ቀደም ብሎ በውጪ አገር የፊዚክስ ድኅረ ምረቃ ተማሪ የነበረና በአዕምሮ መታወክ የተነሳ ትምህርቱን ያቋረጠ፣ አንድ ገላጭ ንድፈ ሐሳብ ይዞ ቀረበ። ይኸውም እንዲህ የሚል ነው፣ ‹‹ሙቀትን የሚፈጥሩት ‘የማክስዌል ዲመንስ’ ወይም አጋንንት መሆናቸው ይታወቃል፡፡ ሆኖም ቅዝቃዜ የተከሰተው አጋንንቱ ተፈላጊውን የእርግብግቦሽ መጠን መስጠት ባለመቻላቸው ነው። ይህም የሆነው በአጋንንቱ ኢነርጂ ማጣት፣ የተመጣጠነ ምግብ አለማግኘት ነው። በዚህም የተነሳ ለአጋንንት የሚከተለውን ጥሪ አቅርበናል›› ይላል ወጣቱ፣ ‹‹አጋንንት ሆይ! ባላችሁበት፣ በአየሩ፣ በባህሩ፣ በምድሩ፣ መልዕክቴ ይድረሳችሁ። ይህን መፈክር አንግባችሁ ተነሱ፣ ‹‹ጭቆና ይብቃ! ብጣሽ ጥብሳ ጥብስ ይወረወርልናል፣ ምግባችን አምድና አተላ ነው! ይህ መቆም አለበት፣ እኛም ዕድል ይድረሰንና ከማዕዱ እንቅረብ! እስከ መቼ እንደ ሁለተኛ ዜጋ እንታያለን? እኛም እኮ እንራባለን፣ እንጠማለን፣ እንታረዛለን፣ እኛ አስታዋሽ ያጣን ሕዝቦች ነን፣ እስቲ ተመልከቱት፣ የሰው ልጆች ትምህርት ቤት ገብተው ፊደል ይቆጥራሉ፣ የእኛ ልጆች ሙያ ተምረው አገራቸውንና እራሳቸውን ለመደገፍ ይጥራሉ፣ የኛዎቹ ሙያቸው ክፋት፣ ችግር፣ ጥፋት ነው። ይህ ሁኔታ እንደዚህ ከቀጠለ የዘለአለም ፀፀት ሊከሰት ይችላል! ነፃነት፣ እኩልነት፣ ወንድማማችነት! የዓለም ጭቁን አጋንንት ተባበሩ! እናሸንፋለን!››
– ግርማ ሙልኢሣ ‹‹ለጭውውት ያህል›› (ክብሩ ቡክስ)