- እየደገፉን ያሉ አንዳንድ ልማታዊ ወጣቶች በከተማ አስተዳደሩ ላይ ቅሬታ አቅርበዋል።
- እኛ ላይ?
- አዎ!
- ቅሬታቸው ምንድነው? ለምን ለእኛ አላሳወቁንም?
- የሚሰማቸው ስላላገኙ ነው ቅሬታቸውን ወደ እኛ ይዘው የመጡት።
- እስኪ ነገሩን አጣራለሁ ለማንኛውም ቅሬታቸውን ይንገሩኝ?
- እንደ ልማታዊ ወጣት ለመንግሥት ድጋፍ እያደረግን ቢሆንም በከተማ ውስጥ የመኖሪያ ቤት የምንገነባበት መሬት ልናገኝ አልቻልንም ነው የሚሉት። ይህ ደግሞ ሆነ ተብሎ የተፈጸመባቸው እንደሆነ ነው የሚያነሱት።
- ክቡር ሚኒስትር ከተማው ውስጥ የመኖሪያ ቤት መሥሪያ ቦታ እጥረት እንዳለ ያውቃሉ አይደል? ባይሆን ጥያቄያቸውን በሌላ መንገድ መፍትሔ እንዲያገኝ ብናደርግ አይሻልም?
- ሌላ መንገድ ማለት?
- ባዶ የሆኑ የኮንዶሚኒየም ቤቶች ካሉ ፈልገን እንዲያገኙ ማድረግ እንችላለን።
- ኮንዶሚኒየም ቤትማ በራሳቸው መከራየት ይችላሉ ወይም …
- ወይም ምን ክቡር ሚኒስትር?
- ወይም ሊገዙ ይችላሉ።
- እንደዚያ ማድረግ እየቻሉ ለምን በእኛ ላይ ቅሬታ ያቀርባሉ ታዲያ?
- ለመኖሪያ ቤት መሥሪያ መሬት እንዲሰጣቸው ጠይቀው በመከልከላቸው አልኩኝ እኮ፣ አልሰሙኝም?
- ክቡር ሚኒስትር ኮንዶሚኒየም ቤት መከራየት ወይም መግዛት እየቻሉ መሬት እንዲሰጣቸው መጠየቃቸው በራሱ ትክክል ነው ብለው ያምናሉ?
- እንዴት? ድጋፍ የሚያደርጉልን ልማታዊ ወጣቶች ናቸው እያልኩኝ አይደለም እንዴ?
- እህ… እንደዚያ ነው?
- እንዲያውም እነሱ ሳይጠይቁ ነበር መሬት እንዲያገኙ ማድረግ የነበረባችሁ። ስለዚህ በአስቸኳይ አስተናግዷቸው።
- ክቡር ሚኒስትር ጥያቄውን እናስተናግዳለን ነገር ግን
- ግን የሚባል አልቀበልም፡፡
- ክቡር ሚኒስትር ለምን መሰልዎት…?
- እህ…
- በአሁኑ ወቅት ያለውን መሬት ወረራ ለመከላከል ብለን የመሬት ጥያቄዎችን እያስተናገድን አይደለም።
- በልዩ ሁኔታ የምታስተናግዱት እንዳለ ሰምቻለሁ።
- የተፈናቀሉ አርሶ አደሮችን ጥያቄ ብቻ ነው በልዩ ሁኔታ እያስተናገድን ያለነው።
- ቢሆንም እነሱንም በዚሁ መንገድ ማስተናገድ ትችላላችሁ፣ ከላይ የወረደ ትዕዛዝ ነው!
- ልማታዊ ወጣቶች ናቸው አላሉም እንዴ ክቡር ሚኒስትር?
- አዎ፣ ልክ ነው።
- ታዲያ አርሶ አደሮች ካልሆኑ ምን ብለን እናስተናግዳቸዋለን?
