Thursday, September 28, 2023
- ማስታወቂያ -
- ማስታወቂያ -

ኅብረት ባንክ ካፒታሉን ወደ 20 ቢሊዮን ብር ለማሳደግ ወሰነ

ተዛማጅ ፅሁፎች

ከጦርነቱ ጋር በተያያዘ የብድር አመላለስ ጫና ፈጥሮበታል

የኅብረት ባንክ ጠቅላላ ጉባዔ የባንኩን ካፒታል ወደ 20 ቢሊዮን ብር ለማሳደግ የቀረበለትን የውሳኔ ሐሳብ ተቀብሎ አጸደቀ።

ባንኩ ኅዳር 8 ቀን 2015 ዓ.ም. ባካሄው አስቸኳይ ጠቅላላ ጉባዔ ላይ የባንኩ የዳይሬክተሮች ቦርድ የባንኩን ካፒታል ለማሳደግ የውሳኔ ሐሳብ ያቀረቡ ሲሆን፣ በጠቅላላ ጉባዔው የተሳተፉ ባለአክሲዮኖች የውሳኔ ሐሳቡን በአብላጫ ድምፅ አፅድቀዋል። በዚህም መሠረት የባንኩን ካፒታል በ15 ቢሊዮን ብር ለማሳደግ የወሰኑ ሲሆን፣ የተጠቀሰውን ያህል ገንዘብ ማመንጨት የሚችሉ አዲስ አክሲዮኖች እንዲሸጥና በአምስት ዓመት ውስጥ በሁለት ዙር ተከፍሎ እንዲጠናቀቅ ተስማምተዋል፡፡

አዲሱ የኅብረት ባንክ የዳይሬክተሮች ቦርድ ሰብሳቢ ሳምራዊት ጌታመሳይ (ኢንጂነር) ካፒታሉን ለማሳደግ አስፈላጊ የሆነበትን ምክንያቶች የዘረዘሩ ሲሆን፣ ከነዚህም መካከል በዋናነት የተጠቀሱት የኢትዮጵያ የባንክ ዘርፍ ለውጭ ገበያ ክፍት ከመሆኑ ጋር ተያይዞ የሚገጥሙ ተግዳሮቶችን ለማቋቋም ታሳቢ ያደረገ መሆኑን ነው፡፡ ‹‹በግድም ይሁን በውድ በአገር ውስጥ ያሉ ባንኮች የሚጣመሩበት ሁኔታ ሊፈጠር እንደሚችል ጠቋሚ ምልክቶች አሉ›› ያሉት የቦርድ ሊቀመንበሯ፣ ‹‹በዚህ ሒደት ውስጥ የሚገባ ከሆነ ከፍተኛ የካፒታል አቅም ያለው ተጠቃሚ የሚሆንበት ሁኔታ ሊፈጠር ይቻላል፤›› ብለዋል፡፡ ስለዚህ ባንካቸው ከወዲሁ ካፒታሉን በማሳደግ ዝግጁ መሆን ስላለበት የካፒታል ማሳደጉ የውሳኔ ሐሳብ መቅረቡን ተናግረዋል።

የውጭ ባንኮች ወደ ኢትዮጵያ በሚገቡበት ወቅት ብቁ ተወዳዳሪ ለመሆን ከሚገቡት ባንኮች ጋር በጋራ ለመሥራትና ተመራጭ ሆኖ ለመገኘት የባንኩን ካፒታል ማሳደግ አስፈላጊና የግድ መሆኑንም ገልጸዋል። የባንኩን ካፒታል ለማሳደግ ከቀረቡት ሰባት አንኳር ምክንቶች  ውስጥ የባንኩን የማበደር አቅም ለማሳደግ የሚለውም ተጠቅሷል፡፡ የባንኩን ካፒታል አቅም ከአቻ ባንኮች ጋር ለማስተካከልና ባንኩን የበለጠ ተወዳዳሪ ለማድረግ የሚቻለውም ካፒታሉን በማሳደግ በመሆኑ፣ ጠቅላላ ጉባዔው ይህንን በመገንዘብ የቀረበውን የውሳኔ ሐሳብ ያፀደቀው ዘንድ ጠይቀዋል፡፡ በዚሁ የውሳኔ ሐሳብ ላይ የተወያየው ጠቅላላ ጉባዔውም ሐሳቡን በአብላጫ ድምፅ አፅድቆታል፡፡

ባንኩ ካፒታሉን በ15 ቢሊዮን ብር ጨምሮ 20 ቢሊዮን ብር ለማድረስ ሐሳብ ከማቅረቡ ቀደም ብሎ አቅዶ የነበረው ካፒታሉን በ11 ቢሊዮን ብር ለማሳደግ ነበር፡፡ ሆኖም ከጥቂት ሳምንታት በፊት የባንኩ ቦርድ በዚህ ጉዳይ ላይ ተሰብስቦ በመምከር አዲስ የሚጨመረው ካፒታል መጠን 15 ቢሊዮን ብር እንዲሆን መወሰኑን ሪፖርተር ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡

