የምሥራቅና የአፍሪካ ቀንድ አገሮች ሥራ ፈላጊ ዜጎቻቸው በቀጣናው ውስጥ፣ እንዲሁም ወደ መካከለኛው ምሥራቅና ሌሎች የአፍሪካ አገሮች ለሥራ ሲሄዱ በትብብር ለመሥራት የሚያስችል ቀጣናዊ የሚኒስትሮች የጋራ ፎረም መሠረቱ፡፡
ኢትዮጵያ በሊቀመንበርነት የምትመራውና 11 አባል አገሮች ያሉበት ይህ ፎረም፣ በዋነኝነት የጋራ የፖሊሲ ሐሳቦች በማመንጨት ኢመደበኛ የሆነውን የሰዎች ዝውውር ሕጋዊ ሥርዓቱን ተከትሎ እንዲከናወን፣ መነሻና መተላለፊያ በሆኑ የምሥራቅ የአፍሪካ ቀንድ አገሮችና ወደ መካከለኛው ምሥራቅ አገሮች ለሚሰማሩ ሥራ ፈላጊዎች፣ ወጥ የሆነ የሥራ ምደባና ክፍያ እንዲያገኙ የሚያስችል እንደሆነ ተገልጿል፡፡
በተጨማሪም በአገሮቹ መካከል ወጥ የሆነ የአሠራር ሥርዓት በመዘርጋት ለወጣቶች የሥልጠናና ሥራ ፈጠራ ሥምሪት አስፈላጊ የሆነ የሥራ ገበያ መረጃ ሥርዓት ልውውጥ በመፍጠር፣ ሥራ ፈላጊዎችን ብቁና ተወዳዳሪ በማድረግ፣ ለሥራ በሚላኩባቸው አገሮች ለሚገጥሟቸው ማናቸውም ችግሮች ሁሉም አገሮች በየኢምባሲዎቻቸው በኩል ከቀጣናው አገሮች ለሚሄዱ ዜጎች ድጋፍ እንዲያደርጉ የሚረዳ ፎረም መሆኑን፣ የሥራና ክህሎት ሚኒስትሯ ወ/ሮ ሙፈሪያት ካሚል ተናግረዋል፡፡
አገሮቹ የመሠረቱት የሚኒስትሮች ፎረም የሙያተኞች ውይይት ከመስከረም 9 እስከ መስከረም 10 ቀን 2015 ዓ.ም. በአዲስ አበባ የተካሄደ ሲሆን፣ ከአባል አገሮች የተውጣጡ ተሳታፊዎች ተገኝተዋል፡፡
በምሥራቅ አፍሪካ የአይኦኤም ከፍተኛ ባለሙያ የሆኑት ታቲና ሃድጂማኑኤል ለሪፖርተር እንደተናገሩት፣ የሕገወጥ የሰዎች ዝውውር በኮቪድ ወረርሽኝ ወቅት መቀነስ አሳይቶ የነበረ ቢሆንም፣ አሁን ከፍተኛ የሆነ የፍልሰት ምጣኔ አለ፡፡ በቀጣናው ከሚታየው ለሥራ የሚደረግ ፍልሰት፣ ኢትዮጵያውያን ቀዳሚውን ድርሻ ቢይዙም እንደ ኬንያ፣ ኡጋንዳ፣ ታንዛኒያ፣ ሩዋንዳና ሶማሊያ ባሉ አገሮች ይኸው ችግር እንዳለ አስረድተዋል፡፡
በቀጣናው በሚገኙ አገሮች የሕዝብ እንቅስቃሴ በቀላሉ የሚገታ ጉዳይ አለመሆኑን የጠቀሱት ባለሙያዋ፣ በአመዛኙ የተሻለ ዕድገት አላቸው ተብለው በሚታሰቡት እንደ ኬንያ፣ ሩዋንዳና ኡጋንዳ በርካታ ወጣቶች የሚሰደዱባቸው መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡
