Thursday, September 28, 2023

የወልቃይት ጥያቄና የሰላም ስምምነቱ

- Advertisement -spot_img

በብዛት የተነበቡ

በአማራና በትግራይ ክልሎች የይገባኛል ጥያቄ ሲነሳበት የቆየው የወልቃይት ጉዳይ፣ አሁንም የመነጋገሪያ ርዕስ ነው፡፡ በቅርቡ በደቡብ አፍሪካ የሰላም ስምምነት ከተፈረመ በኋላ፣ የወልቃይት ይገባኛል ጥያቄ የፖለቲካ ውጥረት ምክንያት ሆኖ ቀጥሏል፡፡

ባለፈው ሳምንት ፓላርማ ተገኝተው ማብራሪያ የሰጡት ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር)፣ ‹‹የወልቃይት ጉዳይ በሕግና በንግግር ይፈታል ነው ያልነው›› ብለው መናገራቸው፣ መንግሥታቸው በጉዳዩ ላይ የጠራ አቋም አልያዘም የሚል አስተያየት እያሰጠ ነው፡፡ የወልቃይት ጉዳይ ድርድሩንና የሰላም ስምምነቱን ተከትሎ በተዛባ መንገድ ለፖለቲካ ዓላማ መዋሉን ዓብይ (ዶ/ር) ተናግረው ነበር፡፡ ሆን ተብሎ ጉዳዩን በመጠምዘዝ ለፖለቲካ ንግድ የማዋል ዝንባሌ ይታያል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ በሕገ መንግሥቱና አገሪቱ በገነባቻቸው ተቋማት ውሳኔ እንደሚያገኝ ገልጸዋል፡፡

ይህን በተመለከተ የወልቃይት ጥያቄን የሚያነሱ ወገኖች ችግሩ መንግሥት በሚለው መንገድ ሊፈታ እንደማይችል ሥጋታቸውን እያሰሙ ነው፡፡ የመንግሥት ዕርምጃ ችግሩን እንደሚያወሳስበው በመግለጽ ላይ የሚገኙት እነዚህ ወገኖች፣ ችግሩ በፖለቲካ ውሳኔ ዕልባት እንዲሰጠው በመጠየቅ ላይ ናቸው፡፡

የወልቃይት ተወላጅ የሆኑት አቶ አስፋው አብረሃ የወልቃይት የአማራ ማንነት አስመላሽ ኮሚቴ፣ በባህር ዳር ለሦስት ቀናት ስብሰባ ማድረጉን ገልጸዋል፡፡ ቅዳሜ ጥቅምት 10 ቀን 2015 ዓ.ም. ይጠናቀቃል ተብሎ በነበረው በዚህ ስብሰባ፣ ኮሚቴው የመንግሥትን አቋም አስመልክቶ የራሱን አቋም ይይዛል ተብሎ እንደሚጠበቅ አቶ አስፋው ተናግረዋል፡፡

‹‹ኮሚቴው ወልቃይትን በሚመለከት በሰላም ስምምነቱ የተደረሰውን ስምምነት፣ እንዲሁም መንግሥት የያዘውን አቋም ይፈትሻል፡፡ ከዚህ ተነስቶም ለወልቃይት ይበጃል የሚለውን የራሱን አቋም ያስቀምጣል፡፡ በዚህ ስብሰባ የተለያዩ የውሳኔ ሐሳቦች ይቀርባሉ፡፡ ከእነዚህ ውስጥ ግን ችግሩ በሪፈረንደም (ሕዝብ ውሳኔ) ይፈታ የሚል ውሳኔ ፈጽሞ እንደማይኖር በእርግጠኝነት መናገር እችላለሁ፤›› በማለት ነው አቶ አስፋው ለሪፖርተር የተናገሩት፡፡

አጠቃላይ አገራዊ ሁኔታውም ቢሆን የወልቃይትን ጉዳይ በጠረጴዛ ዙሪያ ተቀምጦ ለመወያየትና በሕገ መንግሥት ለመፍታት አመቺ ምኅዳር እንደሌለው የተናገሩት አቶ አስፋው፣ ከዚህ አንፃር ኮሚቴው ከሚያቀርባቸው ውሳኔዎች የተሻለውን ውሳኔ ያሳልፋል ብለው እንደሚያምኑ ተናግረዋል፡፡

