በኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት ለሦስት ዓመታት ያህል ተቋርጦ የነበረው የኢትዮጵያና የጂቡቲ የጋራ የሚኒስትሮች ኮሚሽን ስብሰባ በአዲስ አበባ መካሄድ ጀመረ፡፡
የሁለቱ አገሮች የጋራ የሚኒስትሮች ኮሚሽን ስብሰባ እ.ኤ.አ. በ2019 ለ15ኛ ጊዜ በጂቡቲ ቢካሄድም፣ ከሦስት ዓመታት ቆይታ በኋላ ከጥቅምት 15 እሰክ 17 ቀን 2015 ዓ.ም. በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው፡፡
በስብሰባው በዓመት ከ20 ቢሊዮን ዶላር በላይ የኢኮኖሚ ግንኙነት ያላቸውን ሁለቱን አገሮች የሚመለከቱ በርካታ ጉዳዮችን የሚዳስስ ነው፡፡ ለአብነት ያህል በትራንስፖርት፣ በንግድ፣ በፋይናንስ፣ በሎጂስቲክስ፣ በሰዎች ዝውውር፣ በፖለቲካ፣ በዲፕሎማሲ፣ እንዲሁም በሌሎች ዘርፎች ላይ ውይይት እንደሚደረግ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአፍሪካ ጉዳዮች ዳይሬክተር ፍሰሐ ሻውል (አምባሳደር) ተናግረዋል፡፡
በኢትዮጵያና ጂቡቲ መካከል ያለው ግንኙነት ስትራቴጂካዊ መሆኑን ያስረዱት ዳይሬክተሩ፣ በሁለት ቀናት ውስጥ ኮሚሽኑ ባቋቋመው የቴክኒክ ኮሚቴ አማካይነት ከዚህ በፊት ስምምነት የተደረሰባቸውንና አሁን መስተካከል የሚገባቸውን ጉዳዮች ከተወያየ በኋላ፣ ውሳኔ ሊደረስባቸው የሚገቡ ጉዳዮችን በመለየት፣ ነገ ሐሙስ ጥቅምት 17 ቀን 2015 ዓ.ም. ሚኒስትሮች በተገኙበት በሚደረገው የመዝጊያ ስብሰባ ውሳኔ ይሰጥባቸዋል ብለዋል፡፡
ከጥቂት ዓመታት በፊት ሁለቱን አገሮች በኢኮኖሚ ለማዋሀድ የተጀመረ እንቅስቃሴ እንደነበረ አስታውሰው፣ በቀጣናው ሕወሓት ሁኔታዎችን ለማበላሸት የጀመረው ድርጊት ከተስተካከለና ከጠራ በኋላ፣ ሁለቱ አገሮች ይበልጥ በኢኮኖሚ የሚዋሀዱበት ሁኔታን ለመፍጠር እንደሚሠራ ዳይሬክተሩ አስረድተዋል፡፡
ከኢትዮጵያ ወደ ጂቡቲ የሚያመራው መንገድ ምንም እንኳ የሕወሓት ታጣቂዎች ጥቃት እንዳይፈጽሙበት ከዚህ በፊ ሥጋት የነበረ ቢሆንም፣ አሁን ግን የትራንስፖርት እንቅስቃሴውና የንግድ ሥራው ሰላማዊ በሆነ መንገድ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የጂቡቲ ወደብ ለኢትዮጵያ ንግድ ትልቁ መውጫ በር ሲሆን፣ ለጂቡቲ ደግሞ ዋነኛው የገቢ ማግኛ ምንጭ ነው፡፡
በተመሳሳይ ዜና የጂቡቲ የግብርና፣ የዓሳና የውኃ ሀብት ሚኒስትር ሙሐመድ አህመድ፣ ኢትዮጵያ ስንዴ ወደ ወጭ ለመላክ ስትጀምር አገራቸው የመግዛት ፍላጎት እንዳላት ተናግረዋል፡፡ ኢትዮጵያ በጂቡቲ ጫት፣ አትክልትና ፍራፍሬ፣ እንዲሁም ንፁህ የመጠጥ ውኃ የምታቀርብ መሆኗ ይታወቃል፡፡