- ብሔራዊ ፌዴሬሽኑ ማንኛውም አትሌት የሚወስደውን መድኃኒት ማሳወቅ አለበት ብሏል
የዓለም አቀፍ የፀረ አበረታች ቅመሞች ኤጀንሲ (ዋዳ) አትሌቶች ‹‹ትራማዶል›› የተሰኘውን መድኃኒት እንዳይወስዱ አስጠነቀቀ፡፡
በየዓመቱ የተከለከሉ የፀረ አበረታች ቅመሞችን ዝርዝር ይፋ የሚያደርገው ዋዳ፣ ማንኛውም አትሌት ትራማዶል መድኃኒትን መጠቀም እንደማይችል ይፋ ያደረገ ሲሆን፣ የአትሌቲክስ ፌዴሬሽኖች፣ ብሔራዊ ፀረ አበረታች ተቋማት እንዲሁም ባለድርሻ አካላት ጋር ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ አሳስቧል፡፡
የዓለም ፀረ አበረታች ቅመሞች ኤጀንሲ (ዋዳ) በ2023 የተከለከሉ ንጥረ ነገሮችና ዝርዝሮችን፣ እንዲሁም የክትትል መርሐ ግብር ተግባራዊ እንዲሆኑ በሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴው አማካይነት ካፀደቀ በኋላ ነበር የተከለከሉ ንጥረ ነገሮች ይፋ ያደረገው፡፡
ዋዳ የተከለከሉ መድኃኒቶች በውድድርም ሆነ ከውድድር ውጪ መጠቀም ፍፁም የተከለከለ እንደሆነ አስታውቋል፡፡
በ2023 አትሌቶች እንዳይጠቀሙ ይፋ ካደረጋቸው ውስጥ አንዱ የሆነው ትራማዶል በዋዳ አማካሪ ቡድኖች ንጥረ ነገሩ ከአደንዛዥ ዕፅ ጋር የሚመደብ መሆኑ በመረጋገጡ ነው፡፡ በውድድር ላይ መጠቀም እንደማይቻል የተደነገገው፡፡
ኤጀንሲው ውሳኔውን ተግባራዊ ለማድረግ መዘግየቱን ጠቅሶ፣ ይህም ከአትሌቶች ማናጀሮች፣ አሠልጣኞች፣ እንዲሁም የሕክምና ባለሙያዎች ጋር ሰፊ ግንኙነትና ትምህርት ለመስጠት ተጨማሪ ዓመት በማስፈለጉ እንደሆነ አመልክቷል፡፡
እንደ ዋዳ ማብራሪያ ከሆነ በአትሌቲክሱ አንደኛው አትሌት ለሌላው አትሌት አበረታች ቅመም በመታገዝ ተጠቃሚ እንዳይሆን፣ የተለያዩ ትምህርቶችን በመታገዝ አትሌቶች ሥልጠናዎችን እየሰጠ እንደሚገኝ ገልጿል፡፡
በዚህም መሠረት በቅርቡ ዋዳ ትራማዶል ላይ ከፍተኛ ክትትል ሲያደርግ መቆየቱን የገለጸ ሲሆን፣ መድኃኒቱ ለአትሌቶች የተለየ ኃይል እየሰጠ መቆየቱን ደርሼበታለሁ ብሏል፡፡ ከዚህም ባሻገር በጥናቱ ላይ በተገኘው መረጃ መሠረት ትራማዶልን ያላግባብ መጠቀም፣ አካላዊ ጉዳት እንዲሁም ለሱሰኝነት እንደሚያጋልጥም ገልጿል፡፡
ዋዳ የተከለከሉ መድኃኒቶችን ዝርዝር ይፋ ከማድረጉ አስቀድሞ ዓመታዊ የክለሳ ሒደቶችን የሚከተል ሲሆን፣ የተለያዩ ስብሰባዎችን አድርጎ አዳዲስ ክስተቶች ላይ ይመክራል፡፡ በዚህም መሠረት የተለያዩ መረጃዎችን ካሰባሰበ በኋላ፣ በሳይንሳዊ መንገድ በሕክምና በመታገዝ ጥናቶችን እንደሚያደርግ አስረድቷል፡፡
የኤጀንሲው የጤና፣ ሕክምናና ምርመራ ኮሚቴ ምክረ ሐሳቡን ለሥራ አስፈጻሚው አቅርቦ እንደሚያፀድቅም ተጠቅሷል፡፡ አንድ ንጥረ ነገር ወደሚከለክሉ ዝርዝሮች ውስጥ ለማካተት ሦስት መመዘኛዎች በዋነኛነት የሚታዩ ሲሆን፣ ይህም ንጥረ ነገር የስፖርት እንቅስቃሴ የሚያጎለብት ወይም የሚያሳድግ ከሆነ፣ በአትሌቶች የጤና እክል የሚያስከትል ከሆነ፣ እንዲሁም የስፖርት መንፈስን የሚጎዳ የሚሉት በቀዳሚነት ይታያሉ፡፡
ከቀናት በፊት የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን የ2022 ዓመት እየተጠናቀቀ መምጣቱን ምክንያት በማድረግ የዓለም አትሌቲክስ ኢንተግሪቲ ዩኒት አማካይነት (Athletics Integrity Unit) ቁጥራቸው ከ120 ከሚበልጡ ኢትዮጵያውያን አትሌቶችና ባለድርሻ አካላት ጋር የቨርቹዋል (በይነ መረብ) ውይይት አካሄዷል፡፡
የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ፣ የብሔራዊ ፀረ አበረታች ቅመሞች ባለሥልጣን፣ የፌዴሬሽኑ የሕክምና ባለሙያዎችና አሠልጣኞች ማኅበር በውይይቱ ላይ ተገኝተዋል፡፡
በውይይቱም በተለይ በምርመራ ቋት ውስጥ ለሚገኙ አትሌቶች በወቅታዊና በቀጣይ መከናወን ስላለባቸው የአበረታች ቅመሞች ጥንቃቄ ጉዳዮች በተያያዘ ማሳሰቢያዎች ላይ ተመካክረዋል፡፡
በዚህም መሠረት በብሔራዊ ፀረ አበረታች ቋት ውስጥ የሚገኙ እንዲሁም መላው አትሌቶች በሙሉ በድንገተኛና በቆየ ተመላላሽ ሕመም ምክንያት የሚታዘዙ ማንኛውም ዓይነት መድኃኒቶች ከመውሰዳቸው አስቀድሞ፣ ለኢትዮጵያ አትሌቲስ ፌዴሬሽን ሕክምና ክፍል ማሳወቅ እንደሚገባቸው ፌዴሬሽኑ አሳስቧል፡፡
ከጊዜ ወደ ጊዜ ውስብስብ እየሆነ የመጣው የአበረታች ንጥረ ነገሮች ዝርዝር በተለያዩ የስፖርት ዓይነቶች ላይ በማወቅም ይሁን ባለማወቅ አትሌቶች ሲጠቀሙት ይስተዋላል፡፡
ሆኖም ከዘጠኝ የስፖርት ዓይነቶች ውስጥ በአትሌቲክስ ላይ አበረታች ንጥረ ነገሮችን በመጠቀም በቀዳሚነት ይቀመጣሉ፡፡ እ.ኤ.አ. በ2019 በተደረገ ጥናት መሠረት በአትሌቲክስ ላይ የሚሳተፉ 205 አትሌቶች አበረታች መድኃኒት መጠቀማቸው ተቀምጧል፡፡