቢሊዮን ብር ለማሳደግ በተወሰነው መሠረትም አዳዲስ አክሲዮኖች ለነባር ባለአክሲዮኖች፣ ለባንኩ ሠራተኞችና ለአዲስ ገዥዎች ተከፋፍሎ የሚሸጥ ይሆናል፡፡
ወቅታዊውን የአገሪቱን የባንክ ኢንዱስትሪ በማስመልከት የቦርድ ሊቀመንበሩ ባቀረቡት ሪፖርት በዓለም አቀፍ ደረጃ በተፈጠረው ሁኔታ ደግሞ የዋጋ ማሻቀብ የኅብረተሰቡን የመግዛት አቅም ከማዳከሙም በላይ በቁጠባ ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ ሊኖረው እንደሚችል ይታመናል ብለዋል፡፡ በመሆኑም በአሁኑ ወቅት ከተከሰተው ዓለም አቀፋዊና አገራዊ ሁኔታ አንፃር የገጠሙ ችግሮችን መኖራቸውን ገልጸው፣ በተለይ ከባንካቸው ባህሪ አንፃር የአማራ ባንክ የአክሲዮን መጠን ከምሥረታው በኋላ በተፈለገው መጠን አለመጨመር አንዱ ተግዳሮት ነበር ብለዋል፡፡ የቅርንጫፎች የኪራይ ዋጋ በከፍተኛ መጠን መጨመርና ለገበያ አመቺ ያለመሆን፣ እንዲሁም ለቅርንጫፍ የሚሆኑ ቢሮዎችን አለማግኘት፣ የዋጋ ግሽበት በግዥ ሒደት ላይ ከፍተኛ ጫና ማሳደሩ ገጠመን ካሏቸው ችግሮች መካከል ተካተዋል፡፡ የተወዳዳሪ ባንኮችና የአማራ ባንክ ክፍያና ጥቅማ ጥቅም አለመመጣጠን፣ ባንኩ ተወዳዳሪ የሚያደርገውን ባለሙያዎችን በፈለገው ጊዜ አለማግኘት፣ ባንኩ ጀማሪ እንደመሆኑ መጠን የአሠራርና የአመለካከት እንዲሁም ተቋማዊ ባህል አለመዳበር፣ አማራ ባንክ ካጋጠሙት ዓበይት ተግዳሮቶች መካከል የሚጠቀሱ ናቸው ብለዋል፡፡
ይሁንና የባንክ ኢንዱስትሪው በተግዳሮት ውስጥ ባለበት ወቅት አማራ ባንክ በሁሉም አመለካከቶች ዕድገት ማስመዝገቡን የገለጹት አቶ መላኩ፣ ባንኩ በ2014 የሒሳብ ዓመት በሠራባቸው 11 ቀናት ውስጥ ተስፋ ሰጪ ውጤቶች ማስመዝገቡን በሪፖርታቸው አመልክተዋል፡፡
በዚህም ሪፖርታቸው ከሰኔ 18 እስከ ሰኔ 30 ቀን 2022 ባሉት አሥራ አንድ ቀናት 531 ሚሊዮን ብር ገቢ ማግኘቱንና ከታክስ በፊት 237 ሚሊዮን ብር ማትረፍ መቻሉን ገልጸዋል፡፡ ባንኩ ሁለት ሳምንት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ አገኘ የተባለውን ከፍተኛ ትርፍ በተመለከተ ሪፖርተር ባደረገው ማጣራት የተገኘው ትርፍ ከባንክ ሥራ የመነጨ ሳይሆን ባንኩ በሌሎች ባንኮች ካስቀመጠው ተቀማጭ ገንዘብ ያገኘው የወለድ ገቢና ከአገልግሎት ክፍያ የተገኘ ትርፍ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡
በባንኩ ሪፖርት መሠረት በ2014 የሒሳብ ዓመት መጨረሻ ላይ በነበሩት 75 ቅርንጫፎች 401 ሚሊዮን ብር ተቀማጭ ገንዘብ ማሰባሰቡንና 82 ሺሕ አስቀማጮች ማፍራት መቻሉንም አቶ መላኩ ገልጸዋል፡፡ ከ2014 የሒሳብ ዓመት መዝጊያ አንስቶ እ.ኤ.አ. እስከ ታኅሳስ 24 ቀን 2022 ባለው ጊዜ ውስጥ ደግሞ የባንኩ ተቀማጭ ገንዘብ መጠን 8.7 ቢሊዮን ብር፣ የቅርንጫፎች ብዛት ደግሞ 201 መድረሱን አቶ መላኩ ገልጸዋል። የቦርድ ሊቀመንበሩ እንደገለጹት፣ የባንኩ አስቀማጭ ደንበኞች ቁጥር አሁን ላይ ከግማሽ ሚሊዮን (550,000) በላይ የደረሰ ሲሆን፣ ባንኩ የሰጠው አጠቃላይ የብድር መጠን ደግሞ 6.5 ቢሊዮን ብር ነው። የባንኩ የተከፈለ ካፒትል 5.3 ቢሊዮን ብር መድረሱም ታውቋል፡፡ በ2014 የሒሳብ ዓመት መጨረሻ ላይ በብሔራዊ ባንክ የፀደቀለት የተከፈለ ካፒታል ግን 4.8 ቢሊዮን ብር እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል፡፡ በዚህ ካፒታል መጠን ዙሪያ ተጨማሪ ማብራሪያ የሰጡት የአማራ ባንክ ፕሬዚዳንት አቶ ሔኖክ ከበደ፣ በመተዳደሪያ ደንቡና መመሥረቻ ጽሑፉ ላይ ያልፈረሙ ባለአክሲዮኖች ድርሻ እንዲካተት ቢፈቀድ ኖሮ የተከፈለው ካፒታል መጠን ከዚህም ከፍ ሊል እንደሚችል አስረድተዋል። አክለውም፣ በአሁኑ ወቅት ብዙዎቹ ባለአክሲዮኖች ቀሪ ክፍያቸውን እየከፈሉ በመሆኑ ይህ የተከፈለ ካፒታል መጠን ወደ 5.5 ቢሊዮን ብር አካባቢ እየደረሰ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡
አማራ ባንክ አውጥቶት ለነበረው የሥራ ማስታወቂያ ወደ 300 ሺሕ ሥራ ፈላጊዎች አመልክተው እንደነበር የጠቀሱት ፕሬዚዳንቱ፣ ከዚህ ውስጥ 20 ሺሕ የሚሆኑት ፈተና ወስደው የተመረጡ 3,000 ሠራተኞች ተቀጥረዋል።
በአሁኑ ወቅት የዘጠኝ ኤትኤሞችን ሥራ ማስጀመሩንና የ125 ኤትኤሞች ግዥ እየተከናወነ ነው፡፡ አጠቃላይ የባንኩ ሀብት ደግሞ በ2014 የሒሳብ ዓመት መጨረሻ ላይ 7.1 ቢሊዮን ብር መድረሱን አቶ ሔኖክ ገልጸዋል፡፡ አማራ ባንክ ኢትዮጵያ ውስጥ ካሉ ባንኮች ከፍተኛ ቁጥር ያላቸውን ባለአክሲዮኖች የያዘ ሲሆን፣ ሰኔ 2014 ዓ.ም. መጨረሻ ላይ በብሔራዊ ባንክ ያፀደቀለት የባለአክሲዮኖች ቁጥር 141 ሺሕ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