- የተመድና የአውሮፓ ኅብረት አበርክቶ አሉታዊ እንደነበር ጠቁመዋል
በመንግሥትና በሕወሓት መካከል በደቡብ አፍሪካ የተካሄደው የሰላም ድርድር እንዲሳካና ስምምነት ላይ እንዲደረስ፣ የአሜሪካ መንግሥት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን፣ የኢትዮጵያ መንግሥትን የወከለው ተደራደሪ ቡድን መሪና የጠቅላይ ሚኒስትሩ የብሔራዊ ደኅንነት አማካሪ ሬድዋን ሁሴን (አምባሳደር) አስታወቁ።
ሬድዋን (አምባሳደር) እሑድ ጥቅምት 27 ቀን 2015 ዓ.ም. ከሕወሓት ጋር የተካሄደውን የድርድር ሒደትና የተፈረመውን የሰላም ሰምምነት ይዘቶች የተመለከተ ማብራሪያ፣ መቀመጫቸውን አዲስ አበባ ላደረጉ የውጭ ዲፕሎማቶች ሰጥተዋል። በማብራሪያቸው ማጠናቀቂያ ላይም የውጭ መንግሥታትና ዓለም አቀፍ ተቋማት ለሰላም ሒደቱ ያበረከቱትን አወንታዊና አሉታዊ አስተዋጽኦ ተናግረዋል።
በዚህም መሠረት የአሜሪካ መንግሥት ለድርድሩ ስኬታማነት ከፍተኛ ሚና መጫወቱን የጠቀሱት ሬድዋን (አምባሳደር)፣ ‹‹የአሜሪካ መንግሥት ሕወሓትን በማሳመን፣ በመጫን፣ እንዲሁም ወደ ድርድሩ እንዲመጣ ወሳኝ ሚና ነበረው፡፡ ለዚህም ለአሜሪካ መንግሥት ትልቅ ምሥጋና አለን፤›› ብለዋል።
በደቡብ አፍሪካ በተካሄደው ድርድር በታዛቢነት የተሳተፉት ኢጋድ፣ አሜሪካና የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ሲሆኑ፣ በዚህ የሰላም ሒደት ላይ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) ሚና አሉታዊ እንደነበር ገልጸዋል።
የአዉሮፓ ህብረትን በመወከል ድርድሩን የታዘቡት የተመድ የአፍሪካ ቀንድ ተወካይ አኔት ዌበር መሆናቸውን የጠቀሱት ሬድዋን (አምባሳደር)፣ የኢትዮጵያ መንግሥት የተወካይዋን የግል ጥረት እንደሚያደንቅ ገልጸዋል።
‹‹ከተወካይዋ ጋር ችግር የለንም። በግላቸው ያደረጉትን ጥረት እናደንቃለን። ተወካይዋ በድርድሩ አዎንታዊ ሚና ማበርከት ያልቻሉት ከአቅማቸው በላይ የሆነ ጫና ከበስተኋላ ተደርጎባቸው ሊሆን ይችላል፤›› ብለዋል።
የአውሮፓ ኅብረት በድርድሩ የታዛቢነት ሚና ባይኖረውም በኢትዮጵያ መንግሥት ላይ ከፍተኛ ጫና ሲያደርግ እንደነበር የጠቀሱት ሬድዋን (አምባሳደር)፣ የአውሮፓ ኅብረት በነበረው አጠቃላይ አሉታዊ ሚና የኢትዮጵያ መንግሥት ቅሬታ እንዳለው፣ ነገር ግን ከኅብረቱ ጋር ስትራቴጂካዊ ግንኙነታቸው እንዲቀጥል የመንግሥት ፍላጎት መሆኑን ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ መንግሥት በአውሮፓ ኅብረት ላይ እንደ ተቋም ቅሬታ እንደሌለው ገልጸው፣ ችግር እየፈጠረ ያለው አንድ የአውሮፓ ኅብረት አባል አገር ብቻ እንደሆነ ጠቁመዋል።
በስም ያልጠቀሱት ይህ የአውሮፓ ኅብረት አባል አገር አሁንም የሰላም ስምምነቱ አይሳካም የሚል እምነት እያራመደ እንደሚገኝም ተናግረዋል። ከዚህ አንድ የአውሮፓ ኅብረት አባል አገር ጋር ያለውን አለመግባባት ለመፍታት የኢትዮጵያ መንግሥት እንደሚሠራም አክለዋል።
ሬድዋን (አምባሳደር) በሰላም ሒደቱ ላይ አሉታዊ ሚና ነበረው ያሉትን የአውሮፓ ኅብረት አባል አገር በስም ባይገልጹም፣ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኰንን ከጥቂት ሳምንታት በፊት ለአየርላንድ አቻቸው በጻፉት ደብዳቤ፣ የአየርላንድ መንግሥት በኢትዮጵያና በአውሮፓ ኅብረት መካከል ያለውን ግንኙነት እያወከ እንደሆነ በመጥቀስ መውቀሳቸው ይታወሳል።