ተጨማሪውን ካፒታል የአክሲዮን ክፍፍልና ሽያጭ በተመለከተም ተጨማሪውን 15 ቢሊዮን ብር በሁለት ዙር ሽያጭ በማከናወን አጠቃላይ ሽያጩን በአምስት ዓመት ውስጥ እንዲጠናቀቅ ውሳኔ ተላልፏል፡፡ ይህ ውሳኔ የሚተገበረውም ባንኩ አሁን ካለው የአምስት ቢሊዮን የተፈረመ ካፒታል ውስጥ ያልተከፈለው ቀሪ ገንዘብ ተከፍሎ ከተጠናቀቀ በኋላ እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል። የባንኩ የተፈረመ ካፒታል አምስት ቢሊዮን ብር ሲሆን ከዚህ ውስጥ 4.3 ቢሊዮን ብሩ የተከፈለ መሆኑን የባንኩ መረጃ ያመለክታል። ይህ እንደተጠናቀቀም የባንኩ ባለአክሲዮኖች ባላቸው የአክሲዮን መጠን የተደለደለላቸውን አዲስ አክሲዮን በመግዛትና በአምስት ዓመት ውስጥ ከፍለው በማጠናቀቅ የተጨመረውን 15 ቢሊዮን ብር ማሳካት ይጠበቅባቸዋል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ ባንኩ ከአስቸኳይ ጠቅላላ ጉባዔው ቀደም ብሎ በመደበኛ ጠቅላላ ጉበዔው የባንኩን የ2014 የሒሳብ ዓመት አፈጻጸም ይፋ አድርጓል፡፡ ከዓመታዊ የሥራ አፈጻጸሙ ሪፖርት መረዳት እንደተቻለው፣ ባንኩ በ2014 የሒሳብ ዓመት ከታክስ በፊት 1.8 ቢሊዮን ብር በላይ ትርፍ አስመዝግቧል፡፡ ሌሎች የሥራ አፈጻጸሞቹን በተመለከተ የቦርድ ሊቀመንበሩ እንደገለጹት፣ የባንኩ ጠቅላላ የተቀማጭ ገንዘብ መጠን ከቀደመው የሒሳብ ዓመት ጋር ሲነፃፀር የ9.98 ቢሊዮን ብር ወይም የ22.78 በመቶ ዕድገት በማሳየት 53.81 ቢሊዮን ብር ደርሷል፡፡ በሌላ በኩል ከወለድ ነፃ አገልግሎት ዘርፍ ባንኩ 2.45 ቢሊዮን ብር ተቀማጭ መሰብሰቡን ገልጸዋል፡፡ ይህም ካለፈው የሒሳብ ዓመት ውጤት ጋር ሲነፃፀር የ604.35 ሚሊዮን ብር ወይም 32.69 በመቶ ጭማሪ ያሳየ እንደሆነ አመልክተዋል፡፡

ባንኩ በሒሳብ ዓመቱ ለተለያዩ የኢኮኖሚ ዘርፎች የሰጠውን ብድር በተመለከተ፣ ከወለድ ነፃ የባንክ አገልግሎት ተጠቃሚዎች የተሰጠውን ብድር ጨምሮ በተለያየ ዘርፍ ተሰማርተው ለሚገኙ ለባንኩ ደንበኞች የተሰጠው አጠቃላይ የብድር ክምችት ካለፈው የሒሳብ ዓመት ጋር ሲነፃፀር የ10.06 ቢሊዮን ወይም የ28.03 በመቶ ዕድገት የታየበት ነው ተብሏል፡፡ እስከ 2014 ዓ.ም. መጨረሻ ድረስ የባንኩ የተከማቸ የብድር መጠን 45.9 ቢሊዮን ብር ደርሷል፡፡ ባንኩ በሒሳብ ዓመቱ ለብድር ካዋለው ገንዘብ 21.4 በመቶ የሚሆነው ለገቢ ንግድ የተሰጠ ሲሆን፣ የማንፉክቸሪንግ ዘርፍ 19.7 በመቶ ድርሻ፣ የአገር ውስጥ ንግድና አገልግሎት የ15.94 በመቶ ድርሻ ይዘዋል።

ባንኩ በሒሳብ ዓመቱ ያገኘው ውጭ ምንዛሪ ገቢ ከቀደመው ዓመት ያነሰ መሆኑን ሪፖርቱ ያመለክታል። ባንኩ በ2014 የሒሳብ ዓመት ከዓለም አቀፍ የባንክ አገልግሎት ዘርፍ 217.8 ሚሊዮን ዶላር ያገኘ ሲሆን፣ በ2013 የሒሳብ ዓመት ከተገኘው 253.1 ሚሊዮን ዶላር ጋር ሲነፃፀር የ13.9 በመቶ ቅናሽ ማሳየቱን ሪፖርቱ ይጠቁማል። የባንኩ የውጭ ምንዛሪ ገቢ ሊቀንስ የቻለው በሩሲያና በዩክሬን መካከል የተቀሰቀሰው ግጭት በዓለም ኢኮኖሚ ላይ የፈጠረው ተፅዕኖ በኢትዮጵያ ኢኮኖሚ፣ በተለይም በባንክ ዘርፉ አፈጻጸም ላይ ጫና በማሳደሩ እንደሆነ የቦርድ ሊቀመንበሩ ገልጸዋል፡፡

