Wednesday, November 29, 2023
- Advertisment -
- Advertisment -

ዘረፋ የሚቆመው በተቋማዊ አሠራር እንጂ በዘመቻ አይደለም!

ኢትዮጵያ ውስጥ ሌብነት ከመንግሥት አቅም በላይ ሆኖ ለያዥ ለገናዥ ሲያስቸግር ከማየት በላይ አሰቃቂ ነገር የለም፡፡ በፌዴራል፣ በክልሎችና በከተማ አስተዳደሮች መረን የተለቀቀው ሌብነት አስነዋሪ መሆኑ ከተረሳ ዓመታት መቆጠራቸው ሲታሰብ ይደንቃል፡፡ ከዘመነ ኢሕአዴግ እስከ ዘመነ ብልፅግና ገዥ ፓርቲን ተጠግቶ መዝረፍና ማዘረፍ የተለመደው፣ በኢትዮጵያ ምድር ተቋማዊ አሠራር እንዳይኖር ተደርጎ በመዳፈኑ ነው፡፡ የፓርቲና የመንግሥት ሥራ እየተደበላለቁ ግልጽነትና ተጠያቂነት የጠፋው ተቋማት በመሽመድመዳቸው ነው፡፡ መንግሥት አደባባይ ወጥቶ ሌብነት ከላይ እስከ ታች ወርሶኛል ሲል፣ የፀረ ሌብነት እንቅስቃሴው በስፋትና በጥልቀት መከናወን ያለበት በዘመቻ ሳይሆን በተቋማዊ አሠራር መሆን አለበት፡፡ ፀረ ሙስና ብሔራዊ ኮሚቴ በማቋቋም በጥናት ላይ የተመሠረተ ዕርምጃ ለመውሰድ መታሰቡ መልካም ቢሆንም፣ ከኮሚቴው ይልቅ ከዚህ ቀደም የፖለቲካ መሣሪያ ሆኖ እንዲያገለግል ተፈርዶበት ከዚያም ውልቅልቁ የወጣውን የሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ጉልበት ሰጥቶ እንዲያንሰራራ ማድረግ ይሻላል፡፡ አገሪቱን እንደ ነቀዝ እየበላ ያለው የዝርፊያ ሠራዊት ጉልበቱ ጠንካራ ስለሆነ፣ ይህንን አደገኛ ኃይል መመከትና ማሸነፍ የሚቻለው በዘመቻ ሳይሆን በተቋማዊ አሠራር ብቻ ነው፡፡

መንግሥት በሕግ የተሰጠውን ኃላፊነት በአግባቡ እንዲወጣ የሚፈለግ ከሆነ፣ ለተቋማዊ አሠራር ትኩረት መስጠት ያስፈልጋል፡፡ ኢኮኖሚውን ለማሳደግ የሚያግዙ የልማት ሥራዎችን ለማከናወን፣ በማኅበራዊ መስክ ያሉ ዘርፈ ብዙ ችግሮችን ለመፍታት፣ ፖለቲካው ሥርዓት ኖሮት በአግባቡ እንዲመራ፣ ሰላምና ፀጥታ ለማስፈን፣ ሕገወጥ ድርጊቶችን ለመከላከል፣ በውጭ ግንኙነትና በዲፕሎማሲው መስክ የተሳካ ሥራ ለማከናወን፣ በመንግሥት ውስጥም ሆነ በሌሎች አካላት በስፋት የሚስተዋለውን ዝርፊያ ከምንጩ ለማድረቅ፣ ፍትሕ ለማስፈን፣ ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶችን ለማስከበር፣ ለሕዝቡ በበቂ መጠን አገልግሎት ለመስጠትና ለመሳሰሉት ተቋማዊ አሠራር ወሳኝ ነው፡፡ መንግሥት ሥራውን ሲያከናውን ግልጽነት፣ ተጠያቂነትና ኃላፊነት የሚባሉትን መርሆች በተግባር ማረጋገጥ የሚችለው ተቋማዊ የአሠራር ጥንካሬ ሲኖር ነው፡፡ መንግሥታዊ ተቋማት ከግለሰቦች ዕገታ ነፃ ሆነው በኃላፊነት ስሜት ተግባራቸውን ማከናወን የሚችሉት፣ ተቋማቱ በብቁ አመራሮችና ባለሙያዎች ተሟልተው ዘመኑን የሚመጥን ቁመና ሲኖራቸው ነው፡፡ መንግሥትም ሆነ ሌሎች የሚመለከታቸው አካላት በሙሉ ለተቋማዊ አሠራር ትኩረት ካልሰጡ፣ ማንኛውም ጥረት ‹‹ውኃ ቢወቅጡት እምቦጭ›› ነው የሚሆነው፡፡

