በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል አሶሳ ዞን ውስጥ የሚገኘው ባምባሲ ወረዳ፣ በአጎራባቹ የኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ወለጋ ዞን ውስጥ በሚንቀሳቀሰው ‹‹ኦነግ ሸኔ›› ሥጋት ምክንያት የሰዓት ዕላፊ ተጣለ፡፡
የሰዓት ዕላፊው የተጣለው ወረዳው የሥጋት ቀጣና ከሆኑ አካባቢዎች ጋር ተጎራባች በመሆኑ በተፈጠረ የፀጥታ ሥጋት መሆኑን የወረዳ አስተዳደሩ የገለጹ ሲሆን፣ ባምባሲ ወረዳ የ‹‹ኦነግ ሸኔ›› ትኩረት ያደረገበት አካባቢ ስለመሆኑ አንዳንድ ተጨባጭ ማሳያዎች በመኖራቸው መሆኑን አስታውቋል፡፡
የኦነግ ሸኔ ኃይሎች በምዕራብ ወለጋ ዞን ውስጥ 45 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ጦርነት መክፈታቸውን የወረዳው የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ቡድን መሪ አቶ ጥላሁን ጌታቸው ለሪፖርተር ተናግረው፣ የሰዓት ገደቡ የተጣለው ሰርጎ ገቦች ወደ ወረዳው እንዳይገቡ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
‹‹ጦርነት ከፍቶ ነበር አልተሳካለትም፤›› ያሉት የቡድን ኃላፊው፣ ቡድኑ ጥቃቱን የከፈተው ሰኞ ጥቅምት 21 ቀን 2015 ዓ.ም. ከጠዋቱ 3፡00 ሰዓት አካባቢ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ታጣቂዎቹ በምዕራብ ወለጋ ዞን ቤንጓ አካባቢ በከፈቱት ጥቃት ዞኑን ከአሶሳ ዞን ባምባሲ ወረዳ የሚያገናኘው የዳቦስ ወንዝ ድልድይ በመጣስ ወደ ወረዳው የመግባት ዓላማ እንደነበራቸው ተናግረዋል፡፡ ታጣቂዎቹ ወደ ድልድዩ ቀርበው ጥቃት ከከፈቱ በኋላ፣ በተደረገው ውጊያ የተኩስ ድምፅ ይሰማ እንደነበርም አክለዋል፡፡
ይሁንና በድልድዩ አካባቢ የሠፈሩት የፌዴራል ፖሊስና የክልል ልዩ ኃይሎች በወሰዱት ዕርምጃ ጥቃቱ መገታቱን አስታውቀዋል፡፡ ታጣቂዎቹ ሲመቱ መሣሪያቸውን ጥለው፣ ልብስ ለብሰው ጥናት ለማጥናት ይገባሉ፤›› ሲሉም በወረዳው የሰዓት ዕላፊ የተጣለበትን ምክንያት አስረድተዋል፡፡
ከሰኞ ጥቅምት 21 ቀን 2015 ዓ.ም. አንስቶ በተጣለው ሰዓት ዕላፊ ከምሽቱ 1፡00 ሰዓት እስከ ንጋት 12፡00 ሰዓት ድረስ ማንኛውም ተሽከርካሪ እንዳይንቀሳቀስ መከልከሉን አስረድተዋል፡፡ ለፀጥታ ሥራ ከሚንቀሳቀሱና ወላድ ከሚያንቀሳቅሱ አምቡላንሶች በእነዚህ ሰዓታት ውስጥ መንቀሳቀስ የተፈቀደላቸው ሲሆን፣ ከዚህ ውጪ ያሉ ተሽከርካሪዎች ለመንቀሳቀስ ከወረዳ አስተዳደሩ ፈቃድ ማግኘት በግዴታነት ተቀምጦባቸዋል፡፡ እንደ ሆቴል፣ ሬስቶራንት፣ መጠጥ ቤት ያሉ ሕዝብ የሚሰበሰብባቸው ቦታዎችም ከምሽቱ አንድ ሰዓት ጀምሮ አገልግሎት እንዳይሰጡ ክልከላ ከተጣለባቸው ውስጥ ናቸው፡፡
በወረዳው ከተመደበው መደበኛ ሠራዊት ውጪ ማንኛውም የፀጥታ አካል፣ የተጣለውን የሰዓት ዕላፊ ገደብ አልፎ ሲንቀሳቀስ ከተገኘ በቁጥጥር ሥር እንደሚውል ወረዳው አስጠንቅቋል፡፡
የወረዳው መንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ቡድን መሪ አቶ ጥላሁን እንደሚናገሩት፣ ከሰኞ ጀምሮ ተግባራዊ መሆን የጀመረው የሰዓት ዕላፊ የተጣለው ጎረቤት አካባቢዎች እስከሚረጋጉ በሚል ሲሆን፣ የሰዓት ዕላፊው እስከ መቼ እንደሚቆይ የጊዜ ገደብ አልተቀመጠም፡፡