በስምንት ክልሎች በሚገኙ 44 ወረዳዎች ውስጥ በ22 ሚሊዮን ዶላር ተግባራዊ የሚሆንና በእናቶችና ሕፃናት ጤና ላይ የሚያተኩር የመጀመርያ ደረጃ ጤና ክብካቤ አገልግሎት ማሻሻያ ፕሮጀክት ይፋ ሆነ፡፡
አርብቶ አደሮች፣ ከፊል አርብቶ አደሮችና አርሶ አደሮች ባሉበት በእነዚሁ ወረዳዎች ፕሮጀክቱ ተግባራዊ የሚሆነው አምሪፍ ሔልዝ እና ጄኤስአይ በተባሉ አጋር ድርጅቶች ቅንጅት ነው፡፡
እንደ ጤና ሚኒስቴር ፕሮጀክቱ በመጪዎቹ ሁለት ዓመታት በተመረጡ 14 ወረዳዎች የሚተገበር ሲሆን፣ ቀጥሎ በሚኖሩት አምስት ዓመታት ውስጥ ደግሞ በ30 ወረዳዎች ላይ ተግባራዊ ይሆናል፡፡
የአምሪፍ ሔልዝ አፍሪካ ምክትል ዳይሬክተር ስንታየሁ ፀጋዬ (ዶ/ር) የፕሮጀክቱን ተግባራዊ መሆን አስመልክተው እንዳሉት፣ በአገር አቀፍ ደረጃ መንግሥት በጤናው ዘርፍ በዋናነትም የመጀመርያ ደረጃ ጤና ክብካቤ አገልግሎትን ለማሻሻል እያከናወናቸው ላሉት ተግባራት የበኩሉን ዕገዛ ያደርጋል፡፡
የአምሪፍ ሔልዝ አፍሪካ የመጀመርያ ደረጃ ጤና ክብካቤ ዳይሬክተር አቶ ተመስገን አየሁ በበኩላቸው፣ ፕሮጀክቱ በእናቶችና ሕፃናት ጤና ላይ እንደሚያተኩርና በዚህም የኅብረተሰቡን መደጋገፍ እንደሚያጠናክር ገልጸዋል፡፡
ፕሮጀክቱ ይፋ ሲሆን የተገኙት የጤና ሚኒስትር ሊያ ታደሰ (ዶ/ር) ፕሮጀክቱ ከዓመት በፊት ፀድቆ ወደ ሥራ የገባውን የጤና ኤክስቴንሽን ፍኖተ ካርታ እንደሚያግዝ አስረድተዋል፡፡
ፕሮጀክት ይፋ የሆነው በሐዋሳ ከተማ ጥቅምት 10 እና 11 ቀን 2015 ዓ.ም. በተካሄደው 24ኛው ዓመታዊ የጤና ጉባዔ ላይ ነው፡፡