ባለፈው ሳምንት ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በነበራቸው ቆይታ ካነሱዋቸው ጉዳዮች መካከል አንዱ፣ ኢትዮጵያ ውስጥ ሙስና አደገኛ እየሆነ መምጣቱን የሚመለከተው ተጠቃሽ ነው፡፡ በተለይ በመሬት ላይ እየተስተዋለ ባለው አደገኛ ድርጊት በተለምዶ መሬት የመንግሥትና የሕዝብ ነው የሚለውን የይስሙላ አባባል በመሻር፣ ‹‹…መሬት የሌባ ሹመኞችና የደላላ ነው›› በማለት ነበር የገለጹት፡፡ እሳቸው ይህንን ጉዳይ በጣም ከዘገየ በኋላ በማንሳት ማብራሪያ ቢሰጡበትም፣ መሬት ባለቤት አልባ የሆነ ይመስል በጠራራ ፀሐይ በጉልበተኞች እየተዘረፈ ጥቂቶች እየከበሩበት ስለመሆኑ ሰሚ ጠፍቶ ብዙ የተባለበት ነው፡፡ ከመሬት በተጨማሪም ዘረፋው ያልገባበት ሥፍራ የለም፡፡ የመንግሥትን በጀት በቡድን ከመዝረፍ ጀምሮ ለተፈናቃዮች የሚላክ ዕርዳታ አድራሻውን እስከ ማጥፋት ድረስ ያለው ውንብድና የታወቀ ነው፡፡ ግብር ማጭበርበርና መሰወር የሚከናወነው በመንግሥት ሹማምንት ዕውቅና ጭምር ነው፡፡ በመንግሥት የሚከናወኑ ፕሮጀክቶች መዘረፍ፣ ጥራት መጓደልና መዘግየት የሌብነቱ ሌላው መገለጫ ነው፡፡ አድሎአዊና አግላይ አሠራሮች የተበራከቱት ዘረፋው በኔትወርክ ስለሚከናወን ነው፡፡ ይህ ሁሉ የዘቀጠ ድርጊት የሚከናወነው ተቋማዊ አሠራር ባለመኖሩ ነው፡፡

ሰሞኑን ሙስናን ለመከላከል በጠቅላይ ሚኒስትሩ ብሔራዊ ኮሚቴ ተሰይሟል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባወጡት መግለጫ፣ ‹‹… ሙስና ዛሬ የአገራችን የደኅንነት ሥጋት ሆኗል፡፡ ወደ ብልፅግና የምናደርገውን ጉዞ እጅ ተወርች አስሮ ለመያዝ ከጠላቶቻችን እኩል ሙሰኛው እየታገለን ነው፡፡ የተስተካከለ ቢሮክራሲ፣ የተቀናጀ መዋቅርና ዘመናዊ አሠራር ለሙስና ተጋላጭነትን ስለሚቀንሱ፣ እነዚህን ለማጥፋት ወይም ለማሰናከል ሙሰኛው ቀን ከሌት እየሠራ ነው፡፡ ሕዝባችን በአገልግሎት አሰጣጥ፣ ከመሬት ጋር በተያያዙ አሠራሮች፣ በፋይናንስ ዘርፍ፣ በሽያጭና በግዥ ሒደቶች፣ በፍትሕ አደባባዮች፣ በተለያዩ የመንግሥት ተቋማት፣ በልማት ድርጅቶች፣ በሕዝብ ተቋማት፣ ወዘተ በሚያጋጥመው ሙስና እየተማረረ ነው፡፡ በተለያዩ ጊዜያት ከሕዝብ ጋር በተደረጉ ውይይቶች ከፀጥታ ሥጋቶች እኩል ሙስና የብልፅግና ጉዟችን ዋናው ዕንቅፋት መሆኑን አንስቷል…›› በማለት፣ መንግሥት በጉዳዩ ላይ ጥናት ማካሄዱንና ሌሎች ጉዳዮችንም ዘርዝረዋል፡፡ ሙስና በባህሪው ረቂቅ መሆኑን በመጠቆም፣ ከሕግና ከአሠራር ማሻሻያዎች በተጨማሪ ሙስናን እርም የሚያሰኝ ዕርምጃ አስፈላጊነትን አውስተዋል፡፡ የመንግሥትን ዘመቻ የሚያስተባብርና በጥናት ከተለዩት በተጨማሪ፣ ሌሎችን ተዋንያን ለይቶ ለሕግ የሚያቀርብ ሰባት አባላት ያሉት ብሔራዊ ኮሚቴ መቋቋሙን አስታውቀዋል፡፡