በአዲስ አበባ የወልቃይት ጠገዴ አማራ የሰላምና ልማት ማኅበር ፕሬዚዳንት የሆኑት የኮተቤ ሜትሮፖሊታን ዩኒቨርሲቲ መምህሩ አሰፋ አዳነ (ዶ/ር)፣ ማኅበራቸው በወልቃይት ጉዳይ ስብሰባ ለመቀመጥ መዘጋጀቱን ይናገራሉ፡፡ አዲስ የሚተላለፍ አቋም እንደማይኖርና በዚህ ጉዳይ አቋማቸው እንደማይቀየር የተናገሩት አሰፋ (ዶ/ር)፣ የጠቅላይ ሚኒስትሩ አነጋገር ግልጽ ያልሆነና አወዛጋቢ ነው ብለዋል፡፡

‹‹የወልቃይት ሰዎች ሁለት ዓይነት ጎልዳፋ ቋንቋ የሚናገሩ ሕዝቦች ናቸው ተብሎ በጠቅላይ ሚኒስትሩ መነገሩ፣ ከዚህ ቀደም ያልነበረና ሰምተነው የማናውቀው አዲስ አገላለጽ ነው፡፡ ይህ ለምን እንደተባለ ለእኛ ግልጽ አይደለም፡፡ በዚህ ጉዳይ እንወያያለን ሆኖም ወልቃይትን በተመለከተ አቋማችን ግልጽ ነው፤›› ብለዋል፡፡

የወልቃይትን ወደ ትግራይ የመጠቅለል ሒደት መለስ ብለው ያስታወሱት አሰፋ (ዶ/ር)፣ ‹‹ሕወሓት ደርግን አሸንፎ ሥልጣን ሲይዝ በደነገገው አዋጅ ቁጥር 7/1984 መሠረት ብሔር ብሔረሰቦች የራሳቸውን ክልል እስኪያቋቁሙ ድረስ የአገሪቱ ክልሎች ወሰን ባለበት ይቆያል ብሎ አስቀምጧል፡፡ ይሁን እንጂ ሕወሓት ራሱ ያወጣውን ይህን የሽግግር ጊዜ አዋጅ ሽሮ ነው ወልቃይትና ራያን ወደ ትግራይ ያካለላቸው፤›› በማለትም ያስረዳሉ፡፡

በሽግግር ጊዜ የወጡና አሁንም ድረስ ተፈጻሚነት ያላቸው ያልተሻሩ አዋጆች መኖራቸውን ያስረዱት አሰፋ (ዶ/ር)፣ አዋጅ ቁጥር 7/1984 ከእነዚህ መካከል አንዱ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡

‹‹ወልቃይት ሲባል ብዙ ሰው ያሳስትብናል፡፡ ነገር ግን ግዛቱ ጠገዴን፣ ሁመራን፣ ጠለምትን የያዘ መካከል ላይ የሚገኝ በመሆኑ ነው ወልቃይት በሚል የሚጠራው እንጂ፣ አካባቢው የጎንደር አካል የነበረ ሰፊ የአማራ መሬት መሆኑን ሕዝቡ ሊረዳው ይገባል፤›› በማለትም ስለአካባቢው ገጽታ አስረድተዋል፡፡

‹‹አዋጅ እያለ ነው ሕወሓት በፖለቲካ ውሳኔ ወልቃይትን ወደ ትግራይ ያካለለው፡፡ ይህን የፖለቲካ ውሳኔ ደግሞ መመለስ የሚቻለው በፖለቲካ ውሳኔ ነው፡፡ በሕገ መንግሥት ወይም በሕዝበ ውሳኔ በማለት አትፈታውም፤›› ሲሉም አሰፋ (ዶ/ር) ለችግሩ መፍቻ ያሉትን መፍትሔ ተናግረዋል፡፡

