በኮንጎ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ትጥቅ አንግበው መዋጋት ከጀመሩ አሥር ዓመታት በላይ ያስቆጠሩት የኤም 23 ተዋጊዎች፣ ዘንድሮ ከጥቅምት ወዲህ ዳግም ተጠናክረው በከፈቱት ጥቃት በርካቶችን እየገደሉና እያፈናቀሉ ነው፡፡
እ.ኤ.አ. በ2013 በአገሪቱ መከላከያ ከባድ ምት ተሰንዝሮባቸው ወደ ጎረቤት ሩዋንዳና ኡጋንዳ መሽገው የከረሙት ተዋጊዎች፣ ዘንድሮ የከፈቱት አዲስ ጦርነት፣ በምሥራቅ የአገሪቱ ክፍል ያሉ ነዋሪዎችን ከማፈናቀሉም በተጨማሪ የኮንጎ መከላከያና ቡድኑ በሚያደርጉት ጦርነት ምክንያት የኮንጎ ቁልፍ ከተማ የሆነችው ጎማ ዝግ ሆናለች፡፡
በኡጋንዳና ሩዋንዳ ይደገፋል የሚባለው የኤም 23 ታጣቂ ቡድን፣ በቅርቡ አዲስ ጦርነት ከጀመረ ወዲህ የአገሪቱ መከላከያ ተቆጣጥሯቸው ከነበሩ ከተሞች እየሸሸ መውጣቱ ደግሞ በተለያዩ ከተሞች የሚገኙ ነዋሪዎችን ሥጋት ላይ መጣሉም በተለያዩ ዓለም አቀፍ ሚዲያዎች ተዘግቧል፡፡
ጦርነቱ ባገረሸበት የአገሪቱ ምሥራቃዊ ክፍል በሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎች እየተሰደዱ ጉዳት የደረሰባቸው ዜጎች ደግሞ በዓለም አቀፍ ሰብዓዊ ድጋፍ ሰጪ ድርጅቶች መጠለያ ጣቢያዎች ውስጥና ውጭ በሚገኙ ሆስፒታሎች እየታከሙም ነው ተብሏል፡፡
በአብዛኛው የኮንጎ ቱትሲ ጎሳ አባላት ናቸው የሚባሉት የኤም 23 ተዋጊዎች ከዓመታት ዝምታ በኋላ እ.ኤ.አ. በ2021 አንዳንድ የኮንጎ ምሥራቃዊ ከተማዎችን መቆጣጠር ቢጀምርም፣ ከአገሪቱ መንግሥት ጋር ከባድ ጦርነት ውስጥ ከገባ የወራት ዕድሜ እንኳን አላስቆጠረም፡፡
ከሩዋንዳ ፕሬዚዳንት ፖል ካጋሜ ጎሳ የሚመደቡትና የኮንጎ ቱትሲ ጎሳን መብት እናስጠብቃለን በማለት እ.ኤ.አ. በ2012 ጦር ያነሱት የኤም 23 ታጣቂዎች በአሥር ሺዎች የሚቆጠሩ የኮንጎ ዜጎች እንዲፈናቀሉና እንዲሞቱ ምክንያት ሆነዋል፡፡
የሩዋንዳ ወታደሮች በኮንጎ ገብተው ጥቃት ፈጽመዋል፣ የሩዋንዳ መንግሥት የኤም 23 ታጣቂዎችንም በመሣሪያና በሌሎች ቁሳቁሶች ይደግፋል ሲል የተባበሩት መንግሥታት የባለሙያዎች ቡድን ቢያሳውቅም፣ ከሩዋንዳ መንግሥት ተቀባይነት አላገኘም፡፡ ሆኖም ኮንጎ ለዓመታት ሩዋንዳንና ኡጋንዳን ስትወነጅል ቆይታለች፡፡
ሩዋንዳ በኮንጎ የውክልና ጦርነት እያካሄደች ነው ስትልም ትከሳለች፡፡ የኤም 23 ታጣቂ ቡድን ‹‹ጦርነቱን እኛ አልጀመርንም፣ የጀመሩት የኮንጎ ወታደሮች ናቸው ኃላፊነት አንወስድም፤›› ቢሉም፣ ተመድን ጨመሮ ሰብዓዊ ድጋፍ አድራጊዎች ኤም 23 እና ሩዋንዳን ይወነጅላሉ፡፡
የጦርነቱ ዳግም ማገርሸት፣ ጦርነቱ ለሚካሄድባት ኮንጎ ብቻ ሳይሆን ለምሥራቅ አፍሪካ አገሮችም ሥጋት ሆኗል፡፡
የኬንያ ፕሬዚዳንት ዊልያም ሩቶ የምሥራቅ አፍሪካ ማኅበረሰብ ወታደሮች በምሥራቅ ኮንጎ ሰላም ለማስከበር ይሠራሉ ሲሉ መናገራቸውን አፍሪካ ኒውስ ዘግቧል፡፡
በኮንጎ ኪንሻሳ የአንድ ቀን የሥራ ጉብኝት ያደረጉትና ከኮንጎ ፕሬዚዳንት ፊሊክስ ታሺኬዲ ጋር የመከሩት ፕሬዚዳንት ሩቶ፣ ‹‹በቀጣናው የተመድ ሰላም አስከባሪ ኃይል ቢኖርም፣ ሰላም ሊያመጣ አልቻለም፡፡ የምሥራቅ አፍሪካ ወታደሮች የተሻለ ሰላም ሊያመጡ ይችላሉ፤›› ብለዋል፡፡
ኬንያ ለኮንጎ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ መንግሥት 900 ወታደሮችን ለሰላም ማስከበር የላከች ሲሆን፣ በኤም 23 እና በኮንጎ መንግሥት መካከል የተጀመረው ጦርነት በሰላም እንዲፈታም እየሠራች ነው፡፡
የተለያዩ ታጣቂዎች የሚያምሷት ኮንጎ ሰላሟን ካጣች 30 ዓመታት ያህል አስቆጥራለች፡፡ ከታጣቂዎቹ ደግሞ በርካታ ቦታዎችን ተቆጣጥሯል የሚባለው ኤም 23 ቡድን ጠንካራው ነው፡፡
በቴክኖሎጂ የታገዘ ዘመናዊ መሣሪያ እንደታጠቀ የሚነገርለት ቡድን፣ የቁጥጥር ድሮን እንደሚጠቀምና በሩዋንዳ እንደሚደገፍ የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾችም ይጠቁማሉ፡፡
የኬንያ የቀድሞ ፕሬዚዳንት ኡሁሩ ኬንያታ ባለፈው ሳምንት ወደ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ አቅንተው የነበረ ሲሆን፣ በኤም 23 ቡድንና በኮንጎ መንግሥት መካከል የሰላም ንግግር እንደሚጀመር አሳውቀዋል፡፡
የአንጎላ ፕሬዚዳንት ጆአ ሎሬንሶ የኮንጎንና የሩዋንዳን ባለሥልጣናት ሲያወያዩ፣ የጊኒ ቢሳዎ ፕሬዚዳንትና የምዕራብ አፍሪካ ኢኮኖሚ ማኅበረሰብ (ኢኮዋስ) ሊቀመንበር ኡማሮ ሲስኮ ኪንሻሳና ኪጋሊ በማቅናት ሰላም በሚመጣበት መንገድ መክረዋል፡፡