ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) ቤተ መንግሥት የያዘ “የጫካ ሃውስ” የተሰኘ ፕሮጀክት እየተከናወነ መሆኑን አረጋገጡ፡፡
በመንግሥት ሊገነባ የታሰበው “የጫካ ሃውስ” ፕሮጀክት “ሳተላይት ሲቲ” እንደሆነ ገልጸው፣ ፕሮጀክቱ ከቤተ መንግሥት በተጨማሪ “በሺሕ የሚቆጠሩ” ቤቶችንና ሆቴሎችን እንደሚይዝ አስታውቀዋል፡፡ እስከ 500 ቢሊዮን ብር ለሚደርሰው የ”ሳተላይት ሲቲ” ግንባታ የሚሆን በጀት በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንደማያስመድቡም ለምክር ቤቱ አባላት ተናግረዋል፡፡
በእንግሊዝኛው ዘ ሪፖርተር ጋዜጣ በግንቦት ወር 2014 ዓ.ም. “የጫካ ፕሮጀክት” በሚል ስያሜ በ49 ቢሊዮን ብር ቤተ መንግሥት እየተገነባ መሆኑ መዘገቡ ይታወሳል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ቤተ መንግሥትን የያዘ ፕሮጀክት እየተከናወነ መሆኑን አረጋግጠው፣ ‹‹ጠቅላይ ሚኒስትሩ ቤተ መንግሥት በ49 ቢሊዮን ብር እየገነቡ ነው [ተብሏል]፣ [ጠቅላይ ሚኒስትሩ] እየገነቡ ነው [ነገር ግን] በ49 [ቢሊዮን ብር] ሳይሆን በ400 እና በ500 ቢሊዮን [ብር] ነው የሚገነቡት፤›› ብለዋል፡፡
ማክሰኞ ኅዳር 6 ቀን 2015 ዓ.ም. በምክር ቤቱ ስድስተኛ ዙር አንደኛ ዓመት አራተኛ መደበኛ ስብሰባ ላይ የተገኙት ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ (ዶ/ር)፣ የመንግሥትን የ2015 ዓ.ም. የትኩረት አቅጣጫና ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ከምክር ቤቱ አባላት ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡
በጉባዔው ላይ ከሥራ ዕድል ፈጠራ ጋር በተያያዘ ለተነሱ ጥያቄዎች ምላሽ ከሰጡ በኋላ፣ ከምክር ቤት አባላቱ ጥያቄ ባይነሳበትም “ከቤተ መንግሥት ግንባታ” ጋር በተያያዘ የተለያዩ ሐሳቦች እንደሚነሱ ገልጸው ማብራሪያውን ሰጥተዋል፡፡
‹‹ልንገነባ ያሰብነው የጫካ ሃውስ ይባላል፤›› ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ፕሮጀክቱ “እጅግ ዘመናዊ” መሆኑን ገልጸው፣ “የኢትዮጵያ ቤት” ሲሉ ጠርተውታል፡፡ እስከ 500 ቢሊዮን ብር ይወጣበታል ለተባለው “የሳተላይት ሲቲ” ግንባታ የሚውለውን በጀት፣ ‹‹ለምነን ሪሶስር አምጥተን እንሠራለን፤›› በማለት ከምክር ቤቱ የበጀት ምደባ እንደማይጠይቁ አስታውቀዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ‹‹ያ ፕሮጀክት ቢያንስ ቢያንስ ሁለት ቢሊዮን ዶላር እንዲያመጣና በአንድ ቢሊዮን ተኩል ዶላር አካባቢውን ገንብተን ትርፍ ልናተርፍበት እንጂ፣ ፓርላማ መጥተን እባካችሁ ቤተ መንግሥት የምንገነባበት 49 ቢሊዮን ብር ስጡን ለማለት አይደለም፣ አልጠየቅናችሁም፣ አንጠይቃችሁም፤›› ሲሉም አብራርተዋል፡፡
በመሬት አቀማመጡ ከፍታና ጫካ በሚገኝበት ሥፍራ ላይ የሚገነባው “ሳተላይት ሲቲ” የግንባታ ፕሮጀክት፣ ከአሁኑ “ሽኩቻ” እንዳጋጠመው ዓብይ (ዶ/ር) ተናግረዋል፡፡ ‹‹አሁን ለምን ሽኩቻው መጣ? 49 [ቢሊዮን ብር] ከየት መጣ? ስትሉ ጫካና ከፍ ያለ ቦታ ላይ ነው ያለው፡፡ እኛ ሥር ኤምባሲዎች አሉ፡፡ አኮረፉ ሊያዩን ነው ብለው፤›› ብለው በስም ያልጠቀሷቸው የውጭ አገሮች ኤምባሲዎች ቅሬታ እንደተሰማቸው ገልጸዋል፡፡ ነገር ግን ግንባታው ፕሮጀክቱ ከሚገኝበት ቦታ ሥር የሚገኙ ኤምባሲዎች፣ ‹‹የማይታዩበትና ችግር የማይፈጠርበት መንገድ›› ተፈጥሮ እንደሚካሄድ ተናግረዋል፡፡
‹‹ሥራው ሲያልቅ ግን የኢትዮጵያ ቤት እንጂ የመንግሥት ቤት አይደለም፡፡ የኢትዮጵያን ቤት ነው የምንገነባው፡፡ ፓርላማው ከፈለገ ትንሽ ጊዜ ይስጠንና በአካል እናየዋለን፡፡ እዩትና ትመሰክራላችሁ፤›› ሲሉ፣ የምክር ቤቱ አባላትም በጭብጨባ ድጋፋቸውን ገልጸዋል፡፡
“የጫካ ሃውስ” የተባለው ፕሮጀክት ማሳያ ሞዴል እንደሚሆንና ሌሎች ከተሞችም ፕሮጀክቱን “ያስፋፉታል” የሚል ተስፋ እንዳላቸው ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ (ዶ/ር) ተናግረዋል፡፡
ሪፖርተር ሥለ “የጫካ ሃውስ” ፕሮጀክት ያገኛቸው መረጃዎች እንደሚያመላክቱት፣ ፕሮጀክቱ የሚከናወነው በ503 ሔክታር መሬት ላይ ሲሆን፣ ከየካ ክፍለ ከተማ አምስት ወረዳዎችን ይነካል፡፡ ግንባታው ሰው ሠራሽ ሐይቆችን ጨምሮ የተለያዩ መሠረተ ልማቶችን እንደሚያካትትም የሪፖርተር ምንጮች ተናግረዋል፡፡ የኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር ፕሮጀክቱ ለሚያካትታቸው አካባቢዎች መገናኛ የሚሆን 20 ኪሎ ሜትር መንገድ ግንባታ እንደጀመረም ተገልጿል፡፡