Thursday, March 23, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ዜናመንግሥት ከሕወሓት ጋር ያደረገውን የሰላም ስምምነት ከኦነግ ሸኔም ጋር እንዲደግም ተጠየቀ

መንግሥት ከሕወሓት ጋር ያደረገውን የሰላም ስምምነት ከኦነግ ሸኔም ጋር እንዲደግም ተጠየቀ

ቀን:

የፌዴራል መንግሥት ከሕወሓት ጋር የጀመረውን የሰላም ስምምነት፣ በኦሮሚያ ክልል ንፁኃን እያለቁበት ያለውን ችግር ለመፍታት ከኦነግ ሸኔም ጋር እንዲደግም የፖለቲካ ፓርቲዎች ጥያቄ አቀረቡ፡፡

ሁለት ዓመታት ባስቆጠረው የሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎች ሞተውና በርካቶች ቆስለው፣ ከ25 ቢሊዮን ዶላር በላይ የሚተመን ሀብት ከወደመ በኋላ፣ የፌዴራል መንግሥትና ሕወሓት የሰላም ስምምነት አድርገው ጦርነቱ በመቆሙ ዜጎች የሰላም አየር መተንፈስ መጀመራቸውን ፓርቲዎቹ ተናግረዋል፡፡  

ይሁን እንጂ በሰሜን የአገሪቱ ክፍል የነበረው ጦርነት ጋብ ቢልም በምዕራብ በኩል በተለይም በኦሮሚያና ቤንሻንጉል ክልል የሚታየው የንፁኃን ዜጎችን ሞት ለማስቆም፣ የፌዴራል መንግሥቱ ተመሳሳይ ዕርምጃ መውሰድ እንዳለበት የፖለቲካ ፓርቲዎቹ አሳስበዋል፡፡

ጥያቄው የቀረበው የጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) የብሔራዊ ደኅንነት አማካሪ ሬድዋን ሁሴን (አምባሳደር) ለበርካታ የፖለቲካ ፓርቲዎች የፌዴራል መንግሥቱ ከሕወሓት ጋር እያካሄደ ስላለው ሰላማዊ ድርድር ማብራሪያ በሰጡበት ወቅት ነው፡፡

ምርጫው ስንሻው የተባሉ የአማራ ግዮናዊ ንቅናቄ ፓርቲ አባል የአማራ ክልል ሕዝብ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ላይ ትልቅ ተቃውሞ አለው ብለው፣ የአማራ ተወላጆች በወለጋ ሲጨፈጨፉ መንግሥት ጆሮ ዳባ ልበስ የማለቱ ሚስጥር አማራውን በእጅጉ አሳዝኗል፣ ጎድቶታልም ብለዋል፡፡ አክለውም ጭፍጨፋውን በተመለከተ መንግሥት ዝምታው ለምን ይሆን ሲሉ ጠይቀዋል፡፡

የአርጎባ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ አባል ሙሐመድ ሙሳ፣ መንግሥት በትግራይ ክልል የወሰደውን የሰላም ዕርምጃና ጥረት በየትኛውም የአገሪቱ ክፍል እየተከሰተ ያለውን ውጊያና ግድያ ለማስቆም ለምን አይጠቀምበትም ሲሉ ጠይቀዋል፡፡  

‹‹አሁን ለትግራይ ክልል ሰላም ተሰጥቶ ለኦሮሞ ሕዝብ ደግሞ ድሮንና ጥይት ተሰጥቷል፣ ደግሞ ያሉት የኦነግ አባል አቶ ጄቤሳ ገቢሳ ናቸው፡፡

‹‹ሰላም አይከፋፈልም›› ያሉት አቶ ጄቤሳ፣ ‹‹መንግሥት ማዕከላዊ ኮማንድ የላቸውም፣ የፖለቲካ ዓላማ የላቸውም በሚል በተዋቸው አካላት ምክንያት የሚፈጠረውን ጥፋት ማስቆም አለመቻሉ ስንት ኦሮሞ እስከሚያልቅ ነው የሚጠብቀው? መቼስ ነው ይህን ችግር በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት የሚሞክረው?›› በማለት ጠይቀዋል፡፡

የአረና ፓርቲ አመራር አቶ ገብሩ አሥራት ከኦነግ ሸኔ ጋር ያለው ችግር  ከሕወሓት ጋር በተደረገው መንገድ ምክክርና ውይይት በማካሄድ፣ ለአካባቢው ሕዝብ ሰላም ማምጣት ለምን እንዳልተቻለ ጠይቀዋል፡፡

‹‹ይህ ካልሆነ ችግሩን በአመፅ እንመልሰዋለን ብሎ ማሰብ በትግራይ ክልል ያጋጠመውን ቀውስ መድገም ሊሆን ስለሚችል፣ በሰሜን የአገሪቱ ክፍል የታየውን ዕልቂት መድገም ይሆናል፤›› ብለዋል፡፡

