Friday, June 2, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ማኅበራዊየልጆች የማንበብ ክህሎትን ለማዳበር እስከ ምን ድረስ ተኪዷል?

የልጆች የማንበብ ክህሎትን ለማዳበር እስከ ምን ድረስ ተኪዷል?

ቀን:

ሕፃናትና ታዳጊ ወጣቶች የማንበብ ክህሎታቸውን እንዲያሳድጉና በመልካም ሥነ ምግባር ታንፀው እንዲያድጉ ኢትዮጵያ ሪድስ፣ ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ቤተ መጻሕፍትና ቤተ መዛግብት ኤጀንሲ እንዲሁም ከትምህርት ሚኒስቴር ጋር በመሆን ለሁለት ቀናት የቆየ ዓመታዊ የሕፃናት ንባብ ጉባዔ ሐሙስ መስከረም 12 ቀን 2015 ዓ.ም. በሳፋየር ሆቴል ለሦስተኛ ጊዜ አካሂዷል፡፡

የኢትዮጵያ ሪድስ የፕሮግራም አስተባባሪ አቶ ብርሃኑ ግርማ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ጥናቶች እንደሚሳዩት ከሆነ በኢትዮጵያ አብዛኛዎቹ ሕፃናት/ልጆች የማንበብና አንብቦ የመረዳት ክህሎታቸው ዝቅተኛ ነው፡፡

ሕፃናት ልጆች በለጋ ዕድሜያቸው የማንበብ ባህልን እንዲያዳብሩ መንግሥት፣ ወላጆችና ማኅበረሰቡ የበኩሉን ድርሻ መወጣት አለበት የሚሉት አቶ ብርሃኑ፣ ይህ ካልሆነ ችግሩ እየተባባሰ ሄዶ ትውልድን ሊጎዳ እንደሚችል አክለው ገልጸዋል፡፡

እስከ ዘጠኝ ዓመት ዕድሜ ክልል ላይ የሚገኙ ሕፃናት አዕምሯቸው የመቀበል አቅሙ ከፍተኛ መሆኑን ገልጸው፣ በዚህ ዕድሜ ክልል ላይ ለሚገኙ ልጆች ምቹ የሆኑ የማንበቢያ ቦታዎችን በመፍጠር የማንበብ ክህሎታቸውን ማሳደግ ያስፈልጋል ብለዋል፡፡

በሥዕል፣ በተረት ተረት፣ በሙዚቃና ሌሎችንም ነገሮች ያካተተና ለሕፃናት ልጆች የሚሆኑ ቁምነገር አዘል መጻሕፍትን በማዘጋጀት የሕፃናትን የንባብ አቅም ማሳደግ እንደሚገባ አቶ ብርሃኑ አስረድተዋል፡፡

ድርጅቱም ሕፃናት ላይ ትኩረት ያደረገ ፕሮጀክት ቀርፆ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን የገለጹት አቶ ብርሃኑ፣ ፕሮጀክቱም ከተፀነሰበት ጊዜ አንስቶ ከ400 ሺሕ በላይ የአገር ውስጥና የውጭ አገር መጻሕፍትን በተለያየ መንገድ ለሕፃናትና ለተማሪዎች ተደራሽ ማድረጉን አስታውሰዋል፡፡

በተለያዩ ቋንቋዎች የተዘጋጁ መጻሕፍትን በየትምህርት ቤቱ በማሠራጨት የሕፃናትን የማንበብ ክህሎታቸው እንዲዳብር እየተደረገ መሆኑን፣ ይህም ተግባራዊ ሲደረግ ክልሎችን ጨምሮ ያማከለ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

ቤተ መጻሕፍት ውስጥ ተቀጥረው አገልግሎት ለሚሰጡ ባለሙያዎችም ተቋሙ እንዴት መሥራት እንዳለባቸውና ምንስ ማድረግ እንደሚያስፈልግ፣ በምን መልኩ ሕፃናት ማንበብ እንዳለባቸው እንዲያውቁ ሥልጠናዎች እየተሰጠ መሆኑን አብራርተዋል፡፡

መንግሥት ሆነ ማኅበረሰቡ አንባቢ የሆነ ትውልድ እንዲፈጥር በተለያዩ መንገዶች የንባብ ጠቀሜታን ግንዛቤ የሚፈጥር መድረኮችን ማከናወናቸውን፣ ይህም የሁሉም ሰው ኃላፊነት መሆን እንዳለበት ተናግረዋል፡፡

ከመጻሕፍት ኅትመት ጋር ተያይዞ ተቋሙ ከዚህ በፊት ያሳተማቸው እንደ ማሞ ቂሎ፣ ተክሌ፣ የሾላ ዛፍ፣ የፋፊ በግ፣ ዝሆን፣ ዶሮና የላሊበላዋ ንብ አርቢ ተጠቃሽ መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡

የአፍም መፍቻ ቋንቋ መጽሐፍ ጋር ተያይዞ ከፍተኛ የሆነ ችግር እንዳለ የጠቀሱት አቶ ብርሃኑ፣ በተለይም በሶማሌ ክልልና በሌሎች ቦታዎች ሕፃናትን ያማከለ መጽሐፍ አለመኖሩን ገልጸዋል፡፡

ተቋሙም ከ195 ሺሕ በላይ የሕፃናት መጻሕፍትን በአማርኛ፣ በኦሮሚኛ፣ በሲዳምኛ፣ በጠምባርሳ፣ በሶማሌኛ፣ በዲዚ ቋንቋዎች በ45 ርዕሶች በማዘጋጀትና በማሳተም ተደራሽ ማድረጉን አስታውሰዋል፡፡

እነዚህን የታተሙ መጻሕፍት በአዲስ አበባ፣ በሐዋሳ፣ በባህር ዳር፣ በጅግጅጋ፣ በጎንደር፣ በደሴ፣ በድሬዳዋና በሐረር ከተሞች ለሚገኙ 420 አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች በተለይም ከአንድ እስከ አራተኛ ክፍል ላሉ ተማሪዎች በቤተ መጻሕፍት ውስጥ እንዲጠቀሙ ታሳቢ በማድረግ ሊሠራጭ መቻሉን ጠቁመዋል፡፡

በአገር አቀፍ ደረጃ በተለያዩ ቋንቋዎች የተጻፉ መጻሕፍት አለመኖራቸው ችግሩን አባብሶታል የሚሉት አቶ ብርሃኑ፣ ‹‹ይህንንም ችግር በመረዳት መንግሥት የበኩሉን ድርሻ ሊወጣ ይገባል፤›› ብለዋል፡፡

በዘርፉም ላይ የሚነሱ ችግሮችን ለመፍታት ተቋሙ ተንቀሳቃሽ የሆኑ ቤተ መጻሕፍትን በማዘጋጀት የሕፃናትን የንባብ ክህሎታቸው እንዲያድግ ምቹ ሁኔታዎችን እየፈጠረ መሆኑን አብራርተዋል፡፡

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቤተ መዛግብትና ቤተ መጻሕፍት ኤጀንሲ ይህንን አሠራር ተግባራዊ በማድረግ በየከተማው በተለያዩ ቦታዎች በመንቀሳቀስ የሕፃናትን የማንበብ ክህሎት እንዲያድግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያደረገ ነው ብለዋል፡፡

የኢትዮጵያ ሪድስ በክልሎች ወደ 80 የሚጠጉ የመጀመርያ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ውስጥ ቤተ መጻሕፍትን በማቋቋም ከመንግሥትና ከሌሎች አጋር ድርጅቶች ጋር አብሮ እየሠራ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ድርጅቱ ከተቋቋመበት ጊዜ አንስቶ የተለያዩ ትምህርት ተኮር ፕሮጀክቶችን በመቅረፅ በአማራ፣ በትግራይ፣ በኦሮሚያ፣ በአዲስ አበባ፣ በሲዳማ፣ በደቡብ፣ በድሬዳዋ፣ በሐረሪ፣ በሶማሌ፣ በአፋር፣ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ተደራሽ ማድረጉን አስታውሰዋል፡፡

ሕፃናት በቀላሉ የማንበብ ክህሎታቸው እንዲያሳድጉ እንዲሁም ደግሞ ያላቸውን አቅም እንዲጠቀሙ መንግሥትም ሆነ ሌሎች ባለድርሻ አካላት የበኩላቸውን እንዲወጡም ጥሪ አቅርበዋል፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

የአዛርባጃንን ብሄራዊ ቀን በአዲስ አበባ በድምቀት ተከበረ

የአዛርባጃን ኤምባሲ  የአዛርባጃንን ብሄራዊ ቀን በትላንትናው ዕለት አከበረ። ሰኞ...

የመንግሥትና የሃይማኖት ልዩነት መርህ በኢትዮጵያ

እንደ ኢትዮጵያ ባሉ አገሮች የሃይማኖት ተቋማት አዎንታዊ ሚና የጎላ...

ሐበሻ ቢራ ባለፈው በጀት ዓመት 310 ሚሊዮን ብር የተጣራ ትርፍ ማግኘቱን አስታወቀ

የአንድ አክሲዮን ሽያጭ ዋጋ 2,900 ብር እንዲሆን ተወስኗል የሐበሻ ቢራ...