የወልቃይት ጠገዴ ጉዳይ በመንግሥት በኩል በሕገ መንግሥቱና በንግግር እንዲፈታ ግልጽ አቋም መያዙን ጠቅላይ ሚኒስትሩ በይፋ ተናግረዋል፡፡ መንግሥት ጉዳዩን አለሳልሶ መያዝን የመረጠም ይመስላል፡፡ በትግራይም ሆነ በአማራ ልሂቃን የሚነሳውን የወልቃይት ይገባኛል ጥያቄ አለዝቦና አስታርቆ ለመመለስ ፍላጎት ያለው ይመስላል፡፡ ይሁን እንጂ የወልቃይት ጉዳይ በዚህ መሀል የአማራና የትግራይ ልሂቃን ዋና መፋተጊያ ጉዳይ ሆኖ የቀጠለ ይመስላል፡፡

ከሰሞኑ በአሀዱ ቴሌቪዥን ቀርበው የነበሩት የትግራይ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ትዴፓ) አመራር አቶ ሙሉ ብርሃን ኃይሌና የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄው (አብን) አመራር ደሳለኝ ጫኔ (ዶ/ር) ያደረጉት ክርክርም፣ የዚሁ የሁለቱ ማኅበረሰቦች ፖለቲከኞች ተቃርኖን የሚያሳይ ነበር፡፡

ደሳለኝ (ዶ/ር)፣ ‹‹በሰላም ስምምነቱ መሠረታዊ የሚባሉት የአማራ የፖለቲካ ጥያቄዎች በተለይ የወልቃይትና የራያ ጉዳዮች በሕገ መንግሥቱ ይፈታሉ ተብለው ነው የታለፉት፡፡ ይህ አስገራሚና ታሪካዊ ስህተት ነው፡፡ የሽግግር መንግሥት ከመዋቀሩ፣ እንዲሁም ሕገ መንግሥቱ ከመታወጁ በፊት በወረራ የተያዙ ቦታዎች ናቸው፡፡ በሕገ መንግሥቱ ይፈታሉ ማለት እንዴት ይቻላል? ታሪካዊ ርስቶቻችን ወልቃይትና ራያ የጦርነቱ መነሻ የሆኑ ወሳኝ ጉዳዮች ናቸው፤›› ሲሉ ነበር የተከራከሩት፡፡

አቶ ሙሉ ብርሃን በበኩላቸው፣ ‹‹ወቅቱን ያልተከተሉ ጥያቄዎች ለምን ይቀርባሉ? የማንነትና የርስት ጥያቄ አሁን ወቅቱ ነው ወይ? እኛ እንደ ትግራይ ተወላጆች የፍትሕና የዴሞክራሲ ጥያቄ በኢትዮጵያ ከተመለሰ ጉዳዩ በቀላሉ ይፈታል ብለን እናምናለን፡፡ ፍትሐዊ ተቋማት ካሉንና ዴሞክራሲ በኢትዮጵያ ከሰፈነ ይህ የማንነትና የይገባኛል ጥያቄም ፍትሐዊ በሆነ መንገድ ዕልባት ያገኛል፡፡ የወልቃይትና የራያ ጉዳዮች በአማራና ትግራይ ሕዝብ መካከል አጀንዳ መሆን አልነበረባቸውም፡፡ ሌላ የፖለቲካ ትርፍ ለማግኘት ካልተፈለገ በስተቀር ይህ ጉዳይ መነሳት አልነበረበትም፡፡ እኔ በግሌ ሽሬ ተወልጄ ጎንደር የኖርኩ የአማራንም ሆነ የትግራይን ሕዝብ ሥነ ልቦና በደንብ የማውቅ ሰው ነኝ፡፡ ሁለቱ ሕዝቦች በጋራ ለብዙ ሺሕ ዓመታት ይኖሩ የነበሩ ሕዝቦች ናቸው፡፡ ቦታው ለሁለቱም ይበቃቸዋል፡፡

‹‹ይህንን ጥያቄ ብናቆየውና ሌሎች አንገብጋቢ ጉዳዮች ላይ ብናተኩር ይሻላል፡፡ የችግሮች ሁሉ ፈጣሪ የሆነው ሕወሓትን ትጥቅ በማስፈታት ላይ ብናተኩርና በሒደት እነዚህን ጥያቄዎች ብንመልስ የተሻለ ነው፤›› በማለት ነበር የተከራከሩት፡፡

