Wednesday, November 29, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ማኅበራዊእየተንሰራፋ የመጣው የጡት ካንሰር በሽታ

እየተንሰራፋ የመጣው የጡት ካንሰር በሽታ

ቀን:

የዓለም ጤና ድርጅት መረጃ እንደሚያሳየው፣ በዓለም ላይ በየዓመቱ ከ19 ሚሊዮን በላይ ሰዎች በተለያየ ዓይነት የካንሰር በሽታ ይያዛሉ፡፡ ከእነዚህም ውስጥ 11.7 በመቶ የሚሆኑ ሰዎች የጡት ካንሰር በሽታ ተጠቂዎች ናቸው፡፡ ከመካከላቸውም አብዛኞቹ ስለበሽታው በቂ የሆነ ግንዛቤ የሌላቸው፣ አሊያም ደግሞ ወደ ሕክምና ተቋም ሄደው በጊዜው ክትትል ሳያደርጉ የቀሩ መሆናቸውንም መረጃው ያሳያል፡፡

ይህ የጤና ችግር ኢትዮጵያ ውስጥ ከፍተኛውን ድርሻ ይዟል፡፡ ሕክምና ላይ በሚሠሩ ድርጅቶች፣ በማኅበራዊ ሚዲያዎችና በሕክምና ተቋማት አማካይነት ስለበሽታው ግንዛቤ ቢሰጥም ችግሩ አልተፈታም፡፡ ይሁን እንጂ በዘርፉ ላይ ያሉትን ተግዳሮቶች ለመግታት የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ ጥቁር አንበሳ አጠቃላይ ስፔሻላይዝድ ሪፈራል ሆስፒታል፣ የቅዱስ ጳውሎስ ሚሌኒየም ሜዲካል ኮሌጅ፣ ጅማ ሪፈራል ሆስፒታል፣ የግል ሆስፒታሎችና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች እየሠሩ ይገኛሉ፡፡

በቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሌኒየም ሜዲካል ኮሌጅ የካንሰር ስፔሻሊስትና የካንሰር ክፍል ኃላፊ አብዱ አደም (ዶ/ር) ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ እ.ኤ.አ. በ2018 ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ከተለያዩ ተቋማት ጋር ያደረገው ጥናት፣ በኢትዮጵያ በየዓመቱ ከ72 ሺሕ በላይ ሰዎች በአዳዲስ ዓይነቶች የካንሰር በሽታዎች ይያዛሉ፡፡

ከእነዚህም የካንሰር በሽታዎች ውስጥ 33 በመቶ የሚሆኑት በጡት ካንሰር በሽታ የሚያዙ ናቸው፡፡ በየቀኑም የሕሙማን ቁጥር እየጨመረ መምጣቱን ኃላፊው አስረድተዋል፡፡ 

በኢትዮጵያ ከካንሰር በሽታዎች መካከል የመጀመርያውን ደረጃ የያዘው የጡት ካንሰር በሽታ ነው የሚሉት አብዱ (ዶ/ር)፣ አብዛኛው የማኅበረሰብ ክፍሎች ስለበሽታው በቂ ግንዛቤ ስለሌላቸው ሕመሙ በውስጣቸው ሰርስሮ ከገባ በኋላ ወደ ሕክምና ተቋም እንደሚመጡ አስረድተዋል፡፡

የጡት ካንሰር በሽታ በዓለም አቀፍ ደረጃም ሆነ በኢትዮጵያ የመጀመርያ ደረጃን እንደሚይዝ፣ በሽታውም በሁለቱም ፆታዎች ላይ የሚከሰት መሆኑን አብራርተዋል፡፡

በተለይ በሽታው የሚከሰተው በሴቶች ላይ መሆኑን ያስታወሱት ሐኪሙ፣ ምናልባትም በዓመት ውስጥ አንድ ወንድ ልጅ በበሽታው ቢያዝ፣ ከ150 በላይ የሚሆኑ ሴቶች ደግሞ የዚህ በሽታ ተጠቂ ሊሆኑ እንደሚችሉ ገልጸዋል፡፡

አብዛኛዎቹ የካንሰር በሽታዎች መነሻ ምን እንደሆነ የማይታወቅ መሆኑን፣ ነገር ግን ለካንሰር በሽታ አጋላጭ የሆኑ ነገሮች መኖራቸውንና ቁጥራቸው ከፍተኛ የሆኑ የካንሰር በሽታ ተጠቂዎችም ዕድሜያቸው ከ45 ዓመት ጀምሮ ያሉ መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡

በኢትዮጵያ በተለየ ሁኔታ አብዛኞቹ የጡት ካንሰር በሽታ ተጠቂዎች ከ20 እስከ 30 ዓመት የዕድሜ ክልል ላይ የሚገኙ መሆናቸውን፣ ይህም ‹‹ለምን ሆነ?›› የሚለውን ለመለየት በቂ ጥናት እንደሚያስፈልግ ጠቁመዋል፡፡

