ዲኤስቲቪ የተመልካች ቁጥር እንዲጨምር ለአክሲዮን ማኅበሩ የቤት ሥራ ሰጥቷል
የቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ጨዋታን ለመመልከት ስታዲየም የሚገቡ ተመልካቾች ቁጥር ማነስ፣ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አክሲዮን ማኅበር እንዳሳሰበው አስታወቀ፡፡ በባህር ዳር ስታዲየም እየተከናወነ በሚገኙ ጨዋታዎች ላይ ለመመልከት የሚገቡ ተመልካቾች ቁጥር የተጠበቀውን ያህል እንዳልነበረና ውድድሩን እንዳደበዘዘው የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አክሲዮን ማኅበር ሥራ አስኪያጅ አቶ ክፍሌ ሰይፈ ለሪፖርተር አስረድተዋል፡፡
ውድድሩ የሚከናወኑባቸው ከተሞች ለተመልካቾች ቅርብ አለመሆናቸው ዋንኛ መንስዔ መሆኑን የሚጠቅሱት ዋና ሥራ አስኪያጁ በተለይ የአዲስ አበባ ስታዲየም ግንባታ መጓተት ሌላኛው ተጠቃሽ ምክንያት መሆኑን ያስረዳሉ፡፡
እንድ አቶ ክፍሌ አስተያየት ከሆነ የአዲስ አበባ ስታዲም ግንባት ሒደት እየተከናወነ መሆኑን አስረድተው ግንባታው በታቀደበት ጊዜ ከተጠናቀቀ አብዛኛዎቹን የሊጉን መርሐ ግብሮች በአዲስ አበባ ለማድረግ ውጥን እንዳላቸው አክለዋል፡፡
ጨዋታዎቹ በአዲስ አበባ መሆናቸው ለበርካታ ተመልካቾች ቅርብ ከመሆናቸው አንፃር ያጋጠመውን የተመልካች እጥረት በጥቂቱም ቢሆን ይፈታዋል የሚል ዕምነት እንዳለቸው አቶ ክፍሌ ለሪፖርተር ጠቁመዋል፡፡
ውድድሩን በቀጥታ የማስተላለፍ መብት ያለው ዲኤስቲቪ አክሲዮን ማኅበሩ ቁጥሩን ለመጨመር የቤት ሥራውን እንዲወጣ ሐሳብ ማቀረቡን አቶ ክፍሌ ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡ በተለያዩ ከተሞች እየተዘዋወረ የሚከናወነው ቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የአምስተኛ ሳምንት መርሐ ግብሩን ቢዘህ ሳምንት በባህር ዳር አጠናቆ ከጥቅምት 25 ጀምሮ ከስድስተኛ እስከ አሥረኛ ሳምንታት በድሬዳዋ ይከናወናል፡፡
ሁለተኛውን ዙር የማሰናዳት ዕድል ያገኘው የድሬዳዋ ከተማ ዝግጅት እያደረገ መሆኑ የተገለጸ ሲሆን፣ የስታዲየም ጥገና፣ አርቴፊሻል ሜዳዎች፣ ኤሌክትሮንክ ማስታወቂያዎችና ለመወዳደሪያ ሥፈራ የሚሆኑ ቁሳቁስ ያሟሉትን ክለቦች እየተጠባበቁ መገኘታቸውንና አክሲዮን ማኅበሩ ክትትል እያደረገ እንደሚገኘ አቶ ክፍሌ አብራርተዋል፡፡