በእውቀቱ ሥዩም
ሌሊቱ ተሽሮ፤ ጀንበር ዳግም ነግሳ
ያንሶላ መግነዜን፥ በጥሼ ስነሳ
አንዲት የንጋት ወፍ ፥ መስኮቴ ላይ ቆማ
እንዲህ ትለኛለች ፤ በሚያስገርም ዜማ፥
“እንባህን ቆጥበው ፥ በየጥጉ አትዝራው
መከረኛው እንጂ፤ አያልቅም መከራው”
ዕድሜ ሲገሰግስ
አብሬው ገስግሼ
ከዚህ ዓለም ድግስ
ከፍዳው ጠግቤ፥ ከተድላው ቀምሼ
ለኑሮ እጅ ሰጠሁ፤ ከጣየ ተስማማሁ፥
ጠቢባንን ትቼ፤ የወፍ ምክር ሰማሁ፤
እንባየን ቆጥቤ፤ ሳቄን ላበረክት
ወደ ጌጥ ቀየርሁት፤ የቁስሌን ምልክት::