በዓለም አቀፍ ደረጃ እየተቋቋመ ባለው የአትሌቶች የፀረ አበረታች ቅመሞች ምክር ቤት ውስጥ እንዲሳተፉ ጥሪ ቀረበ፡፡
አራተኛው የኢትዮጵያ ፀረ አበረታች ቅመሞች ጉባዔ መስከረም 10 ቀን 2015 ዓ.ም. በአዲስ አበባ በተካሄደበት አጋጣሚ ጥሪውን ያቀረቡት የዓለም አቀፉ የፀረ አበረታች ቅመሞች (ዋዳ) አመራሮች ናቸው፡፡
ቀደምት ታላላቅ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች እንዳላቸው ስምና ዝና ሁሉ፣ በዓለም አቀፉ የአትሌቶች የፀረ አበረታች ቅመሞች ምክር ቤት ገብተው መሳተፍ ይገባቸዋል ብለዋል፡፡
ኢትዮጵያ የስፖርት አበረታች ቅመሞች (ዶፒንግ) በመከላከልና በመቆጣጠር ረገድ እያከናወነችው ያለችው ተግባራት ውጤታማ እንዳደረጋት የገለጹት በጉባዔው የተሳተፉት የዋዳ አመራሮች፣ የፀረ አበረታች ቅመሞች ባለሥልጣኑ ከተቋቋመበት ጊዜ ጀምሮ ዓለም አቀፍ ግንኙነትን በማጠናከር፣ አፍሪካ ውስጥ ካሉ አቻ ተቋማት በተሻለ ውጤታማ ሥራዎችን መሥራት መቻሉን አውስተዋል፡፡
አመራሮቹ ኢትዮጵያ በቀጣይ የራሷ የሆነ የስፖርት አበረታች ቅመሞችን መመርመር የሚያስችል ላቦራቶሪ ማቋቋም እንደሚኖርባት ጠቁመው፣ ለዚህም ዓለም አቀፉ ተቋም አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚሰጥ መናገራቸውን ባለሥልጣኑ በማኅበራዊ ትስስር ገጹ ባሠራጨው መግለጫ አስታውቋል፡፡
‹‹ንፁህ ስፖርት ለዜጎች ተጠቃሚነት›› በሚል መሪ ቃል በተዘጋጀው ጉባዔ ላይ የኢትዮጵያ የፀረ አበረታች ቅመሞች ባለሥልጣን የቦርድ ሰብሳቢ አክሊሉ አዛዥ (ፕሮፌሰር)፣ ስፖርተኞች ተፈጥሯዊ ባልሆነ መንገድ አበረታች ቅመሞችን (ዶፒንግ) ለመጠቀም የሚያደርጉትን ሙከራ በዘላቂነት መከላከልና መቆጣጠር በሚያስችል መልኩ ባለሥልጣኑ እንደሚገኝ አስታውቀዋል፡፡
ባለፉት አምስት ዓመታት በአገር አቀፍ ደረጃ በተከናወነው እንቅስቃሴም፣ ተቋማዊ አቅሙን ከመገንባት፣ ምርመራና ቁጥጥር ከማድረግ ባሻገር፣ ትምህርትና ሥልጠናን ጨምሮ ዓለም አቀፍ ግንኙነት በማጠናከሩ መሠራቱንም ተናግረዋል፡፡
በመድረኩ በቀደምት ታላላቅ አትሌቶች የተገነባውን የአገር መልካም ገጽታ ለማስቀጠልና በሥነ ምግባር የታነፁ ተተኪ አትሌቶችን ለማፍራት ሁሉም የበኩሉን ድርሻ መወጣት እንዲወጣ ጥሪ ቀርቧል፡፡