የብሔራዊ ሎተሪ አስተዳደር ከተሰጣቸው የስፖርት ውርርድ አጫዋችነት ፈቃድ ውጪ፣ ‹‹ቨርቹዋል ጌም›› የሚባል ያልተፈቀደ ውርርድ ሲያጫውቱ የተገኙ 20 የስፖርት ውርርድ ማጫወቻ ሱቆች (ቅርንጫፎች) መዝጋቱን አስታወቀ፡፡
የብሔራዊ ሎተሪ አስተዳደር የሕዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር አቶ ቴዎድሮስ ንዋይ ለሪፖርተር እንዳስታወቁት፣ ማንኛውም ሎተሪ የሚያጫውት ድርጅት ከብሔራዊ ሎተሪ ፈቃድ ማግኘት አለበት፡፡ በስፖርት ውርርድ አጫዋችነት አገልግሎት ለመስጠት ፈቃድ የወሰዱትን በሕጋዊ መንገድ ቁጥጥር እየተደረገባቸው መሆኑን የገለጹት አቶ ቴዎድሮስ፣ ነገር ግን ከዚያ ውጪ ሕግ ተላልፈው ‹‹ቨርቹዋል ጌም›› የሚያጫውቱ አካላት ላይ ክትትል ተደርጎ ዕርምጃ መወሰዱን ተናግረዋል፡፡
አስተደደሩ ዕርምጃ ከመውሰዱ በፊት በድርጊቱ ላይ ተሳታፊ ሆነው ለተገኙ አካላት ማሳሰቢያ መስጠቱን፣ ይህንን ችላ ብለው ሲንቀሳቀሱ የነበሩ 20 የስፖርት ውርርድ ማጫወቻ ቅርንጫፎችን መዝጋቱ ተገልጿል፡፡
አስተዳደሩ እንዳስታወቀው፣ የቨርቹዋል ውርርድ ጨዋታ ራሱን ችሎ ፈቃድ የሚሰጥበት አይደለም፡፡ ነገር ግን ከብሔራዊ ሎተሪ አስተዳደር የስፖርት ውርርድ ሕጋዊ ፈቃድ የተሰጣቸው ድርጅቶች፣ ከተለያዩ የስፖርት ውድድሮች ጋር በማጣመር በሕግ የተፈቀዱ የተወሰኑ ስፖርት ነክ ጨዋታዎችን (ጌሞችን) ብቻ የሚያካሂዱት ጨዋታ ነው፡፡
አንዳንድ ድርጅቶች በሕግ ያልተፈቀዱትን የቨርቹዋል ጨዋታዎች ከአስተዳደሩ የተሰጠ ፈቃድ ሳይኖራቸው ደረጃውን ባልጠበቀ ሱቅ ውስጥ፣ ባልተፈቀዱ አካባቢዎችና በሕግ ላልተፈቀደላቸው ሰዎች በሕገወጥ መንገድ እያጫወቱ መሆኑን ብሔራዊ ሎተሪ አስተዳደር አስታውቋል፡፡
የብሔራዊ ሎተሪ አስተዳደር በተሻሻለው የስፖርት ውርርድ ጨዋታ መመርያ ማንኛውም የስፖርት ውርርድ አጫዋች ድርጅት የራሱ የሆነ ደረጃውን የጠበቀ ቢሮ ሊኖረው እንደሚገባ፣ ከትምህርትና ከሃይማኖት ተቋማት 500 ሜትር ርቀት ላይ ሊከፈት እንደሚገባው፣ መጠጥ ቤቶች አካባቢ እንዳይቋቋም፣ እንዲሁም ዕድሜያቸው ከ21 ዓመት በታች የሆነና የትምህርት ቤት ዩኒፎርም የለበሱ ተማሪዎችን ማጫወትን እንደሚከልክል የገለጹት የሕዝብ ግንኙነት ዳይሬክተሩ፣ የተወሰደው ዕርምጃም ይህንን መሠረት ያደረገ መሆኑን አስረድተዋል፡፡
እንደ አቶ ቴዎድሮስ ገለጻ፣ የቨርቹዋል ጨዋታም ሆነ ሌሎች ውርርዶች ከአስተዳደሩ ሕጋዊ ፈቃድ ሳያገኙ ማጫወት፣ የሚሠሩበትን ቅርንጫፍ ለአስተዳደሩ አስቀድመው ሳያሳውቁና ደረጃውን የጠበቀ መሆኑ ሳይረጋገጥ መሥራት፣ በሕግ የተከለከሉ አካባቢዎች ላይ ቅርንጫፍ መክፈት፣ በሕግ ያልተፈቀዱ ጨዋታዎችን ማካሄድ፣ ዕድሜያቸው ከ21 ዓመት በታች የሆኑ ወጣቶችን ማጫወት፣ ለተወራራጆች ሕጋዊ ደረሰኝ ሳይቆርጡ ገንዘብ መቀበል፣ ለውርርዱ አሸናፊዎች ያለ ምንም ውጣ ውረድ ክፍያ አለመፈጸም ሕገወጥ በመሆኑ በሕገወጥ ድርጊቱ የተሰማሩ ግለሰቦች በአስቸኳይ የከፈቱትን ቅርንጫፍ ሊዘጉ ይገባቸዋል፡፡
በብሔራዊ ሎተሪ አስተዳደር ማቋቋሚያ ደንብ መሠረት ሕገወጥ ሎተሪ የሚያካሂድ ግለሰብ፣ ከሦስት እስከ አምስት ዓመት የሚያስቀጣ እስርና ከ50 እስከ 100 ሺሕ ብር ቅጣት የሚስቀጣ መሆኑ ተገልጿል፡፡
ሪፖርተር በሃያ ሁለትና በባልደራስ አካባቢ ባደረገው ምልከታ ደረጃውን ባልጠበቀና በጣም አነስተኛ በሆነ ሱቅ ውስጥ፣ በአንድ የቨርቸዋል ጌም ማጫወቻ ኮምፒዩተር (ዴስክቶፕ) ብቻ በርካታ ወጣቶችና 18 ዓመት ያልሞላቸው ታዳጊ ልጆችን መመልከት ተችሏል፡፡
አነስተኛ ሱቅ በትንሽ ብር በመከራየት የማጫወቻ ኮምፒዩተር በመግዛትና በላዩ ላይ ሶፍትዌሮችን በመጫን የሚዘወተረው ይህ ውድድር፣ በተለይም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በተለያዩ አካባቢዎች መንሰራፋቱን ሪፖርተር ያነጋገራቸው ወጣቶች አስረድተዋል፡፡ በጉዳዩ ላይ የስፖርት ውርርድ ማኅበር አመራሮችን ለማነጋገር የተደረገው ጥረት አልተሳካም፡፡