የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት ወጪ አስተዳድርና ቁጥጥር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ፣ በምክር ቤቱ በሚደረግ የኦዲት ባለድርሻ አካላት መድረክ፣ በተደጋጋሚ የማይገኙ የተቋማት ኃላፊዎች፣ ፓርላማው የሚያደርገውን ጥሪ አክብረው እንዲገኙ አሳሰበ፡፡
ቋሚ ኮሚቴው በዓመት ውስጥ በሚያደርጋቸው ከሦስት የማይበልጡ የስብሰባና የግምገማ መድረኮች ላይ የመንግሥት አስፈጻሚ አካላት አለመገኘት ሊታሰብበት እንደሚገባ የገለጹት፣ የኮሚቴው ሰብሳቢ አቶ ክርስቲያን ታደለ ናቸው፡፡
የመንግሥት ወጪ አስተዳድርና ቁጥጥር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የ2014 በጀት ዓመት የኦዲት ባለድርሻ አካላትን የዕቅድ አፈጻጸም ሪፖርትና የ2015 በጀት ዓመት የኦዲት ባለድርሻ አካላት ፎረም ዕቅድ፣ ሰኞ ኅዳር 26 ቀን 2015 ዓ.ም. ገምግሟል፡፡
በዚህ ግምገማ ወቅት ከአጠቃላይ አስፈጻሚ አካላት ቁጥራቸው በርከት ያሉ የሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶች ከፍተኛ አስፈጻሚዎች እንደሚገኙ ይጠበቅ የነበረ ቢሆንም፣ የፌደራል ዋና ኦዲተር ወ/ሮ መሠረት ዳምጤን ጨምሮ የተገኙት ከፍተኛ የመንግሥት ኃላፊዎች የትምህርት ሚኒስትር ደኤታ ሳሙዔል ክፍሌ (ዶ/ር)፣ የፍትሕ ሚኒስቴር ደኤታ አቶ ፍቃዱ ፀጋ እንዲሁም የፕላንና ልማት ሚኒስትር ደኤታ ጥሩማር አባተ ብቻ ናቸው፡፡
አቶ ክርስቲያን፣ ‹‹በዚህ መድረክ ለሚኒስትሮች መገኘት ቀላል ነገር ነው፡፡ የግለሰብ ሆቴሎችን ለመመረቅ ብዙ ሚኒስትሮች ሲሄዱ እናስታውሳለን፡፡ የአገሪቱ ሕዝብ የልዕልና መገለጫ የሆነው ምክር ቤት ሲጠራ በመድረክ መገኘት መብትም ግዴታም ነው፡፡ በመሆኑም በዚህ መድረክ የተገኛችሁ ኃላፊዎች በጥብቅ እንድትነግሩልን እንፈልጋለን፤›› በማለት መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡
የአስፈጻሚ ተቋማት የበላይ ኃላፊዎች እንዲገኙ የተፈለገበት ምክንያት፣ አቅጣጫዎችን በበላይነት በመያዝ በሚኒስትሮች ምክር ቤት በሚደረጉ ስብሰባዎች ላይ በባለቤትነት እንዲሠሩ ለማድረግና ሥልጣኑ ከሰጣቸው ወንበር የሚመነጭ አቅም ስላለ እንጂ፣ የተለየ የግለሰብም ሆነ የምርጫ ጉዳይ አለመሆኑን አስረድተዋል፡፡
በመሆኑም ሚኒስትሮችና ኃላፊዎች በእዚህ መድረክ ላይ መገኘታቸው ለእነሱም ሆነ ለፓርላማውም ክብር በመሆኑ፣ ስለዚህ ለሥራው ሲባል እንዲገኙ ‹‹አደራ›› ብለዋል፡፡
በተመሳሳይ የኦዲት ተደራጊ ተቋማት የበላይ የሥራ ኃላፊዎች በምክር ቤቱ በሚከናወኑ መድረኮች እንዲገኙ በተደጋጋሚ ቢጠየቅም፣ እየተገኙ አለመሆናቸውን የቋሚ ኮሚቴው አባል አቶ እንድሪስ አህመድ አስረድተዋል፡፡
የበላይ ኃላፊዎች አለመገኘት ሊታረም እንደሚገባ የጠየቁት የቋሚ ኮቴው አባል፣ ኃላፊዎች በውይይት መድረኮች ተገኝተው የሚሰጡ አቅጣጫዎችን መቀበል እንዳለባቸው አሳስበዋል፡፡ ‹‹ይህ የተከበረ ምክር ቤት ነው፣ ምክር ቤቱ የሚያስቀምጠውን አቅጣጫ መስማት አለባቸው፡፡ ምክር ቤቱ ነው የሾማቸው፣ ስለዚህ እዚህ መድረክ ተገኝተው ሐሳቡን ሰምተው የጋራ ምክክር በማድረግ በቀጣይ የሚሠሩትን ሥራ ውጤታማ ለማድረግ የሚረዳ እንቅስቃሴ ላይ መሳተፍ አለባቸው፤›› ብለዋል፡፡
ገዳዩ በተደጋጋሚ መልስ ሊያገኝ ባለመቻሉ ቋሚ ኮሚቴው ቁርጠኛና ጠበቅ ያለ ዕርምጃ ሊወሰድ እንደሚገባ አቶ እንድሪስ ጠይቀዋል፡፡
የበላይ ኃላፊዎች በመድረኩ ካለመገኘታቸውም በተጨማሪ የተወሰኑት ባስገቡት ዕቅድ መሠረት ሥራቸውን አከናውነው ሪፖርት አለመላካቸው፣ የተገኘባቸውን የኦዲት ግኝት መሠረት አድርገው ማሻሻያ አለማድረጋቸውና መሰል ጉዳዮች ተጠቅሰዋል፡፡