ዓይን በሰው ልጅ ሕይወት ውስጥ ትልቅ ሚና ያለው አካላተ ስሜት ነው፡፡ ተፈጥሮው ትንሽ ቢሆንም ከርቀት ያለውን ነገር ማየትና መለየት ይችላል፡፡ የሚታየውንም ነገር ወደ አዕምሮ በመላክ መልዕክቱን ወደ ምስል በመቀየር ያለምንም ችግር በቀላሉ ለመረዳት የሚያስችሉ ሁኔታዎችን በማመቻቸት ረገድ የጎላ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክት በዘርፉ የተከናወኑ ጥናቶች ያስረዳሉ፡፡
ይህም ሆኖ ግን ከፍተኛ ጥንቃቄ ያስፈልገዋል፡፡ ምክንያቱም ዓይን በተፈጥሮው ጉዳትን መቋቋም የማይችል በመሆኑ ነው፡፡ በተጠቀሰውም ጉዳት የተነሳ ለተለያዩ የዓይን በሽታ የተዳረጉ ወገኖች መኖራቸውን ቤት ይቁጠረው፡፡ በበሽታው ዙሪያ የሚሠሩ የጤና ተቋማትና የዓይን ሐኪሞችም እጥረት ለበሽታው መስፋፋት አስተዋጽኦ ማድረጉን አያከራክርም፡፡
ከሁለት አሠርታት ወዲህ ግን በመንግሥትና በግሉ ዘርፍ ጥረት የዓይን ሕክምና ተቋማት እየተስፋፉና የሐኪሞችም ቁጥር እየጨመረ መምጣቱ እየተስተዋለ ነው፡፡ ይህ መስፋፋት የታየውም በዋናነት አዲስ አበባን ጨምሮ በጥቂት የክልል ከተሞች ነው፡፡ ከዚህ አኳያ ከመንግሥት ባሻገር የቀሩት ተቋማት ተደራሽነታቸውና የክፍያ ዋጋቸው አይቀመስም፡፡
መንግሥታዊ ከሆኑ የዓይን ሕክምና ተቋማት መካከል የዳግማዊ ምኒልክ ኮምፕርሄንሲቭ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታልና የቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሌኒየም ሕክምና ኮሌጅ የዓይን ሕክምና ማዕከላት ይጠቀሳሉ፡፡ ከእነዚህም መካከል በአንጋፋነቱ የሚታወቀው የዳግማዊ ምኒልክ ሆስፒታል ማዕከል ሲሆን ለዓይን ሕክምና መስፋፋትም ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክቷል፡፡
ሆስፒታሉ ከምዕት ዓመት በላይ የተለያዩ የሕክምና አገልግሎት በመስጠት ላይ የሚገኝ ሲሆን፣ በቅርቡ የተመረቀው ዓይን ሕክምና ማዕከሉ ደግሞ ጊዜውን በሚመጥን የሕክምና መሣሪያዎች ተሟልቷል፡፡ ይህ ዓይነቱም አደረጃጀት የታካሚዎችን የአገልግሎት እርካታን፣ የሕክምና ጥራትንና አቅምን እንደሚጨምር ከጤና ሚኒስቴር የወጣው መረጃ ያመለክታል፡፡
ማዕከሉ ባለ አራት ወለል ሲሆን 120 አልጋዎች፣ ለሕፃናትም ምቹ የሆነና የተደራጀ ዘመናዊ የእንግዳ መቀበያ እንዳለው፣ ከተለያየ ክልሎች ለሚመጡ ታካሚዎችም አገልግሎት እንደሚሰጥ፣ ከዚህም አገልግሎት ባሻገር ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር ትምህርትና ሥልጠና እንደሚሰጥ ነው የተገለጸው፡፡
የሕክምና ማዕከሉን ለመገንባትና ውስጣዊ ድርጅትንም ለማሟላት 461 ሚሊዮን ብር መፍጀቱን፣ በዚህም 45 የምርመራ፣ አራት የቀዶ ሕክምና፣ የትምህርትና ሌሎችም የመገልገያ ክፍሎች እንዳሉት ለማወቅ ተችሏል፡፡ ከዚህም ሌላ 22 ስፔሻሊስትና ስድስት ሰብ ስፔሻሊስት ሐኪሞች ያሉት የዓይን ሕክምና ማዕከል መሆኑን ነው በምረቃው ወቅት የተነገረው፡፡
