በኢትዮጵያ ለአካለ መጠን ያልደረሱ ሕፃናትን ለጦርነትና ለውትድርና የመለመሉ አካላትን ለሕግ የማቅረብ ሥራ ችላ መባሉን የሕግ ባለሙያዎች ለሰብዓዊ መብቶች ድርጅት አስታወቀ፡፡
ድርጅቱ ኅዳር 22 ቀን 2015 ዓ.ም. ባዘጋጀው መድረክ ላይ ኢትዮጵያን ጨምሮ በዓለም ደረጃ የተደረጉ የእርስ በርስ ጦርነት ላይ ቁጥራቸው በርከት ያሉ ሕፃናት እንደተሳተፉም ተገልጿል፡፡
በመድረኩ ጥናት ያቀረቡት የሕግ ባለሙያና አማካሪ ሽመልስ ሲሳይ (ዶ/ር) እንደተናገሩት፣ ከዚህ ቀደም በኢትዮጵያ ለውትድርና ለመመልመል ዕድሜ ሳይሆን አካላዊ ሁኔታን ማየት በቂ ተደርጎ ይወሰድ ነበር፡፡
በኢትዮጵያም በልጅነት ወደ ጦርነት መግባት እንደ ጀግንነት ይቆጠር እንደነበር ያወሱት ሽመልስ (ዶ/ር)፣ በዚህም ሳቢያ በጦርነቱ ቀጥተኛ ተሳትፎ የሚያሳዩ መኖራቸውን አስረድተዋል፡፡
ሆኖም በሕግና በክልከላ ደረጃ፣ የኢትዮጵያ የወንጀል ሕግ ከ18 ዓመት በታች የሆናቸውን ሕፃናት ለወታደራዊ አገልግሎት መመልመል ተጠያቂ እንደሚያደርግ ተናግረዋል፡፡
ሕፃናትን ለውትድርና የመለመለና በቀጥታ ያሳተፈ አካል ቅጣቱ ከአምስት እስከ 20 ዓመታት ፅኑ እስራት፣ የዕድሜ ልክ እንዲሁም የሞት ቅጣት መሆኑንም በሕጉ እንደተቀመጠ አስረድተዋል፡፡
ይሁን እንጂ ትልቁ ችግር በተለያዩ የኢትዮጵያ አካባቢዎች የሚታየው የሕፃናት ወታደራዊ ተሳትፎ ሕገወጥ ታጣቂ ቡድኖች በሚባሉት በመሆኑ ችግሩን ውስብስብና የጎላ እንደሚያደርገውና ለተጠያቂነት አመቺ እንዳልሆነ ተናግረዋል፡፡
ድርጊቱ በወንጀል የሚያስጠይቅ ቢሆንም፣ እስካሁን ለድርጊቶቹ ጥፋተኛ ተደርጎ ዕርምጃ የተወሰደበት እንደሌለም በመደበኛው ፍርድ ቤትም የቅጣት ብይን ተሰምቶ እንደማይታወቅ አክለዋል፡፡
ከጉዳዩ ስፋትና አሳሳቢነት አንፃር ቦታ ያልተሰጠው መሆኑንና ወደፊት መንግሥትና የፍትሕ አካላት ትኩረት ሰጥተው ሊሠሩበት እንደሚገባም ተናግረዋል፡፡
ዓለም አቀፍ መረጃዎችን ዋቢ አድርገው የተናገሩት የሕግ ባለሙያው፣ በዓመት በዓለም አቀፍ ደረጃ 300 ሺሕ ሕፃናት ለውትድርና ይመለመላሉ፡፡