የባንኩ የ2014 የሒሳብ ዓመት ገቢ በ33.1 በመቶ ዕድገት በማሳየት፣ 8.1 ቢሊዮን ብር መድረሱንና ወጪው ደግሞ በ33.8 በመቶ በመጨመር 6.22 ቢሊዮን ብር መድረሱን መረጃው ያመለክታል።

በቦርድ ሊቀመንበሯ ሪፖርት በኋላ ከጠቅላላ ጉባዔው አባላት የተለያዩ አስተያየቶች የተሰጡ ሲሆን፣ ለመናገር ዕድል ከተሰጣቸው አብዛኛዎቹ ባለአክሲዮኖች የትርፍ ድርሻ ክፍፍል መጠን ላይ ቅሬታ ያላቸው መሆኑን አስታውቀዋል፡፡

ከኅብረት ባንክ ጋር አቻ ከሚባሉ ባንኮች ያነሰ የትርፍ ድርሻ እየሰጠ ነው በማለት ቅሬታ የተሰማቸው ባለአክሲዮኖች፣ የባንኩ አፈጻጸም አሁንም ጥሩ የሚባል ቢሆንም፣ ከትርፍ ድርሻ አንፃር የተገኘውን ውጤት እንዳላስደሰታቸው ተናግረዋል፡፡ ባንኩ 25 ዓመት በኢንዱስትሪው እንደመቆየቱ መጠን የትርፍ መጠኑም ሆነ የትርፍ ድርሻ ክፍፍሉ ከፍ ሊል ይገባው ነበር በማለት አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡

ለጥያቄዎቹ ምላሽ የሰጡት የባንኩ ፕሬዚዳንት አቶ መላኩ ከበደ፣ የዘንድሮ የትርፍ ድርሻ መጠን ከቀዳሚው ዓመት ብዙም ያልተለየበት ዋናው ምክንያት ከጦርነቱ ጋር በተያያዘ የብድር አመላለስ ላይ የፈጠረው ጫና ከሌላው ጊዜ በተለየ ከፍተኛ ፕሮቪዥን በመያዙ ነው ብለዋል፡፡ የባንኩ ካፒታል መጨመርም የትርፍ ድርሻ ክፍፍሉ ላይ የተወሰነ ተፅዕኖ እንደሚኖረው ጠቅሰዋል፡፡ ነገር ግን የባንኩን ትርፋማነት የበለጠ ለማሳደግ ባንኩ በርካታ ሥራዎችን እየሠራ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ባንኩ በሒሳብ ዓመቱ ከታክስ በፊት ያገኘው ትርፍ ከቀዳሚው ዓመት በ30.6 በመቶ ወይም 441.1 ሚሊዮን ብር ጭማሪ ማሳየቱ የተጠቀሰ ቢሆንም፣ በሒሳብ ዓመቱ አንድ አክሲዮን ያስገኘው ትርፍ ድርሻ መጠን ቅናሽ አሳይቷል። በዚህም መሠረት ባለፈው የሒሳብ ዓመት 28.8 ብር ያስገኘ አንድ አክሲዮን፣ ዘንድሮ 26.4 ብር አስገኝቷል።

ኅብረት ባንክ በአሁኑ ወቅት አጠቃላይ የሀብት መጠኑ በ13.3 ቢሊዮን ወይም በ24.6 በመቶ በመጨመር በ2014 ዓ.ም. መጨረሻ ላይ 67.4 ቢሊዮን ብር እንደደረሰ ተገልጿል፡፡ የባንኩ ጠቅላላ ካፒታልም በ2014 ዓ.ም. መጨረሻ ላይ 7.25 ቢሊዮን ብር እንደደረሰ የሚያመለክተው የባንኩ መረጃ የተከፈለ ካፒታል ደግሞ 4.3 ቢሊዮን ብር ደርሷል፡፡ የባንኩ የተከፈለ ካፒታል ከቀዳሚው ዓመት አንፃር ሲታይ የ10.9 በመቶ ዕድገት እንዳሳየ ታውቋል፡፡

በተጠናቀቀው የሒሳብ ዓመት 40 አዳዲስ ቅርንጫፎችን የከፈተው ኅብረት ባንክ፣ አጠቃላይ የቅርንጫፎቹን ቁጥር 423 ያደረሰ ሲሆን፣ የሠራተኞቹን ቁጥር ደግሞ 7,658 ነው፡፡

spot_img
- Advertisement -spot_img

የ ጋዜጠኛው ሌሎች ፅሁፎች

- ማስታወቂያ -

በብዛት ከተነበቡ ፅሁፎች