Saturday, December 2, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -

የተመረጡ ፅሑፎች

መንግሥት ቀይ መስመር ያለው ሌብነት ቀይ ምንጣፍ ከሆነ ምንጣፉን ያንሳ!

ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) ሰሞኑን በፓርላማ ተገኝተው ማብራሪያ ከሰጡባቸው አንኳር ጉዳዮች መካከል አንዱ ሥር እየሰደደ የመጣውን ሌብነትና የመልካም አስተዳደር ችግርን የሚመለከተው ተጠቃሽ ነው፡፡

በመልካም አስተዳደር ችግር ሕዝብ በብርቱ መሰቃየት ከጀመረ የቆየ ቢሆንም ችግሩ እየባሰ ስለመጣ አሁንም ‹‹ኧረ የመፍትሔ ያለህ?›› ተብሎ ጥያቄው በፓርላማ ቀርቧል፡፡ እንዲህ ያለው ጥያቄ ከዚህ ቀደም በተደጋጋሚ ሲቀርብ መቆየቱ አይዘነጋም፡፡ እስከ ዛሬ ሌብነት ላይ እንዘምታለን ተብሎ በየመድረኩ ሲደሰኮር የነበረውን ያህል ዕርምጃ ባለመወሰዱ ዜጎች የገዛ መብታቸውን ወይም የሚሹትን አገልግሎት ጉቦ ሰጥተው ካልሆነ ማግኘት ባለመቻላቸው ጥያቄው ደግሞ ደጋግሞ ቢቀርብ አያስገርምም፡፡ ዜጎች ታክስ ከፍለው እንዲያስተዳድራቸው ደመወዝ የሚከፍሉት የመንግሥት ሹመኛ ወይም ‹‹አገልጋይ›› ጉቦ ካልከፈሉ አገልግሎት ለማግኘት ተቸግረዋል። ይህ ጉዳይ ሃይ ባይ አጥቶ አሁን ላይ ሕጋዊ አሠራር እስከመምሰል ደርሷል፡፡  እንዲህ ያለውን ዓይን ያወጣ ሌብነት በተለይ እንደ መሬት አስተዳደርና መሰል አገልግሎት መስጫ ተብለው የተደራጁ የመንግሥት ቢሮዎች ውስጥ መመልከት ‹‹ሕጋዊ ሥራ›› ወደ መሆን እንደተቃረበ መረዳት ያስችላል። ነገሩ የአደባባይ ሚስጥር ከመሆን አልፎ  ‹‹ኧረ ወዴት ሄደን አቤት እንበል?›› እስከማለት የደረሰ ምሬትን በሕዝብ ዘንድ ፈጥሯል። ይህንን ጩኸት የሰማ ግን የለም፡፡ ዘረፋውም ቀጥሏል፡፡

ከሰሞኑ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የፓርላማ ማብራሪያ መንግሥት ይህ ዓይን ያወጣ ሌብነት የት ድረስ እንደተጓዘ በሚገባ የሚያውቅ መሆኑን ነው፡፡

በአሁኑ ወቅት የተንሰራፋው ሌብነት የዕድገት ደረጃ ብዙ ርቀት በመሄድ ያለ ከልካይ በክብር በቀይ ምንጣፍ ላይ እየተጓዘ ስለመሆኑ ጭምር ማብራሪያቸው አመልክቶናል፡፡

ሌብነት ቀይ መስመር መሆኑ እየተገለጸ እንኳን እነሱ ቀይ መስመሩን ቀይ ምንጣፍ  አድርገውት እየተሞሸሩበት ስለመሆኑ መግለጻቸውም ሌብነት የደረሰበትን ደረጃ ከማመላከት ባለፈ መንግሥት ችግሩን በሚገባ ማወቁን አረጋግጠውልናል፡፡ እንደውም የሌብነት ደረጃ ህልውና እስከመፈታተን ደርሷል የተባለበት ምክንያት የችግሩን ግዝፈት ዓሳይቷል፡፡ 

