Wednesday, September 27, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ዓለምየሱዳንን የፖለቲካ ቀውስ ይፈታል የተባለው የሱዳን ጄኔራሎችና የፖለቲካ ፓርቲዎች ስምምነት

የሱዳንን የፖለቲካ ቀውስ ይፈታል የተባለው የሱዳን ጄኔራሎችና የፖለቲካ ፓርቲዎች ስምምነት

ቀን:

የሱዳን የጦር መኮንኖችና የፖለቲካ ፓርቲዎች ለሁለት ዓመታት የሚቆይ ሲቪል የሽግግር መንግሥት ለመመሥረት ከስምምነት ላይ ደርሰዋል፡፡

ይህ በሱዳን የሲቪል መንግሥት ለመመሥረት መንገድ ይጠርጋል የተባለው ስምምነት፣ ዝርዝር መረጃዎቹ ይፋ ባይሆኑም፣ በሱዳን ላለፉት አራት ዓመታት የተከሰተውን የፖለቲካ ቀውስ ለማረጋጋት ያስችላል የሚል እምነት አሳድሯል፡፡

የሱዳን የቀድሞ ፕሬዚዳንት ኦማር አልበሽር እ.ኤ.አ. በ2019 በአመፅ ከሥልጣን ከወረዱ በኋላ፣ የመከላከያና የሲቪል መሪዎች ‹‹የነፃነትና የለውጥ ኃይል›› የሚል ጥምረት ፈጥረው የሽግግር መንግሥት መሥርተው የነበረ ቢሆንም፣ ሊዘልቅ አልቻለም ነበር፡፡

የሽግግር መንግሥቱ ጠቅላይ ሚኒስትር አብደላ ሃምዶክ ላይ መፈንቅለ መንግሥት ያካሄደውና በመከላከያ ኤታማዦር ሹሙ አብዱል ፈታህ አል ቡርሃን የተመራው ጦር ለሱዳን ሰላምን ሊያሰፍን አልቻለምም ነበር፡፡

ፕሬዚዳንት አልበሽር ከሥልጣን ከተወገዱ በኋላ የሲቪልና ወታደራዊ አስተዳደር ሊግባቡ ባለመቻላቸውም ሕዝቡ በአልበሽር አሊያም በሲቪል አስተዳደር አቀንቃኝነት ተከፋፍሎ የሱዳንን ፖለቲካ ሲዘውረው ቆይቷል፡፡

የተደረሱ ስምምነቶችም አንዴ ሲተገበሩ በሌላ ጊዜ ሲሻሩ ቆይተዋል፡፡ ይህ ደግሞ አሁንም አዲስ ስምምነት ተደርጎ በሱዳን ሰላም እንዳይሰፍን ምክንያት ሆኗል፡፡

አል በሽር ከሥልጣን ከተሰናበቱ በኋላ በጥምርም ሆነ በተናጠል ሱዳንን ሲያስተዳድር የነበረውን መከላከያ የሚመሩት አል ቡርሃን፣ ከሲቪል የፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር የሲቪል መንግሥት ሥልጣኑን በሚቆጣጠርበት ሁኔታ ላይ ከስምምነት ቢደርሱም፣ የዴሞክራሲ አቀንቃኝ ናቸው የተባሉ ሱዳናውያን ስምምነቱን ነቅፈው ተቃውሞ ሠልፍ ወጥተዋል፡፡

‹‹ከዚህ ቀደም የነበረው እምነት ተሰብሯል፡፡ ወታደራዊ ክፍሉ ድጋሚ ወደ ሥልጣን ይመጣል›› ሲሉም በመከላከያ አመራሩ ላይ እምነት እንደሌላቸው መግለጻቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡

በፕሬዚዳንቱ ቤተ መንግሥት የመላከያው መሪ ጄኔራል አልቡርሃንና የፖለቲካ ፓርቲዎች ከስምምነት ደርሰው ደስታቸውን ሲገልጹ፣ ካርቱም ደግሞ ወጣት ሴቶችና ወንዶች በብዛት የተሳተፉበት ተቃውሞን አስተናግዳለች፡፡

