የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን የ30 ኪሎ ሜትር የጎዳና ውድድርን፣ እሑድ ጥቅምት 27 ቀን 2015 ዓ.ም. በቢሾፍቱ ከተማ ያከናውናል፡፡
ዓመታዊው ውድድር ለክልሎችና ለከተሞች ለክለቦችና ለግል ተወዳዳሪዎች ዕድል ለመፍጠርና ተተኪ አትሌቶችን ለማፍራት የተዘጋጀ መሆኑን ፌዴሬሽኑ ገልጿል፡፡
ለውድድሩ 100 ሴቶችና 304 ወንዶች፣ በአጠቃላይ 404 አትሌቶች መመዝገባቸውን ብሔራዊ ፌዴሬሽኑ በጋዜጣዊ መግለጫው አስታውቋል፡፡
ከዓመት ዓመት የተሳታፊ ቁጥር እየጨመረ መመጣቱን ያስታወቀው ፌዴሬሽኑ፣ በተለያዩ ዓለም አቀፍ የጎዳና ውድድሮች ላይ ለመሳተፍ እየተዘጋጁ ላሉ አትሌቶች መልካም አጋጣሚን ፈጥሯል ብሏል፡፡
በውድድሩ ላይ ከሚሳተፉ ታዋቂ አትሌቶች መካከል የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሯጮች ሙሌ ዋሲሁንና ፋንታሁን ሁነኛ፣ ከኦሮሚያ ፖሊስ ጠበሉ ዘውዴና ብርሃኑ በቀለ፣ ከመቻል ልመንህ ጌታቸው፣ ከኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይለ ማርያም ኪሮስና ባየልኝ ተሻገር ይገኙበታል፡፡ በሴቶች ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሕይወት ገብረ ኪዳንና ሶፊያ ሸምሱ፣ ከኦሮሚያ ፖሊስ አፀደ ባይሳና ትዕግሥት በቀለ፣ ከሲዳማ ፖሊስ ታዱ ተሾመና ባሻንቄ ሙሴ፣ ከፌዴራል ፖሊስ መገርቱ ገመቹ፣ ከመቻል ብሩክ ታምሬና ከአማራ ማረሚያ አገሬ በላቸው እንደሚካፈሉበት ታውቋል፡፡
ማንኛውም የማራቶን ተወዳዳሪ እንዲሁም ዕድሜው 18 ዓመትና ከዚያ በላይ የሆነ ማንኛውም አትሌት መወዳደር እንደሚችል በጋዜጣዊ መግለጫው ተጠቅሷል፡፡
ውድድሩን ለማካሄድ ዳኞች፣ የፌዴሬሽኑ ሠራተኞች፣ በጎ ፈቃደኞች፣ የጉልበት ሠራተኞችና አስተባባሪዎችን ጨምሮ 160 ሰዎች እንደሚሳተፉበት ተገልጿል፡፡
በሁሉም ምድብ ከአንደኛ እስከ ሦስተኛ ለሚወጡ አትሌቶች የወርቅ፣ የብርና የነሐስ ሜዳሊያ ከመሸለማቸው በተጨማሪ፣ እነሱን ጨምሮ እስከ ስምንተኛ የሚወጡ ገንዘብ ይሸለማሉ፡፡ ለሽልማቱ የተመደበው ገንዘብ 780 ሺሕ ብር ነው፡፡
በ2001 ዓ.ም. በአዳማ ከተማ የመጀመርያው ውድድር የተከናወነ ሲሆን፣ እስከ 2003 ዓ.ም. ለተከታታይ ዓመታት በዚያው ከተማ ሲካሄድ ቆይቷል፡፡ እስከ 2010 ዓ.ም. ድረስ ውድድሩ ተቋርጦ በድጋሚ አራተኛውንና አምስተኛውን ውድድር በቢሾፍቱ ከተማ እንዲቀጥል ተደርጓል፡፡