ሌላው ከሌብነትና ከመልካም አስተዳደር ግድፈት ጋር የተያያዘው ማብራሪያቸው የመሬት ዝርፊያን የተመለከተው ነው፡፡ መሬት የመንግሥትና የሕዝብ መሆኑ ቀርቶ የደላሎች ሆኗል ብለው ቆምጨጭ ያለ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ እዚህ ጋር አንድ ነገር እንጨምር ደላሎች የመሬት ባለቤት ብቻ ሳይሆኑ የዚችን አገር አጠቃላይ የግብይት ሥርዓት ያበለሻሹ ኢኮኖሚውንም በተበለሻሸ ሥሌት የሚዘውሩ ናቸው፡፡ ዛሬ አገር የገባችበትን አስከፊ የዋጋ ንረት በማባበሱ ረገድ የደላሎች ሚና ከፍተኛ ነው፡፡ የሸቀጦችና የተለያዩ ምርቶች ዋጋ እንደተፈለገ ወደ ላይ እንዲወጣ የደላሎች የተደራጀ አካሄድና ሸማቹን ስለማማረሩ መነገር የተጀመረው ዛሬ አይደለም፡፡ የቤት ኪራይ ዋጋ በዘፈቀደ የሚቆለለው ተከራይ አንዱ ቤት ወደ ሌላ ቤት የሚገለበጥበት ዋና ምክንያት የመኖሪያ ቤት እጥረት ብቻ ሳይሆን በእጥረቱ ሰበብ ደላሎች እንዳሻቸው ሲሆኑበት ምንም ዕርምጃ አለመወሰዱ ነው፡፡ ዛሬ የዶላር ረሃባችን ወደ ችጋር እየቀየሩብን ያሉ ብዙ ምክንያቶች ቢኖሩም በጥቁር ገበያው የሚዘዋወረው የውጭ ምንዛሪ የሚገለባበጠውና ከአንዱ ወደ ሌላው የሚሸጋገረው በደላሎች አገናኝነት ስለሆነ የደላሎች መረን የለቀቀ የማናለብኝነት ተግባር በመሬት ባለቤትነት ብቻ ተጠቅሶ የሚያልፍ አይደለም፡፡

ለማንኛውም ወደ መሬት ጉዳይ እንመለስ፡፡ አሁንም ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ማብራሪያ የምንረዳው መሬት በደላሎችና በሹመኞች እጅ መሆኑን መንግሥት እርግጠኛ ስለመሆኑ ደርሼበታለሁ የሚለውን ትርጉም ይሰጠናል፡፡ ችግሩ በዚህ ደረጃ መገለጹ በራሱ መልካም ነው፡፡

ደላሎችና የመንግሥት ሹመኞች የመሬት ቸርቻሪ ሆነው መገኘታቸው በዚህን ያህል ደረጃ ከታወቀ ደግሞ ችግሩ ደላሎችንና ሌባ ሹመኞችን ልክ አለማስገባት እንደሆነ ያስገነዝበናል፡፡

አንድን ችግር ለመፍታት ግማሽ የሚሆነውን መፍትሔ እንደማግኘት የሚቆጠረው ችግሩን ማወቅ ወይም የጥፋት አድራሾቹን ማንነት መለየት በመሆኑ በመንግሥት ዕርምጃ ለመውሰድ በቂ መረጃ አለው ብለን እንድናስብ ያደርገናል፡፡ 

ምክንያቱም የከተማው መሬት በደላሎች እጅ ሆኖ  መሬቱን ለመቸብቸብ አጋዥ የሆኑት ሹመኞች መሆናቸው ታውቋል ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ከዚህ በኋላ መንግሥት ዕርምጃ ለመውሰድ በመንም ሊያስብ አይችልም፡፡ ዛሬ ችግሩ የህልውና ጉዳይ እስከመሆን ደርሷል ከመባሉ በፊት ከሥር ከሥር በተዛተው ልክ ዕርምጃ ቢወሰድ ዛሬ ‹‹ዘመቻ ሌብነት›› ተብሎ በአገር ደረጃ ብሔራዊ ኮሚቴ ባልተዋቀረና በሌሎች ሥራዎች መጠመድ ያለባቸው ሰዎች ሌቦችን ወደ ማሳደግ ባልገቡም ነበር፡፡ በነገራችን ላይ ቢዘገይም ጉዳዩ በአገር ደረጃ ትኩረት ተሰጥቶት በሌብነት ላይ ለመዝመት ጉዳዩን ተከታትሎ ዕርምጃ ለመውሰድ ኮሚቴ ተቋቁሞ ወደ ሥራ መገባቱን ግን ማድነቅ ይገባል፡፡