‹‹ትልቁ ችግር የመፈንቅለ መንግሥቱ መሪ የነበሩት አል ቡርሃንና ምክትላቸው አሁንም በሥልጣን ላይ ናቸው፡፡ ሰዎች ተገድለዋል፣ ተጎድተዋል፣ በመቃወማቸው ብቻ ታስረዋል፡፡ አሁን ደግሞ ይህን ያደረጉ ባለሥልጣናት ያለምንም ተጠያቂነት እየኖሩ ነው፤›› ብለዋል፡፡

ለሁለት ዓመታት የሚቆይ የሲቪል ሽግግር መንግሥት ከማቋቋም ባለፈም፣ መከላከያው የደኅንነትና የመከላከያ ፖርትፎሊዮን በሲቪል የሽግግር መንግሥቱ ለሚመጣው ጠቅላይ ሚኒስትር እንደሚያስረክብ ከስምምነት ተደርሷል፡፡

ነገር ግን ባለፉት አራት ዓመታት ተቃውሞ ሠልፍ ወጥተው የተገደሉ በርካታ ሲቪሎች ፍትህ አለማግኘት፣ በ2020 መከላከያው ከተለያዩ ፓርቲዎች ጋር ስምምነት ሲያደርግ መከላከያውን ይደግፉ የነበረ ታጣቂ ቡድን የስምምነቱ አካል የነበረ መሆኑና አሁን የሲቪል አስተዳደር ሲመጣ በምን መንገድ እንደሚስተናገድ አለመገለጹና መከላከያው አብላጫ ድምፅ በመያዝ የሲቪል መንግሥቱን ሐሳብ የሚያስቀይርበት አሠራር የነበረ መሆኑ፣ ለሲቪል መሪዎችንና ለአስተዳደሩ ፈተና ሊሆኑ እንደሚችሉም ተገምቷል፡፡

የነፃነትና የለውጥ ኃይል ፓርቲ ቃል አቀባይ አል ዋቲቅ አል ባሪር እንደሚሉት ግን፣ የስምምነቱ ዓላማ ሙሉ የሲቪል አስተዳደር መመሥረት በመሆኑ፣ ነፃ የፖለቲካ ምኅዳርና ሰፊ የፖለቲካ ተሳትፎ ያለበት መንግሥት ለመመሥረት ያስችላል፡፡

ኅዳር 26 ቀን 2015 ዓ.ም. ከተደረገው የመጀመርያ ስምምነት በተጨማሪ ሌላ የመጨረሻ ስምምነት የሚፈረም ቢሆንም፣ ጊዜው አልተገለጸም፡፡

በዚህ ወር ማብቂያ ሱዳንን ለ30 ዓመታት ያህል የገዙት አል በሽር ከሥልጣን በአመፅ ከተወገዱ አራት ዓመት ይሆናቸዋል፡፡ እሳቸው ከሥልጣን ከተወገዱ በኋላ ዴሞክራሲያዊ ለውጥ ይመጣ ዘንድ በርካታ ተቃውሞዎች ተደርገዋል፡፡

ይህ ተቃውሞ ያበቃና የሲቪል አስተዳደር የሱዳንን መንግሥት ይመራ ዘንድም የአፍሪካ ኅብረት፣ የዓረብ አገሮችና የምዕራባውያን መንግሥታት በሁለቱም ተከራካሪ ወገኖች በኩል ከስምምነት እንዲደርስ ጫና ማድረጋቸው ተዘግቧል፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

የአማራ ክልል ወቅታዊ ሁኔታ

እሑድ ጠዋት መስከረም 13 ቀን 2016 ዓ.ም. የፋኖ ታጣቂዎች...

ብሔራዊ ባንክ ለተመረጡ አልሚዎች የውጭ አካውንት እንዲከፍቱ ለመጀመሪያ ጊዜ የፈቀደበት መመርያና ዝርዝሮቹ

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የውጭ ምንዛሪ አጠቃቀምንና ተያያዥነት ያላቸው ጉዳዮችን...

እነ ሰበብ ደርዳሪዎች!

ከሜክሲኮ ወደ ዓለም ባንክ ልንጓዝ ነው። ሾፌርና ወያላ ጎማ...