የጤና ሚኒስትር ሊያ ታደሰ (ዶ/ር) ማዕከሉ ለኢትዮጵያ ታላቅ እመርታ መሆኑና በቀጣይም በተለያዩ ክልሎች የዓይን ሕክምና አገልግሎትን ለማስፋፋት ትኩረት ተሰጥቶት እየተሠራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
የዓይን ሕክምና እንደ አገር ትኩረት የሚሻ ዋናው ዘርፍ መሆኑንና ዘርፉንም በሰው ኃይልና በግብዓት ለማሟላት አስፈላጊው ድጋፍ ሁሉ እንደሚደረግ ሚኒስትሯ ሳይገልጹ አላለፉም፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጤና ቢሮ ኃላፊ ዮሐንስ ጫላ (ዶ/ር) ቀደም ሲል የነበረው የዓይን ሕክምና ክፍል ከግማሽ ምዕተ ዓመት በላይ ሲሠራበት የቆየውን አካሄድ በመቀየር፣ በአዲስ ቴክኖሎጂ በታገዘና ደረጃውን በጠበቀ ማዕከል መተካቱን ነው የተናገሩት፡፡ ይህም ከተማ አስተዳደሩ ለጤናው ዘርፍ ትኩረት በመስጠት የኅብረተሰቡን ዕርካታ ለመጨመር እየሠራ መሆኑን በተግባር ያረጋገጠበት መሆኑን እንደሚያመላክት ነው የገለጹት፡፡
የአዲስ አበባ ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ ሁሉንም የጤና ተቋማት ወረቀት አልባ ዲጂታል የጤና አገልግሎት እንዲሰጡና አዲስ አበባንም የጤና ቱሪዝም ማዕከል ለማድረግ እየተሠራ መሆኑን ገልጸው፣ ከተማ አስተዳደሩ ከፍተኛ ትኩረት ከሰጣቸው ዘርፎች መካከል የጤናው ዘርፍ ዋነኛው መሆኑን አስረድተዋል፡፡
እንደ ከንቲባዋ አባባል፣ የሕክምና ማዕከሉ በአጠቃላይ በኢትዮጵያ የሚሰጠውን የዓይን ሕክምና አገልግሎት ያዘመነና ያሻሻለ ከመሆኑም በላይ የበጀት ብክነት ሳያጋጥምና በተያዘለት ጊዜ ውስጥ ፕሮጀክቶችን የመፈጸም አቅምን የዳበረ መሆኑን ያመላከተ ነው፡፡ አዲስ አበባን የሕክምና ማዕከል ለማድረግ በመንግሥት ከሚሠሩ ፕሮጀክቶች በተጨማሪ የግሉን የጤና ዘርፍ ለማበረታታት የሚያስችል እንቅስቃሴ እየተከናወነ ነው፡፡
የአዲስ አበባ ዲዛይንና ግንባታ ሥራዎች ቢሮ ሰው ተኮር ፕሮጀክቶችን በማስፈጸም ላይ እንደሚገኝና የዓይን ሕክምና ማዕከሉ ቢሮው ከሚያሠራቸው 390 ፕሮጀክቶች አንዱ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የቢሮው ኃላፊ አያልነሽ ሀብተማርያም (ኢንጂነር) ናቸው፡፡
በኢትዮጵያ የመጀመርያ የሆነው የዳግማዊ ምኒልክ ኮምፕረሄንሲቭ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል፣ የካቲት 12 ሆስፒታልና ሜዲካል ኮሌጅ፣ የጋንዲ መታሰቢያ ሆስፒታል፣ ራስ ደስታና ጥሩነሽ ቤጂንግ ጠቅላላ ሆስፒታሎች በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጤና ቢሮ ሥር የሚተዳደሩ ናቸው፡፡