የጉምዝ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ ሊቀመንበር አቶ ግራኝ ጉደታ፣ ‹‹መንግሥት በሰሜኑ ክፍል የጀመረውን የሰላም ስምምነት በምዕራቡ ያለውን ችግር ለመፍታት ለምን ዝምታን መረጠ?›› ብለዋል፡፡ አክለውም የኦነግ ሸኔ ጥቃት ወደ ቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል እየተዛመተ በመሆኑ ትኩረት ይሰጠው ሲሉ ጠይቀዋል፡፡

‹‹ከሕወሓት ጋር ከተፈጠረው ጦርነት ባልተናነሰ የኦነግ ሸኔ ከፍተኛ ተግዳሮት ደቅኗል፡፡ ይሁን እንጂ መንግሥት ጉዳዩን በተመለከተ እየሰጠ ያለው መልሰ ይህ ተዋጊ አካል የተደራጀ የፖለቲካ ኃይልና አቋም የለውም፤›› የሚል መሆኑን የተናገሩት የአገው ብሔራዊ ሸንጎ አባል አቶ አላምረው ይርዳው ናቸው፡፡ ‹‹ይህ የተደራጀ አካል ምንስ ኖረው አልኖረው የአገሪቱን ሰላም እስከነሳ ድረስ ይህ ምን ያደርግላችኋል?  ግለሰብስ ቢሆን ጉዳዩን በሰላም ለመፍታት ለምን ጥረት አታደርጉም?›› ሲሉ ጠይቀዋል፡፡

ሬድዋን (አምባሳደር) ለፖለቲካ ፓርዎች በሰጡት ማብራሪያ አገር መምራት ከባድ ነው በማለት ምላሽ ሰጥተዋል፡፡

‹‹ሁሉም ሰው ኢትዮጵያን ይወዳል፣ ነገር ግን ከግጥሙና ከዘፈኑ ባለፈ መሬት ላይ ልንሠራና ልንተገብረው ስንሞክር አገርን እንዴት ነው መምራት የምንችለው? ያለ ለቅሶ፣ ሐሜትና ጉንተላ፣ መሣሪያ ሳናነሳ ከሞላ ጎደል ይበቃናል ብለን ብንሠራ ፍላጎታችንን እንዴት ነው ማሳካት የምንችለው?›› ብለው እንዲጠይቁ ለፓርቲዎቹ አመራሮች ተናግረዋል፡፡

አክለውም አገርን መምራት ከባድ በመሆኑ መንግሥትን ከመጠየቅ ባለፈ፣ ‹‹ይህን አገር እኔ ብመራው እንዴት ነው  በአፋር፣ በኦሮሚያ፣ በአማራና በትግራይ፣ እንዲሁም በሌላው አካባቢ ግጭት እንዳይፈጠር አድርጌ መምራት የምችለው የሚለውን ማሰብ አለብን፤›› ብለዋል፡፡

‹‹አንዳንድ ጊዜ ጥያቄ ሲጠየቅ ሌላኛውን ፍላታችንን የሚያፈርስ በመሆኑ፣ ይህን ዓይነት ጥያቄ ለመመለስ ደግሞ በተጀመረው አገራዊ ምክክር ሁሉም የሚመስለውን ይዞ በመቅረብ ሐሳቡን እያብላላ፣ እየተነጋገረ፣ በጋራ እያነሳና እየጣለ ለመፍትሔው መሥራት አለበት፤›› ሲሉ ተነግረዋል፡፡

ሬድዋን (አምባሳደር) በምሳሌ ሲያብራሩ፣ ‹‹የወባ መድኃኒት ሰዎች ሲወስዱት ይመራል፡፡ ነገር ግን የሚመረውን ወስዶ የባሰውን በሽታ ለማከም ነው ይህ የሚሆነው፡፡ ደግሞ ከጥፋት ለመዳን ነው፡፡ ነገር ግን አገር ውስጥ እውነትን መዋጥ ከሚፈልግ ይልቅ፣ ሌላ ሰው እንዲውጥለት የሚፈልገው ይበዛል፡፡ ይህንን ካልፈታን ግን አገር አይቆምም፤›› ብለዋል፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

[ክቡር ሚኒስትሩ ከሚያከብሯቸው አንድ የቀድሞ ጉምቱ ፖለቲከኛ ስልክ ተደውሎላቸው እያወሩ ነው]

አንዳንድ ነገሮች ቢያሳስቡኝ ነው ቀጠሮ ሳልይዝ ላወራህ የፈለኩት ክቡር...

የትግራይ ክልል የሽግግር አስተዳደር ምሥረታና የሰላም ስምምነቱ ሒደት

በትግራይ ክልል ጊዜያዊ የሽግግር መንግሥት ለመመሥረት ደፋ ቀና እየተባለ...

ጥራዝ ነጠቅነት!

ከሜክሲኮ ወደ ጀሞ እየሄድን ነው፡፡ የተሳፈርንበት አሮጌ ሚኒባስ ታክሲ...