በመንግሥትም ሆነ በሌሎች የፖለቲካ ኃይሎች ዘንድ የወልቃይት ጥያቄ ጉዳይ ለፖለቲካ ዓላማ እየዋለ ይገኛል የሚል ሐሳብ ተደጋግሞ ይደመጣል፡፡ በእርግጥ ይህን ጉዳይ ለፖለቲካ ትርፍ ሊገለገልበት የሚፈልገው ማን ነው? በሚለው ላይ ግን ሰፊ ልዩነት ይታያል፡፡

መንግሥት የወልቃይትን ፖለቲካ በማራገብ ለራሳቸው የፖለቲካ ትርፍ ለማዋል የሚፈልጉ ወገኖች አሉ ብሎ ሌሎችን እንደሚወነጅለው ሁሉ፣ ከጉዳዩ ለማትረፍ የሚሞክረው መንግሥት ነው የሚል ወቀሳም ከሌሎች አቅጣጫዎች ይሰማል፡፡

ይህን ሐሳብ የሚጋሩት አሰፋ (ዶ/ር) ይህ ዓይነት አካሄድ መኖሩን ይናገራሉ፡፡ ‹‹የአማራና የትግራይ ማኅበረሰብ የሚለየው ብዙ ነገር የለም፡፡ በቋንቋ አንዱ የሌላውን ይናገራል፣ የጋራ እምነት፣ ባህል፣ እሴትና ሥነ ልቦና ያለው ነው፡፡ ሕዝቡ ተጋብቶና ተዛምዶም የኖረ ነው፡፡ ነገር ግን በአግባቡ ሊመለስ የሚችለውን የወልቃይት ጥያቄ በማወሳሰብ ሁለቱን ማኅበረሰብ እርስ በርስ ማጋጨት እንደ አንድ የፖለቲካ ሥልት እየተኬደበት ይገኛል፡፡ ሁለቱ ማኅበረሰቦች በጦርነት ተዘፍቀው በድህነት እየዳከሩ ለሌሎች ታዛዥና ተገዥ ሆነው እንዲኖሩ የፖለቲካ ሴራ የመጠንሰስ አዝማሚያ በደንብ ይታያል፤›› በማለት ተናግረዋል፡፡

‹‹የወልቃይትን ጉዳይ ሕገ መንግሥት አያውቀውም፡፡ በሕገ መንግሥቱ ይፈታ ማለት አያስኬድም፤››  ሲሉ የገለጹት አሰፋ (ዶ/ር)፣ የአማራ ክልል የወልቃይት የማንነት ጥያቄን በግልጽ አንስቶ አስፍላጊ ሰነዶችን አያይዞ ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ጥያቄውን ካቀረበ መቆየቱን አስታውሰዋል፡፡ ይህ ውሳኔ እየተጠበቀ ባለበት ጉዳዩን የሚያወሳስብና የሚያምታታ ይዘት ያለው አቋም መንግሥት ማንፀባረቁ አግባብነት እንደሌለው አመልክተዋል፡፡

ሕወሓት ምዕራብ ትግራይ ወደ ትግራይ ካልተመለሰ ብሎ እንደ አንድ ቅድመ ሁኔታ በድርድሩ ያስቀመጠው የወልቃይት ጉዳይ በሕገ መንግሥቱ ማዕቀፍ ይፈታል ቢባልም፣ በየትኛው ዓይነት ሕገ መንግሥታዊ ማዕቀፍ የሚለው እያከራከረ ይገኛል፡፡

የወልቃይት ተወላጅ የሆኑት አቶ ተስፋ የሺወንድም በበኩላቸው፣ ‹‹በየትኛው ሕገ መንግሥት?›› ሲሉ ነው ጥያቄ የሚያነሱት፡፡

‹‹ዜጋን እንደ ዜጋ የማያውቀው የጎሳ ፖለቲካ ሕገ መንትግሥት ባለበት የሚኖርበትና የራሱ መሬት የሌላ ይሁን ቢባል ማን እሺ ይላል?›› ሲሉ ይጠይቃሉ፡፡ ‹‹እንደ አንድ ዜጋ ሁሉም ኢትዮጵያዊ በየትም ተንቀሳቅሶ መሥራትና መኖር የሚችልበት ዕድል ተነፍጎ፣ መሬትህ በሌላ ክልል ሥር ይሁን ቢባል ማንም እሺ አይልም፤›› በማለትም ያስረዳሉ፡፡

