ልዩ ልዩ ችሎታ ያላቸው ወጣቶች ተሰጥዖዋቸውን የሚያበለፅጉበት ወይም የሚያሳድጉበት ትምህርት ቤት በቡራዩ ከተማ ዕውን ሆነ።
ትምህርት ቤቱ ተሰጥዖ ያላቸውን ተማሪዎች በመለየት ከመደበኛ መማር ማስተማር ሳይለዩ ተሰጥዖዋቸውን የሚያበለፅጉበት ነው፡፡ ከትምህርት ቤቱ ግንባታ ጋር ተያይዞ፣ ያካባቢው ማኅበረሰብም ከመሠረተ ልማት ግንባታ ተጠቃሚ ሆኗል፡፡
ትምህርት ቤቱ የባለተሰጥዖዎች ማደሪያና የተለያዩ ግብዓቶች የተሟላለት መሆኑን ጥቅምት 10 ቀን 2015 ዓ.ም. ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ በመቁበት ጊዜ ተገልጿል፡፡
የማበልፀጊያው ትምህርት ቤት በአሥር ሔክታር ላይ ያረፈ ሲሆን፣ የማስፋፊያ ቦታም አለው ተብሏል።
ትምህርት ቤቱ ከተለያዩ የኢትዮጵያ አካባቢዎች የተወጣጡ 1000 ባለተሰጥዖዎችን የመያዝ አቅም እንዳለው ተገልጿል።
የመመገቢያ አዳራሽ፣ ማደሪያ፣ የአስተዳደር ሕንፃ፣ የሕክምና ማዕከል፣ የመማርያ ክፍሎች፣ የጋራ መማርያ አዳራሽ፣ የተለያዩ ቤተሙከራዎች፣ ቤተመጻሕፍትና ሌሎችም አስፈላጊ ግብዓቶች ተሟልተዋል ተብሏል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር እያሉ በ2001 ዓ.ም. የወጠኑት ፕሮጀክት እንደሆነ የሚነገርት የባለተሰጥዖ ማበልፀጊያ ትምህርት ቤት የተገነባው ከ708 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ ነው፡፡
ኘሮጀክቱ በአሥር ሔክታር ላይ የሚያርፍ መሆኑን፣ የተጠናቀቁት ዘጠኝ ብሎኮች በ4.3 ሔክታር መሬት እንደተሸፈኑ ተልጿል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ በምረቃው ላይ እንደተናገሩት፣ ቴክኖሎጂ ከሚያስገኛቸው የኢኮኖሚ ትሩፋቶች ተጠቃሚ ለመሆን በዘርፉ የላቀ ዕውቀት ያላቸው ባለሙያዎችን ማፍራት ያስፈልጋል።
ዓለም በቴክኖሎጂ መምጠቋን፣ ኢትዮጵያም ቴክኖሎጂ የሚያስገኛቸውን የኢኮኖሚ ትሩፋቶች ተጠቃሚ እንድትሆን፣ በዘርፉ የላቀ ዕውቀት ያላቸው ባለሙያዎችን ማፍራት እንዳለባትም ገልጸዋል።
ባለተሰጥዖ ታዳጊዎችና ወጣቶች ክህሎታቸውን እያዳበሩ፣ አገራቸውን በቴክኖሎጂ ከበለፀጉ አገሮች ተርታ እንዲያሠልፉ፣ እንደቡራዩ የተሰጥዖ ማበልፀጊያ ትምህርት ቤት ያሉ የተሰጥዖ ማዕከላትን ማብዛት እንደሚገባ አስረድተዋል።
ከትምህርት፣ ከሰው ኃይል ልማትና ከሥራ ዕድል ፈጠራ፣ ከሳይንስ ቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ልማትና ምርምር ሥርዓት አኳያ መሠረት እንደሚጥል ታምኖበታል፡፡
ፕሮጀክቱ ለአካባቢው ሕዝብ አገልግሎት የሚውል የሁለት ኪሎ ሜትር መንገድ፣ የውስጥ ለውስጥ የጎዳና መብራትና የውኃ አገልግሎት መዘርጋቱም ተገልጿል፡፡
በዋናነት ተጠሪነቱ የፌዴራል መንግሥት መሆኑን፣ ለፕሮጀክቱ መሳካት የከተማ አስተዳደሩም ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማድረጉ በዕለቱ ተገልጿል፡፡
በትምህርት ቤቱ የተለያዩ ተሰጥዖ ያላቸው ተማሪዎች ያቀረቧቸውን ሥራዎች በጠቅላይ ሚኒስትሩና በባለሥልጣናቱ ተጎብኝተዋል፡፡