መንግሥት በዚህ መጠን ዘራፊዎች ላይ ለመዝመት ያሳየው ተነሳሽነት መልካም ሆኖ ሳለ፣ ነገር ግን ይህንን ተግባር በዘመቻ ለማከናወን ኮሚቴ ማቋቋሙ ችግሮች አሉበት፡፡ ከዚህ ቀደም የሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን የሚባል ተቋቁሞ ከእነ ችግሮቹም ቢሆን በርካታ ተግባራትን ሲያከናውን መቆየቱ ይታወሳል፡፡ ኮሚሽኑ በአዋጅ ተቋቁሞ በበርካታ ባለሙያዎች እየታገዘ ሥራውን ቢጀምርም፣ በመሀል ተቋማዊ ነፃነቱ ተገፎ የፖለቲካ መሣሪያ እንዲሆን መደረጉ አይዘነጋም፡፡ ቆይቶ ደግሞ የመመርመርና የመክሰስ ሕጋዊ ኃላፊነቱን ተገፎ የሥነ ምግባር አስተማሪና ሀብት መዝጋቢ መደረጉም አይረሳም፡፡ ኮሚሽኑ ያንን የመሰለ ገናና ስም ይዞ በአግባቡ ሥራውን እንዲሠራ ቢደረግ ኖሮ፣ ሊያስገኝ ይችል የነበረው ውጤት ቀላል እንደማይሆን ብዙዎችን ያስማማል፡፡ ነገር ግን በወቅቱ ገዥዎች ስላልተፈለገ ተሽመድምዶ ቀረ፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ ላቡን አንጠፍጥፎ በሚያፈራው ሀብት የተመሠረተ ተቋም ማስተካከያ ተደርጎለት፣ ብቁ አመራሮችና አስተማማኝ ባለሙያዎች ተመድበውለትና ጉልበት አግኝቶ ኃላፊነቱን እንዲወጣ ቢደረግ ከዘመቻ ሥራ ውስጥ መውጣት ይቻላል፡፡ አሁን የተመሠረተው ብሔራዊ ኮሚቴ አባላት የራሳቸው የማያፈናፍን ኃላፊነት ስላለባቸው ቢታሰብበት፡፡

