በአሁኑ ወቅት ግንባታቸው እየተጠናቀቁ ያሉም ሆኑ ቀደም ሲልም በተደረገ ማጣራት ባለቤት አልባ ሆነው የተገኙ የጋራ መኖሪያ ቤቶች፣ በቅድሚያ ዕድል መብት እንዲተላለፉላቸው የ1997 ዓ.ም. የጋራ መኖሪያ ቤት ተመዝጋቢዎች ጠየቁ፡፡
በአዲስ አበባ የቤት ልማት ፕሮግራም ከተጀመረ 18 ዓመታት እንደተቆጠሩ የሚናገሩት የቤት ተመዝጋቢዎች፣ በተለያዩ ጊዜያት በወጡ ዕጣዎች ዕድለኛ ያልሆኑበትን ምክንያት በየጊዜው ለተሾሙት የቤቶች ልማት ቢሮ ኃላፊዎች አቤቱታ ቢቀርብም፣ ‹‹ተስፋ ከመስጠት ውጭ ጆሮ ዳባ ልበስ ብለውናል፤›› ይላሉ፡፡
በየጊዜው ለአርሶ አደር ልጆች፣ ለፖለቲካ ሹመኞች፣ እንዲሁም ለተለያዩ ግለሰቦች አስተዳደሩ ቤት ሲሰጥ እየታዘብን ነው የሚሉት የቤት ተመዝጋቢዎች፣ ከ18 ዓመታት በላይ ለጠበቁ ቆጣቢዎች ጥያቄ መልስ መስጠት አልተቻለም ብለዋል፡፡
ጥያቄያቸውን ለአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት፣ ከንቲባ፣ ቤቶች ልማት ጽሕፈት ቤት፣ ለሕዝብ ዕንባ ጠባቂ ተቋም፣ ለሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽንና ለፕሬዚዳንት ጽሕፈት ቤት፣ እንዲሁም ለጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት እንዳቀረቡ የሚናገሩት የ1997 ዓ.ም. የጋራ መኖሪያ ቤት ተመዝጋቢዎች፣ በተለይም የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ‹‹ጉዳዩ ማለቅ ያለበት በከተማ አስተዳደሩ ነው›› የሚል ምላሽ መስጠቱን ተናግረዋል፡፡
በቀጣይ የከተማ አስተዳደሩ ዕጣ የማውጣት ሥነ ሥርዓት ሲያካሂድ የ1997 ዓ.ም. ተመዝጋቢዎች ለብቻቸው ነው የሚያስተናግደው? ወይስ ከ2005 ዓ.ም. ተመዝጋቢዎች ጋር በጋራ ነው የሚያወጣው? ተብሎ ለተጠየቀው ጥያቄ የቤቶች ልማትና አስተዳደር ቢሮ ኃላፊዋ ቁርጥ ያለ ምላሽ ለመስጠት እንዳልፈለጉ የቤት ተመዝጋቢዎቹ ጊዜያዊ አሰባሳቢ ኮሚቴ ተወካዮች ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ ‹‹ወደፊት ምላሻችንን እናሳውቃችኋለን›› የሚለውን መልስ ከቤቶች ልማት ቢሮ ኃላፊዋ አንደበት እንደተገለጸላቸው የቤት ተመዝጋቢዎቹ አስረድተዋል፡፡
በ1997 ዓ.ም. ተመዝግበውና ብቁ ቆጣቢ ሆነው እስካሁን ድረስ የቤት ዕድለኛ እንዳልሆኑ የሚናገሩት ተመዝጋቢዎች፣ ኅዳር 21 ቀን 2015 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ከተማ የቤቶች ልማትና አስተዳደር ኤጀንሲና በአዲስ አበባ ከተማ ማዘጋጃ ቤት ተገኝተው ጥያቄያቸውን ለማቅረብ ያደረጉት ጥረት፣ ከፀጥታ አካላት በመጣ ትዕዛዝ እንዲቆም መደረጉን ተናግረዋል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ የ14ኛው ዙር ዕጣ ሲወጣ ባደረጉት ንግግር፣ ‹‹ለዕጣ ከተዘጋጁት 25,791 ቤቶች ከ1997 ዓ.ም. ብቁና ንቁ ተመዝጋቢዎችን ሙሉ በሙሉ በመያዝ ዕጣው ለመውጣት ዝግጁ የተደረጉ ናቸው፡፡ ከዚህ በኋላ በ1997 ዓ.ም. ብቁና ንቁ ተብለው የሚጠሩ ዕጣ የሚወጣላቸው የተለየ ሁኔታ ሳያስፈልግ ሙሉ ተመዝጋቢዎች ዛሬ ይስተናገዳሉ፤›› ማለታቸውን የቤት ተመዝጋቢዎቹ በማስታወስ፣ ነገር ግን በንግግሩ የሰነቁት ተስፋ ውጤት እንዳላመጣ ገልጸዋል፡፡
የቤት ተመዝጋቢዎቹ ጥያቄ በተመለከተ ለአዲስ አበባ ከተማ የቤቶች ልማትና አስተዳደር ቢሮ ኃላፊ ወ/ሪት ያስሚን ወሃብረቢ ጥያቄ ለማቅረብ በተደጋጋሚ የተደረገው የስልክ ጥሪ ሙከራ ምላሽ አላገኘም፡፡ በሌላ በኩል የአዲስ አበባ ከተማ ኮሙዩኒኬሽን ቢሮ ኃላፊንም ለማነጋገር የተደረገው ጥረት አልተሳካም፡፡
ከዚህ ቀደም የ14ኛው ዙር ዕጣ ማውጣት ሥነ ሥርዓት ከመካሄዱ አስቀድሞ በተሰጠ መግለጫ ላይ ገለጻ ያደረጉት የአዲስ አበባ ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች፣ የከተማ አስተዳደሩ እስከ የካቲት 21 ቀን 2014 ዓ.ም. ባደረገው የመረጃ ማጣራት 24 ሺሕ ያህል የ1997 ዓ.ም. ተመዝጋቢዎች ለዕጣ አወጣጥ ሥነ ሥርዓት ብቁ የሚያደርጋቸውን እንደቆጠቡ፣ በዚህም ሙሉ በሙሉ በ14ኛው ዙር ዕጣ አወጣጥ ዝርዝር ውስጥ እንደሚካተቱ መናገራቸው ይታወሳል፡፡