ይህ ኮሚቴ ግን ብዙ ሥራ ይጠብቀዋል፡፡ በተለይ ከመሬት ጋር የተያያዘው ሌብነት ዛሬ የተነገረ ሳይሆን ለዓመታት እንዲሁ ሲዛትበት ቆይቶ መፍትሔ ያልመጣበት አንዱ ምክንያት ሌብነቱ ጠንከር ባለ ኔትወርክ የተሳሰረ ጭምር በመሆኑ ይህንን ኔትዎርክ ለመበጣጠስ ከባድ በመሆኑ ነው ተብሎ ስለሚታሰብ የኮሚቴውን ሥራ አድካሚ ቢያደርገውም እስከ መጨረሻው ተጉዞ ውጤት እንዲያመጣ ግን ይጠበቃል፡፡ ስለዚህ በዚህ ረገድ ሥር የሰደደውና ዓይን ያወጣው ሌብነት ሌቦቹንና ተባባሪዎችን አቅም ለማዳከም የዘረጉትን ሰንሰለት መበጣጠስ ቅድሚያ ሊሰጠው ይገባል፡፡ የኮሚቴው ሥራ ከዚህ በፊት ያለአግባብ የተዘረፉ መሬቶችን ማስመለስንም የሚያጠቃልል መሆንም አለበት፡፡ 

ሥር ነቀል ለውጥ ሊመጣ የሚችለውም እስካሁን በሕገወጥ መንገድ ተላልፈው የተከበረባቸውን መሬቶች ሲያስመልስ ለዚህ ተግባር የተባበሩትን ሕግ ፊት አቅርቦ ሲያስቀጣ ነው፡፡ ከቢሮ ቀጭ ብለው ጉቦ ሲሰበስቡ የነበሩትን ሁሉ መልቀም ካልተቻለና ስህተታቸው ለሌሎች መማሪያ ማድረግ እስካልተቻለ ድረስ በእነሱ እግር የሚተኩትም በዚያው መንገድ ስለሚቀጥሉ ዕርምጃው የጠነከረ መሆን ይገባዋል፡፡ ከዚህ ጎን ልጎን ሌላው በብርቱ መታሰብ ያለበት ይህ ኮሚቴ ሌቦችን በማሳደድ ብቻ ሳይወሰን ከዚህ በኋላ ሌብነትን ለማስቀረት የሚረዳ አሠራርን መዘርጋት የግድ መሆኑን መጥቀስ ይገባል፡፡

ከዚህ ቀደም ብልፅግና ፓርቲ ከሕዝብ ጋር ውይይት ባደረገበት ወቅት ሕዝቡ ሰላሜን አስጠብቅልኝ ሌብነት ላይ ዝመትልኝ በማለቱ በዚሁ መሠረት ፓርቲው ሌብነት እዋጋለሁ ብሎ ቃል ገብቶ ምንም ዕርምጃ እንዳልወሰደና አሁንም ይህ ብሔራዊ ኮሚቴ ሥራው የአንድ ሰሞን እንዳይሆንና እንደ ነገሩ ነካክቶ የበለጠ በተራቡ ጅቦች አገር እዳትበላ ቆምጨጭ ብሎ እንዲሠራና የሕዝብን ምሬት ይታደግ ዘንድ የሌቦቹን መረማመጃ ቀይ ምንጣፍ ማንሳት ሌብነት ላይ ስህተት መሆኑን በተግባር ማሳየት ለመንግሥትም የመጨረሻው ቀይ መስመር መሆኑን ይገባዋል፡፡ ሌብነትን እንደቀድሞ በዛቻና በፉከራ ማስቀረት እንደማይቻል አውቆ ሌብነትን ማጥፋት ቃሉን እንዲጠብቅ ያስፈልጋል፡፡

Latest Posts

- Advertisement -

ወቅታዊ ፅሑፎች

ትኩስ ዜናዎች ለማግኘት