- የአርሶ አደር ልጆች።
[ክቡር ሚኒስትሩ ወደ ቢሯቸው እንደገቡ አማካሪያቸው ፊቱ በፈገግታ ተሞሎቶ እንኳን ደስ አለዎት ክቡር ሚኒስትር እያለ ወደ ቢሯቸው ገባ]
- ፊትህ በፈገግታ ደምቋል፣ ምን አዲስ ነገር አለ?
- በጣም ደስ የሚል ነገር ነው የሰማነው ክቡር ሚኒስትር። እንኳን ደስ አለዎት፡፡
- ምን ሰምተህ ነው?
- ውርጅብኙ ሲበዛባቸው ያቀረቡትን ጥሪ ሰምቼ ነው።
- ጁንታዎቹን ማለትህ ነው? አዲስ ነገር ጥሪ አቀረቡ እንዴ?
- አልሰሙም እንዴ? ጡጫው ሲበዛባቸው እኮ
- የአፍሪካ ኅብረትን አደራዳሪነት እንቀበላለን አሉ፡፡
- አይ አንተ! ቀድሞውንስ መቼ የአፍሪካ ኅብረት አያደራድረንም አሉ?
- የአፍሪካ ኅብረትን ሲያንቋሽሹ አልነበረም አንዴ? አሜሪካንን ጨምሮ የተለያዩ የውጭ መንግሥታትም የአፍሪካ ኅብረት አደራዳሪነትን መቀበሉን በማድነቅ መግለጫ ማውጣታቸውን አይቻለሁ።
- ሆነ ብለው እያደናገሩ ነው እንጂ እስካሁን ድረስ ሲያደራድረን የቆየው የአፍሪካ ኅብረት ነው።
- ታዲያ አዲሱ ነገር ምንድነው?
- ምንም አዲስ ነገር የለም።
- ምን የተለየ ነገር የለም?
- አዎ። በፊትም ቢሆን የአፍሪካ ኅብረት አደራዳሪነትን አለመቀበል ችግር እንደሚያመጣባቸው ስለሚያውቁ ኅብረቱን አንቀበልም አላሉም። ኅብረቱ የሾማቸው አደራዳሪ ላይ ግን የማጥላላት ዘመቻ ከመክፈት ባለፈ እርሳቸውን በአደራዳሪነት አንቀበልም ብለዋል።
- አሁን ግን ይህንን አቋማቸውን የቀየሩ ይመስለኛል። አይደል ክቡር ሚኒስትር?
- ምንም ዓይነት የአቋም ለውጥ አላደረጉም።
- በናይጄሪያዊው ሰውዬ ላይ የነበራቸው አቋምም አልተቀየረም?
- በፍጹም! ያወጡት መግለጫ ምን መሰለህ የሚለው?
- እሺ… እየሰማሁ ነው ይቀጥሉ ክቡር ሚኒስትር?
- በአፍሪካ ኅብረት የሚመራ የሠላም ሒደትን እንቀበላለን። ኅብረቱ ሁለቱም ወገኖች ተስማምተው የተቀበሉትን አደራዳሪ መሾም አለበት ነው የሚለው።
- ለምንድነው ታዲያ ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ጁንታውን እያወደሰ ያለው?
- መንግሥት የቀረበለትን የሰላም ጥሪ ወደ ጎን ገፋ በማለት ዘመቻ ለመክፈት ስለፈለጉ ነው።
- መንግሥት በማንኛውም ቦታና ጊዜ ያለ ቅደመ ሁኔታ የተኩስ አቁም እንዲደረግ ለአፍሪካ ኅብረት ጥሪ ማቅረቡን አያውቁም እንዴ?
- ያውቃሉ!
- ታዲያ ለምን ጁንታው ይህንን እንዲቀበል ጥሪ አላቀረቡም?
- ጁንታው የሚፈልገውን ነገር የያዘ ባለመሆኑ ይመስለኛል።
- ጁንታው የሚፈልገው ምንድነው?
- ቅድመ ሁኔታ!