በሰሜኑ ጦርነት ምክንያት 112 ቅርንጫፎቹ ከሥራ ውጭ በመሆናቸው የ2013ሒሳብ ዓመት ትርፉ አሽቆልቁሎ የበረው ወጋገን ባንክ፣ በ2014 ሒሳብ ዓመት 572 ሚሊዮን ብር ማትረፉን ዛሬ ህዳር 24 ቀን 2015 ዓም አስታወቀ።
ባንኩ የሒሳብ ዓመቱን አፈፃጸም አስመልክቶ ባወጣው መግለጫ እንደገለጸው፣ በ2013 ሒሳብ ዓመት ከነበረበት ዝቅተኛ አፈፃጸም ወጥቶ፣ በ2014 ሒሳብ ዓመት ያገኘው የ572 ሚሊዮን ብር ትርፍ ከ2013 ሒሳብ ዓመት ጋር ሲነፃጸር የ196 በመቶ ወይም 379 ሚሊዮን ብር ብልጫ አለው። የባንኩ ትርፍ ምጣኔ ለባለድርሻወች የሚከፈለውን የትርፍ መጠን ከፍ እንዳደረገው ተገልጿል።
በ2013 ሒሳብ ዓመት የአንድ አክሲዮን ያስገኘው የትርፍ መጠን 4.2 በመቶ የነበረ ቢሆንም በ2014 ሒሳብ ዓመት ግን 16.6 በመቶ ማደግ መቻሉ ተገልጿል። ባንኩ ባካሄደው አስቸኳይ ጠቅላላ ጉባኤ፣ የባንኩ ካፒታል 20 ቢሊዮን ብር እንዲሆን በባንኩ ዳይሬክተሮች ቦርድ የቀረበውን ሀሳብ በሙሉ ድምጽ አጽድቋል።
ወጋገን ባንክ አሁን ያለው ካፒታል የተፈረመ አምስት ቢሊዮን ብር ሲሆን፣የተከፈለ ካፒታሉ 3.4 ቢሊዮን ብር ነው። ተጨማሪ ያጸደቀው 15 ቢሊዮን ብር ካፒታል በአምስት ዓመታት የሚከፈል መሆኑም ታውቋል።