‹‹ይህን ዜጎችን አገር አልባ ያደረገ ሕገ መንግሥት እንዲቀጥል የፈቀደ መንግሥት፣ የማንነትህና የመሬት ጥያቄህ በሕገ መንግሥት መሠረት ይፈታል ብሎ እኔ ላይ አቋሙን ለመጫን እንዳችም የሞራል ልዕልና የለውም፤›› በማለትም፣ የችግሩ ምንጭ ሰፊ የሕግ ጥያቄ የሚያስነሳ መሆኑን አውስተዋል፡፡

‹‹አንዳንድ የማዕከላዊ ፖለቲካ ኃይሎች የወልቃይት አካባቢ ሕዝብ ለዘመናት መሬቱንም ማንነቱንም ተነፍጎ መኖሩን ረስተው፣ ችግሩን አቃለው በኢትዮጵያ ማዕቀፍ በሕገ መንግሥቱ ይፈታል ሲሉ ይደመጣሉ፤›› የሚሉት አቶ ተስፋ፣ ለራሳቸው የማያደርጉትን ነገር የወልቃይት ሕዝብ እንዲቀበል የፖለቲካ ማባበያና መሸንገያ መስጠታቸው አግባብ አለመሆኑን አስረድተዋል፡፡

በቅርቡ በወልቃይትና አካባቢው ጉብኝት የማድረግና የአካባቢውን ተጨባጭ ሁኔታ የመገምገም ዕድል የገጠማቸው የእናት ፓርቲ ዋና ጸሐፊ አቶ ጌትነት ግርማ በበኩላቸው፣ ጉዳዩ ከብዙ አቅጣጫዎች መታየት እንደሚኖርበት ያሳስባሉ፡፡

‹‹መብራት ካገኘን ሁለት ዓመታችን፡፡ ውኃ የምንቀዳው ብዙ ተጉዘን ተከዜ ሸለቆ እየወረድን በአህያ ነው፡፡ ያለንበት የኑሮ ሸክም ከባድ ቢሆንም፣ ነገር ግን የነፃነት አየርን እየማግን ነው፤›› ብሎ አንድ የአካባቢው ነዋሪ እንደነገራቸውም አቶ ጌትነት ይናገራሉ፡፡ ከዚህ በመነሳት የወልቃይት ጉዳይ ከተራራው፣ ከወንዙና ከመሬቱ ብቻ ሳይሆን ካሳለፈው ግፍና ከተገኘው ነፃነት አንፃር መታየት እንዳለበት ይገልጻሉ፡፡

የመንግሥት ውሳኔም ሆነ የሰላም ስምምነቱ የአካባቢውን የፖለቲካ ሁኔታ አወሳስቦታል የሚሉት አቶ ጌትነት፣ ምናልባትም የአካባቢው ይገባኛል ጥያቄ በአጭር ጊዜ በአግባቡ ካልተፈታ ሌላ ዙር የጦርነት ቀውስ እንዳይወልድ እንደሚሠጉ አመልክተዋል፡፡

‹‹የሰሜኑ ፖለቲካ ሚዛኑን በሳተና በተናጋ ቁጥር ደግሞ ቀውሱ አገራዊ የሆነበት አጋጣሚ ብዙ ነው፤›› የሚሉት አቶ ጌትነት፣ የቅርብ ጊዜው ጦርነት በሰሜን ዕዝ ላይ በተፈጸመ ጥቃት መቀስቀሱን አስታውሰዋል፡፡

የትግራይና የአማራ ፖለቲካ ልሂቃን በዚህ ረገድ ‹‹ትንሽ ሻገር የሚል መፍትሔ አፈላላጊ ፖለቲካ›› ያስፈልጋቸዋል ያሉት አቶ ጌትነት፣ በዚህ ጉዳይ ለረዥም ጊዜ ሲበላሉ ከመኖር ቆም ብሎ ሁሉም ወገን ቢያስብበት እንደሚሻል አሳስበዋል፡፡

spot_img
- Advertisement -

ትኩስ ጽሑፎች

ተዛማጅ ጽሑፎች

- Advertisement -
- Advertisement -