‹‹ግማሽ ቀልድ አላውቅም!
ሞት እንደሆን ልሙት በሴኮንድ መቶኛ
እንቅልፍ እንደ ሬሳ ዘላለም ልተኛ
መንገድ ስጡኝ ሰፊ…!
‹‹ጉዞ ካጽናፍ አጽናፍ ፤
ፍጥነት እንደ ብርሃን ዓለማትን ልለፍ
የመሬት ቁራጭ ነኝ
ታሪኳን የምጽፍ፤
በጥቁር ወረቀት በሰማይ ብራና ፤
ስጓዝ እተዋለሁ በጠፈር ላይ ፋና
መንገድ ስጡኝ ሰፊ…!
‹‹ፀሐይ ልሁን ፀሐይ ፤
እንደ ፅርሐ አርያም ሁሉንም የሚያሳይ
እሳተ ገሞራ አመድ እረመጡን፤
የሳት ጎርፍ ልሁን።
ከሲኦል ሚሊዮን ቢሊዮን ልቃጠል
ከገሃነመ እሳት ሚሊዮን ነበልባል
መንገድ ስጡኝ ሰፊ…!
‹‹ልሂድ በጨለማ ዓይን የማያይበት
ጥቁር የከሰለ፤ በጠቆረው ፅልመት
በፀጥታው ቦታ ዘመን ከቆመበት።
በዘላለማዊ ባዶ ቦታ ዋሻ
አየር በሌለበት አድማስ መጨረሻ።
ልንሳፈፍ ልቃኘው
ለእኔ ኮከብ ጠጠር ኳስ መጫወቻ ነው
መንገድ ስጡኝ ሰፊ…!
‹‹ስሄድ እኖራለሁ፤
ስከንፍ እኖራለሁ
ሰማየ ሰማያትን .. እመዘብራለሁ
የተዘጋውን በር .. እበረግዳለሁ
የሌለ እስቲፈጠር፤ የሞተ እስኪነቃ
በትልቅ ዕርምጃ ከመሬት ጨረቃ
ከጨረቃ ኮከብ
ካንዱ ዓለም ወዳንዱ
ስጓዝ እፈጥናለሁ
በፀሐይ ላይ ቤቴን .. ጐጆ እቀልሳለሁ
መንገድ ስጡኝ ሰፊ…!
‹‹ግማሽ ቀልድ አላውቅም ።
ከሲኦል ሚሊዮን ቢሊዮን ልቃጠል።
ከገሃነመ እሳት ሚሊዮን ነበልባል።
መንገድ ስጡኝ ሰፊ . . .
መንገድ ስጡኝ ሰፊ፤
ጉዞ ካጽናፍ አጽናፍ፤
ፍጥነት እንደ ብርሃን ዓለማትን ልለፍ።
ፀሐይ ልሁን ፀሐይ፤
እንደ ፅርሐ አርያም፤ ሁሉንም የሚያሳይ።
መንገድ ስጡኝ ሰፊ
መንገድ ስጡኝ ሰፊ’››
ገብረ ክርስቶስ ደስታ ‹‹መንገድ ስጡኝ ሰፊ››
‹‹ቢያንስ ግማሽ መንገድ…››