የአቢሲኒያ ባንክ ዳይሬክተሮች ቦርድ የባንኩ ካፒታል በ2.5 ቢሊዮን ብር አድጎ 12.5ቢሊዮን ብር እንዲሆን ያቀረበውን ሃሳብ ጠቅላላ ጉባኤው አጸደቀ።
የትርፍ መጠኑን በ127 በመቶ ማሳደጉን የገለጸው አቢሲኒያ ባንክ፣ 13ኛ ጠቅላላ ጉባኤውን ዛሬ ህዳር 17 ቀን 2015 ዓም በኢንተር ሌግዤሪ ሆቴል ያካሄደ ሲሆን፣ ካፒታሉን ያሳደገበትን 2.5 ቢሊዮን ብር ባለአክሲዮኖቹ ባላቸው ድርሻ ግዢ እስከ ሚያዚያ 22 ቀን 2015 ዓም ድረስ እንዲፈጽሙ ጉባኤው ውሳኔ አሳልፏል።
አቢሲኒያ ባንክ የተፈረመ ካፒታሁ አሥር ቢሊዮን ብር ሲሆን፣ እስከ 2014 መጨረሻ ሒሳብ ዓመት ድረስ የተከፈለ ካፒታሉ 8.3 ቢሊዮን ብር ነበር። ባለድርሻዎች ከተፈረመው ካፒታል ውስጥ ያልከፈሉትን ካፒታል በአንድ ወር ውስጥ ከፍለው እንዲያጠናቅቁ ጉባኤው ውሳኔ ያሳለፈ ሲሆን፣አዲስ የተጨመረው የአክሲዮን ሽያጭ የሚጀመረው፣ ቀድሞ የፈረመው ካፒታል ክፍያ ከተጠናቀቀ በኋላ መሆኑንም ጉባኤው አስታውቋል።
ባንኩ ተፈርሞ ያልተከፈለ ካፒታል በአንድ ወር ውስጥ ተከፍሎ እንዲጠናቀቅና፣ የባንኩ ካፒታል በ2.5 ቢሊዮን እንዲያድግ የተወሰነበትን ምክንያት የቦርዱ አመራሮች አስረድተዋል።
የግል ንግድ ባንኮች ካፒታላቸውን በከፍተኛ ሁኔታ አሳድገዋል። በዚህም ህብረት ባንክ ከአምስት ቢሊዮን ወደ 20ቢሊዮን፣ዘመን ባንክ ከአምስት ቢሊዮን ወደ 15 ቢሊዮንና አዋሽ ባንክ ከ 12 ቢሊዮን ወደ 55 ቢሊዮን ብር አሳድገዋል። አቢሲኒያ ባንክም ከአሥር ቢሊዮን ብር ወደ 12.5 ቢሊዮን ብር ያሳደገ ቢሆንም ካፒታሉን ከሁም ባነሰ ሁኔታ ያሳደገ ቢሆንም ምክንያቱንም ቦርዱ አብራርቷል።