ባደጉት አገሮች አብዛኛውን ጊዜ በሽታው የሚከሰተው የወር አበባ ባቆሙ ሴቶች ላይና ዕድሜያቸውም ከ45 ዓመት በላይ በሆኑት ላይ እንደሆነ የተናገሩት ኃላፊው፣ በዚህም ዕድሜ ክልል ላይ የሚገኙ ሰዎች ወደ ሕክምና ተቋም በመሄድ በቂ የሆነ ክትትል ማድረግ ይኖርባቸዋል ብለዋል፡፡

የጡት ካንሰር በሽታን ለመከላከል እንደ አማራጭ ከሚታዩ ነገሮች መካከል የአኗኗር ዘይቤን ማሻሻል መሆኑን፣ በተለይም የአመጋገብ ሥርዓትን መቀየር ትልቅ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ገልጸዋል፡፡

የጡት ሴሎች ወደ ካንሰርነት እንዲለወጡ አሊያም ደግሞ ከተለወጡም በኋላ እንዲባዙ የሚያደርገው ዋነኛ ምክንያት ‹‹ኤስትሮጂን›› የሚባል ሆርሞን ሲሆን፣ ይህም ሆርሞን ሴቶች የወር አበባ ጀምረው እስከሚያቆሙበት ባለው ዕድሜ ክልል ውስጥ የሚገኝ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

ሆርሞኑ የወር አበባን ማየት ያልጀመሩ ሴቶች ልጆች ላይ፣ በእርግዝና ወቅት እንዲሁም ደግሞ የወር አበባ በሚያዩ ጊዜ የማይታይ በመሆኑ በእነዚህ ወቅት በበሽታው የመያዝ ሁኔታ ይቀንሳል ብለዋል፡፡

በሌላ በኩል በመድኃኒትም መልኩ ሆነ በሰውነት ውስጥ የሚቀበሩ ሆርሞን ያላቸው የወሊድ መከላከያዎች ለረዥም ጊዜ መጠቀም ለጡት ካንሰር በሽታ የማጋለጥ ዕድል እንደሚፈጥርና ከስንት አንድ ጊዜ በዘር ሊተላለፍ እንደሚችል አክለዋል፡፡

በኢትዮጵያ የጡት ካንሰር ሕሙማን ሕክምና የሚያገኙበት የራሱ የሆነ ማዕከል አለመኖሩና ለሕክምናውም የሚሆኑ ግብዓቶች በቂ አለመሆናቸው፣ ዘርፉ ላይ ችግር እየፈጠረ ነው፡፡

በተለያዩ ሁኔታ ውስጥ የሚገኙ የካንሰር ሕሙማን የሕክምና አገልግሎት እንዲያገኙ ለማስቻል በቂ የሕክምና ባለሙያ አለመኖሩን፣ በአገር አቀፍ ደረጃም ለጡት ካንሰር በሽታ የሕክምና አገልግሎት የሚሰጡ ሰባት የሕክምና ተቋማት ብቻ መሆናቸውና በቂ እንዳልሆኑም አስረድተዋል፡፡

ለካንሰር በሽታ ሕክምና አገልግሎት ለመስጠት የጨረር ሕክምና መስጫ መሣሪያዎች እጥረት መኖሩን፣ አብዛኛው ሕሙማንም በመድኃኒት ማስታገሻ ብቻ ስለሚቆዩ በሽታው ሊንሰራፋ ችሏል ብለዋል፡፡

70 በመቶ የሚሆኑት የጡት የካንሰር በሽታ ታካሚዎች የጨረር ሕክምና እንደሚያስፈልጋቸውና ይህም ካልሆነ በሽታው እንደ አዲስ ሊያገረሽባቸው እንደሚችል አብራርተዋል፡፡

በአሁኑ ወቅት የጨረር ሕክምና አገልግሎትን እየሰጡ የሚገኙት ጥቁር አንበሳና  ጅማ ሲሆኑ፣ በእነዚህም ሆስፒታሎች በርካታ ሕሙማን ወረፋ እንደሚጠብቁ አብዱ (ዶ/ር) ገልጸዋል፡፡

ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል በአሁኑ ወቅት በተለያዩ ችግሮች ምክንያት ይህንን አገልግሎት እየሰጠ ባለመሆኑ በርካታ ሕሙማን ችግር ውስጥ እንደሆኑ ጠቁመዋል፡፡

ለጨረር ሕክምና አገልግሎት የሚሰጡ ማሽኖችም ከተበላሹ በኋላ መልሶ መጠገን የሚችል ባለሙያ ካለመኖሩ የተነሳ፣ ከተለያዩ ቦታዎች የመጡ ሕሙማን ላልተፈለገ ወጪ እየተጋለጡ ነው፡፡

በሌላ በኩል በተለያዩ የሕክምና ተቋማት ያለው መድኃኒትና በበሽታው የተያዙ ሕሙማን ቁጥር የተመጣጠነ ባለመሆኑ፣ አብዛኛዎቹ ሕሙማን ችግር ውስጥ እየወደቁ ነው፡፡