በአኅጉሩ በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ ለመጣው ፍልሰት ዋነኛ አስገዳጅ ምክንያት ተደርገው የሚወሰዱት ግጭት፣ ድርቅና የአየር ንብረት ለውጥ ናቸው፡፡ በእነዚህ ችግሮች የተነሳ የተሻለ የኢኮኖሚ አማራጮችን ለማግኘት ሰዎች እንደሚሰደዱ የገለጹት ባለሙያዋ፣ አብዛኛው ፍልሰት በቀጣናው ውስጥ ባሉ አገሮች መካከል ቢሆንም፣ በርካቶች ደግሞ መካከለኛው ምሥራቅ አፍሪካ አገሮች መሆኑን አስረድተዋል፡፡
የፕሮግራሙን ወጪ የሚሸፈነው በአይኦኤም፣ በፎረሙ መሥራች አገሮች፣ በአፍሪካ ኅብረትና በኢጋድ አማካይነት መሆኑ ተገልጿል፡፡ ኢትዮጵያ፣ ኤርትራ፣ ኬንያ፣ ኡጋንዳ፣ ታንዛኒያ፣ ሱዳን፣ ደቡብ ሱዳን፣ ሩዋንዳ፣ ሶማሊያ፣ ጂቡቲና ብሩንዲ የፎረሙ አባላት ናቸው፡፡
ኢመደበኛ በሆነ መንገድ በማከናወን የሰዎች ዝውውርና ፍልሰት ላይ የሚያተኩረው የሚኒስተሮች ትብብር ፎረም፣ ወደ ቀጣናውና መካከለኛው ምሥራቅ በሕገወጥ መንገድ የሚደረገውን የሥራ ፍለጋ ጉዞ፣ ሕጋዊ ለማድረግ ብቁ ሙያተኞችን አሰማርቶ እንደሚሠራ ወ/ሮ ሙፈሪያት ተናግረዋል፡፡
ፎረሙ የሥራ ፈላጊዎች መዳረሻ አገሮች ላይ የሚያጋጥሙ መጉላላቶችን ለማስቀረት እንደሚወዱ፣ የሥራ ክህሎት ላይ ወጥ የሆነ ዘመናዊ አሠራር በመዘርጋት ሥልጠናና የገበያ መረጃ ላይ እንደሚያተኩር አስረድተዋል፡፡
በተጨማሪም የትብብር ፎረሙ በዓለም ላይ ያለውን የሥራ ዕድል ገበያ በጋራ በማጥናት፣ ከአሥራ አንዱም አገሮች ሠልጥነው የሚላኩ ሙያተኞች ክፍያቸው በብቃት እንጂ በአገሮች መካከል ባለ ቅርበት ወይም ግንኙነት እንዳይሆን እንደሚሠራ፣ ስታንዳርድ በማውጣት የክፍያ ሥርዓት በሥራ መለኪያ ብቻ በማድረግ ማንም ይሁን ማን በብቃት ብቻ እንዲሆን የሚያደርግ አሠራር ለመዘርጋት ያግዛል ተብሏል፡፡
የኢትዮጵያ መንግሥት ለሥራ ሥምሪት የሚያግዙ አዳዲስና ወቅቱ የሚፈልገው ሙያ ሊገኝባቸው የሚችሉ ከ100 በላይ የሥልጠና ማንዋሎች መዘጋጀታቸውን፣ ብቁ አሠልጣኞችን ለመመልመል እየተሠራ መሆኑን የገለጹት ወ/ሮ ሙፈሪያት፣ ከሥልጠና በኋላ የሚሰማሩ ሙያተኞች አገራቸውን የሚወዱ ነገር ግን የሚሄዱበትን አገር፣ ባህልና ቋንቋ የተረዱ እንዲሆኑ ታሳቢ መደረጉን አስረድተዋል፡፡
በመሆኑም በውጭ አገር የሚሰማሩ ባለሙያዎችን በልዩ ሁኔታ የሚያሠለጥኑ የቴክኒክና የሙያ ተቋማትና አሠልጣኞች ተለይተው፣ ሥራ ፈላጊዎቹ ውጭ አገር ሲሄዱ የሚሰማሩባቸውን መሣሪያዎች ሳያውቁ እንዳይሄዱ የሚያግዙ የቴክኒክና የሙያ መሣሪያዎች መዘጋጀታቸውን አክለው ገልጸዋል፡፡