ለግቢው የቄጤማ አጎዛጎዝ የተለየ ድባብ ሰጥቶታል፡፡ በቄጤማው መሀል የተጎዘጎዘው አሪቲና ባለመዓዛ ቅጠሎች ለአካባቢው ልዩ ጠረንን አምጥቷል፡፡ ከጉዝጓዞው በተጨማሪ ሰንጋ በሬም ይታያል፡፡ የዚህ ሁሉ ድባብ የመስቀል በዓል ለማክበር የሚደረገው ሽርጉድ ማሳያ ነው፡፡ ይህ የበዓል ሽርጉድ አገር ቤት ሄደው ለማያከብሩ ጥሩ ትውስታን ከመፍጠሩ ባለፈ ለዮድ በአቢሲኒያ የባህል አዳራሽ ትልቅ ዋጋ የሚሰጠው ነው፡፡
በአዲስ አበባ ከተማ የኢትዮጵያን ባህልና እሴትን ከሚያስተዋውቁ የባህል አዳራሾች አንዱ የሆነው ዮድ አቢሲኒያ፣ መስከረም 8 ቀን 2015 ዓ.ም. በባህል አዳራሹ የመስቀል በዓልና የደንበኞች ቀንን የመንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣኖች በተገኙበት አክብሯል፡፡
የዮድ አቢሲኒያ ባህል አዳራሽ መሥራችና ባለቤት አቶ ትዕዛዙ ኮሬ እንደተናገሩት፣ ‹‹መስቀል ዳ በቀያንዳ›› የሚባለው የጉራጌ መስቀል በዓልና የደንበኞች ቀን በየዓመቱ ያከብራሉ፡፡ ላለፉት ሁለት አሠርታት የባህል አዳራሻቸው ለአገር መሪዎች፣ ታላላቅ አኅጉር አቀፍና ዓለም አቀፍ የልዑካን ቡድንን የባህል ምግቦችን በማቅረብ እንደሚታወቅም አቶ ትዕዛዙ ተናግረዋል፡፡
ከዚህ በተጨማሪ ወደ አገር ቤት ለመስቀል በዓል ሔደው ማክበር ለማይችሉ በባህላዊ ምግብና ጭፈራ እያዝናና የቆየ ድርጅት መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ በዋናነት የባህል እሴቶችን ከመላው ዓለም ለሚመጡ እንግዶች በማስተዋወቅ የኢትዮጵያ መልካም ገጽታን በማጉላት እንደሚታወቅ ገልጸዋል፡፡
ለቱሪዝም ዕድገት፣ ለሕዝቦች ግንኙነት መጠናከር ባህል አዳራሹ የበኩሉን ሲወጣ መቆየቱን የገለጹት አቶ ትዕዛዙ፣ ‹‹የኢትዮጵያ የባህል አምባሳደር›› የሚል ዕውቅና ያገኘውም ከዚሁ ሥራዎቹ በመነሳት መሆኑን አስረድተዋል፡፡
ማዕከሉ የመስቀል በዓልና የደንበኞች ቀንን በየዓመቱ እንደሚያከብር፣ የዓመቱን 364 ቀኖች የኢትዮጵያን የተለያዩ ባህሎች ሲያስተዋውቅና ሲያሳይ እንደሚቆይ፣ 365ኛውን ቀን ደግሞ የጉራጌን ባህልና ዕሴቶች እንደሚያስተዋውቁ ገልጸዋል፡፡