እንደ ባለሙያው፣ በኢትዮጵያ የሚገኙ የአብዛኛዎቹ የጡት ካንሰር ሕሙማን ደረጃ ሦስትና ደረጃ አራት ማለትም ከፍተኛ የሕመም ደረጃ ላይ ይገኛሉ፡፡

በአሁኑ ወቅት በዘርፉ ላይ የሚታየውን ችግር ለመቅረፍ የቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሌኒየም ሜዲካል ኮሌጅ ለካንሰር ሕሙማን ብቻ የሚያገለግል ባለ ስምንት ወለል ሕንፃ እያስገነባ እንደሚገኝ ኃላፊው አስረድዋል፡፡

የሕንፃውም ግንባታ ከተጠናቀቀ በኋላ በርካታ የካንሰር ሕሙማንን መታደግ እንደሚቻል፣ በሕንፃውም አምስት ለጨረር ሕክምና የሚውል ግብዓትን የሚይዝ ክፍል ለብቻው እንደሚኖርም ተናግረዋል፡፡

ማዕከሉም የደም ካንሰር ማከም ወይም የመቅኒ ንቅለ ተከላ አገልግሎትን የሚሰጥ እንደሚሆን፣ ይህም በተለያዩ ቦታዎች ላይ በበሽታው ተይዘው አገልግሎት ባለማግኘት ሲማቅቁ የነበሩ ሕሙማንን ለመታደግ ትልቅ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው አብራርተዋል፡፡

ግንባታው የተለያዩ አገልግሎቶችን ለመስጠት ታስቦ እየተሠራ ሲሆን፣ ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት በሚጀምርበት ወቅት ውጭ አገር ሄደው የሚታከሙ ሕሙማንን ይታደጋል ተብሎ ይታሰባል ብለዋል፡፡

በተያያያዘም በኢትዮጵያ የጡትና የማኅፀን በር ካንሰር በሽታ ተጠቂ የሆኑ ሰዎች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መምጣቱን፣ የማቴዎስ ወንዱ የኢትዮጵያ ካንሰር ሶሳይቲ ፕሮግራም ዳይሬክተር አቶ ዘለዓለም መንግሥቱ ተናግረዋል፡፡

በአገር አቀፍ ደረጃ ሦስት አራተኛ የሚሆኑ ሰዎች የጡት ካንሰር በሽታ ተጠቂ መሆናቸውን፣ በሽታውንም አስቀድሞ ለመከላከል በማኅበረሰቡ ዘንድ በቂ የሆነ ግንዛቤ አለመኖሩን ዳይሬክተሩ አክለው ገልጸዋል፡፡

ሲጋራ ማጨስ፣ አልኮል መጠቀም፣ ጤናማ ያልሆነ አመጋገብና ሌሎች መሰል ነገሮች ለጡት ካንሰር በሽታ አጋላጭ መሆናቸውን ያስታወሱት አቶ ዘለዓለም፣  ጥቅምት ዓለም አቀፍ የጡት ካንሰር ግንዛቤ ማስጨበጫ ወር ተብሎ መወሰዱን፣ በተቋሙ ፕሮጀክቶች በርካታ ሥራዎች መሠራታቸውን ገልጸዋል፡፡

ተቋማቸው ከአዲስ አበባ ውጪ ሆነው በጡት ካንሰር በሽታ የተያዙ ሰዎች ሕክምናቸውን እስከሚያጠናቅቁ ድረስ የትራንስፖርትና የማረፊያ ወጪ እንዲመቻችላቸው ያደርጋል ብለዋል፡፡ እስካሁን 26 ሰዎች ይህንን አገልግሎት እንዲያገኙ መደረጉን፣ ችግሩም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባባሰ በመምጣቱ፣ መንግሥት ለዘርፉ ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ ሳይገልጹ አላለፉም፡፡

ተቋሙ በየዓመቱ የተለያዩ ፕሮጀክቶችን ቀርፆ ተግባራዊ እንደሚያደርግ ገልጸው፣ ከእነዚህም ፕሮጀክቶች መካከል የጡት ካንሰር በሽታ ተጠቂ የሆኑት አገልግሎት የሚያገኙበት አንዱ ነው ብለዋል፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

የመቃወም ነፃነት ውዝግብ በኢትዮጵያ

ስሟ እንዳይገለጽ የጠየቀችው በአዲስ አበባ ከተማ በተለምዶ የሾላ አካባቢ...

የሲሚንቶን እጥረትና ችግር ታሪክ ለማድረግ የተጀመረው አጓጊ ጥረት

በኢትዮጵያ በገበያ ውስጥ ለዓመታት ከፍተኛ ተግዳሮት በመሆን ከሚጠቀሱ ምርቶች...

የብሔር ፖለቲካው ጡዘት የእርስ በርስ ግጭት እንዳያባብስ ጥንቃቄ ይደረግ

በያሲን ባህሩ በሪፖርተር የኅዳር 9 ቀን 2016 ዓ.ም. ዕትም “እኔ...