በኢትዮጵያ የሁለት ቀናት ቆይታ በማድረግ የተለያዩ አካላትን ያነጋገሩት ከዩክሬን የመጡ የሲቪክ ማኅበራት ተወካዮች፣ ኢትዮጵያ በዓለም አቀፉ መድረክ ላይ አገራቸውን እንድትደግፍ ጥሪ አቀረቡ፡፡ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት በተለያዩ መድረኮች የዩክሬንና የሩሲያን ጦርነት በተመለከተ ለሚያስተላልፏቸው የውሳኔ ሐሳቦች ላይ ኢትዮጵያ ዩክሬንን በመደገፍ ድምጿን እንድትሰጥ የማኅበራቱ ተወካዮች ጥሪ አስተላልፈዋል፡፡
ከኬንያ ናይሮቢ በማስቀጠል አዲስ አበባን ቀጣይ መዳረሻቸው ያደረጉት የማኅበራቶቹ ተወካዮች የጎበኟቸው አገሮች፣ ዩክሬንን እንዲደግፉና አገራቸው ያለችበትን ሁኔታ የማስረዳት ተልዕኮ ይዘው እንዲመጡ ተናግረዋል፡፡ ቡድኑ የዩክሬን ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያንን፣ በቅርቡ ኖቤል የተሸለመው በዩክሬን መቀመጫውን ያደረገው ‹‹ሴንተር ፎር ሲቪክ ላይበርቲስ›› (Center for Civic Liberties)፣ እንዲሁም የዩክሬን ንግድና ኢንዱስትሪ ምክር ቤትን በመወከል ሦስት ተሳታፊዎች የያዘ ሲሆን፣ በተጨማሪም የኪዮቭ ብሔራዊ ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካ መምህርና የተለያዩ ተቋማት አባልና ኃላፊ ኦሌክሲ ሔራንን (ዶ/ር) ይዟል፡፡
በኢትዮጵያም ጉብኝትና ምክክር ያደረገው ይህ ቡድን፣ ሐሙስ ኅዳር 15 ቀን 2015 ዓ.ም. በራዲሰን ብሉ ሆቴል መግለጫ የሰጠ ሲሆን፣ በመግለጫውም ምዕራባውያን አገራቸውን በመሣሪያ እንዲደግፉ እ.ኤ.አ. ከ2014 ጀምሮ ይወተውቱ እንደነበርና አሁን ከረፈደ እየደገፏቸው እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ ሆኖም ግን ሁሉም አገሮች በመሣሪያና በቁሳቁስ ባይደግፏቸውም፣ የምርጫና በመሰል በዓለም አቀፉ መድረክ የሚደረጉ ድጋፎችን በእጅጉ እንደሚሹ ተናግረዋል፡፡ የጉዟቸው ዋነኛ ዓላማም ይህን ለማስተባበር ሲሆን፣ የተለዩ ቡድኖች ከወር በፊት በምዕራብ አፍሪካ አገሮች ናይጄሪያና ጋናም ተጉዘው ነበር፡፡
‹‹ኢትዮጵያ ሩሲያን ጦርነት እንድታቆም የማዘዝ አቅም ላይኖራት እንደሚችል እንረዳለን፡፡ ነገር ግን በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት መድረክ ላይ ሁሉም ድምፆች ዋጋ አላቸው፡፡ ኢትዮጵያ የዩክሬንን የግዛት አንድነት የሚያስከብሩ ውሳኔዎችን እንድትደግፍ ብቻ ነው የምንፈልገው፤›› ሲሉ የቡድኑ አባል ኦሌክሲ (ዶ/ር) ተናግረዋል፡፡
ሆኖም ግን በተመሳሳይ ሁኔታ ኢትዮጵያ በዓለም አቀፉ መድረክ ድጋፍ በምትፈልግበት ጊዜ ዩክሬን ብዙም በድጋፉ ስትሳተፍ አይታይም፡፡ ባለፈው ዓመት የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ሰብዓዊ መብቶች ካውንስል ዓለም አቀፉ የባለሙያዎች ኮሚሽን ለማቋቋምና ኢትዮጵያ መጥተው ተፈጠሩ የሚባሉት የሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶችን እንዲያጣሩ አገሮች ድምፅ በሰጡበት ጊዜ ዩክሬን ስትፈቅድ ሩሲያ ተቃውማ ነበር፡፡
ምዕራባውያን እ.ኤ.አ. ከ2014 ጀምሮ አገራቸውን በሐሳብና የመተባበር ጥረት ቢያደርጉም፣ እንደ ማዕቀብና መሰል ድርጊቶችን ጦርነቱ እስኪጀምር ድረስ የማድረግ አዝማሚያ እንዳልነበራቸው ኦሌክሲ (ዶ/ር) ገልጸዋል፡፡ ‹‹እንዲያውም እንደ ጀርመን ዓይነት የአውሮፓ አገሮች ሩሲያ ላይ ማዕቀብ ሊጥሉ አይደለም፣ የበለጠ ቢዝነስ ሲሠሩ ነበር፤›› ሲሉ ተናግረዋል፡፡
ጦርነቱ ባስከተለው ዓለም አቀፍ የምግብ አቅርቦት ቀውስ እንደ ምሥራቅ አፍሪካ ዓይነት አገሮች እጅጉን መጎዳታቸውን እንደሚረዱ የገለጹት የቡድኑ ተወካዮች፣ ይህንን ጦርነት ማቆም ከዩክሬንም አልፎ ለእንደ ኢትዮጵያ ዓይነት አገሮች ትልቅ ጥቅም እንዳለው ተናግረዋል፡፡