በአፄ ምኒልክ ዘመን ምንይዋብ የጨዋታ ፈላስፋ ነበሩ፡፡ ከዕለታት በአንዱ ቀን አፄ ምኒልክ›› በቆብ ላይ ልጅ ወልደሃል ሲሉ ሰምቻለሁ ልጅህ የታለ? በማለት ሲጠይቁዋቸው ምንይዋብ በማሾፍ መልክ ‹‹ዝኆን አደን ሄዷል›› በማለት መለሱላቸው፡፡ በዚህ ምክንያት ንጉሡ ተናደው ‹‹በጥፊ በሉልኝ›› ብለው በጥፊ አስመቷቸው፡፡ በዚህን ጊዜ ምንይዋብ ‹‹ምነው የኔታ ምኒልክ ቆላ ባጠፋ ደጋ መወረሩ›› አሉ ይባላል/ብልቴ ባጠፋ ፊቴ መመታቱ ለማለት ነው/፡፡
በዚህ የተነሳ ታዲያ ንጉሡ ወህኒ ቤት አስገቡዋቸው፡፡ ትንሽ ቆይተው ‹‹በስሜ እንጀራ ይብላ›› ብለው ፈቷቸው፡፡ በዚህን ጊዜ ምንይዋብ በየመኳንንቱ ቤት እየዞሩ ‹‹ስለ ቅዱስ ምኒልክ›› እያሉ ይለምኑ ጀመር፡፡ በዚህ አድራጎታቸው በድጋሚ ተይዘው እንጉሡ ፊት ቀረቡ፡፡ አፄ ምኒልክም ‹‹ምነው አንተ የመኳንንት መሳቂያ አደረግኸኝ?›› ሲሏቸው ‹‹ልማዳችን ስለማርያም ስለአቦ ነበር ነገር ግን ጃንሆይ በስሜ እንጀራ ይብላ ብለውሃል አሉኝ ከዚያ ወዲያ ምን ልበል?›› ብለው ንጉሡን አሳቁአቸው ይባላል፡፡
- ካሕሣይ ገብረእግዚአብሔር ‹‹ኅብረ-ብዕር ሦስተኛ›› (2009)