የተቋማት ግንባታና ጥንካሬ ጉዳይ ሲነሳ በተለይ የአገር አንጡራ ሀብት ያለበት ሁኔታ በጣም ያሳስባል፡፡ ብዙዎቹ ተቋማት የግለሰቦችና የስብስቦች መጫወቻ የሚሆኑት፣ ተቋማት ዘመኑ ከሚፈልገው ዕሳቤ አኳያ ባለመደራጀታቸው ነው፡፡ ግልጽነትና ተጠያቂነት ሲጠፋ ሌብነትና ዝርፊያ መደበኛ ሥራ ይሆናሉ፡፡ ነገር ግን ይህንን አደገኛ ችግር ከሥሩ መንግሎ ለመጣል ወይም ደረጃ በደረጃ ለማስወገድ፣ ፀረ ሙስና ኮሚሽንን እንደገና በማደራጀት በብቁ የሰው ኃይል፣ በበጀት፣ በቴክኖሎጂና በጥንካሬ ማብቃት ጠቃሚ ነው፡፡ በጠቅላይ ሚኒስትሩ የተመሠረተው ብሔራዊ ኮሚቴ እንደ ቦርድ ወይም ተቆጣጣሪ አካል ሆኖ፣ የዕለት ተዕለት ሥራውን በከፍተኛ የኃላፊነት ስሜትና አደራ ኮሚሽኑ እንዲወጣ ቢደረግ ከዘመቻ ይልቅ ተቋማዊ አሠራር ማስፈን ይቻላል፡፡ ዘረፋን ከኢትዮጵያ ምድር ሥሩን ነቃቅሎ መጣል ከባድ ቢመስልም፣ አሠራሩ ተቋማዊና ዘመናዊ ሲሆን ግን ለማመን የሚያዳግት ውጤት ይገኝበታል፡፡ ዘረፋ የሚቆመው በተቋማዊ አሠራር እንጂ በዘመቻ አይደለም!

በብዛት የተነበቡ ፅሁፎች

- Advertisment -

ትኩስ ፅሁፎች

የመቃወም ነፃነት ውዝግብ በኢትዮጵያ

ስሟ እንዳይገለጽ የጠየቀችው በአዲስ አበባ ከተማ በተለምዶ የሾላ አካባቢ...

የሲሚንቶን እጥረትና ችግር ታሪክ ለማድረግ የተጀመረው አጓጊ ጥረት

በኢትዮጵያ በገበያ ውስጥ ለዓመታት ከፍተኛ ተግዳሮት በመሆን ከሚጠቀሱ ምርቶች...

የብሔር ፖለቲካው ጡዘት የእርስ በርስ ግጭት እንዳያባብስ ጥንቃቄ ይደረግ

በያሲን ባህሩ በሪፖርተር የኅዳር 9 ቀን 2016 ዓ.ም. ዕትም “እኔ...

ሀብቱንና ትርፉን እያሳደገ የቀጠለው አዋሽ ባንክ

አዋሽ ባንክ በአዲስ አበባ ከተማ አዲስ ዋና መሥሪያ ቤት...
spot_img

ተዛማጅ ፅሁፎች

ድጋፍና ተቃውሞ እኩል ይስተናገዱ!

ኢትዮጵያ ውስጥ ለረዥም ዓመታት ለመንግሥት ከሚቀርቡ ጥያቄዎች መካከል አንዱ የመብት መከበር ጉዳይ ነው፡፡ ዜጎች ተፈጥሯዊም ሆኑ ሕጋዊ መብቶቻቸው እንዲከበሩላቸው ለመንግሥት ጥያቄ ሲያቀርቡ፣ ጥያቄው የቀረበለት...

ፖለቲካዊ ችግሮች ፖለቲካዊ መፍትሔ ይፈለግላቸው!

መንግሥት ከኦነግ ሸኔ ጋር በታንዛኒያ ዳሬሰላም ከተማ ሲያካሂድ የነበረው ንግግር ያለ ውጤት መጠናቀቁን ካስታወቀ በኋላ፣ በኦሮሚያ ክልልም ሆነ በሌሎች ቦታዎች ሰላም ለማስፈን የነበረው ተስፋ...

ኢትዮጵያን ከግጭት ቀጣናነት ማላቀቅ የግድ ነው!

ፍሬ አልባ ፖለቲካዊ ልዩነቶች ወደ ግጭት እያመሩ ለአገርና ለሕዝብ የማያባራ መከራ ሲያቀባብሉ፣ ከትናንት ስህተቶች ለመማር ፈቃደኛ ያልሆኑ ፖለቲከኞችና ተከታዮቻቸው በእሳት ላይ ቤንዚን እያርከፈከፉ ጠማማ...