- ሁለት የዑጋንዳ ክለቦች ይካፈላሉ
በቅርቡ የባንኩን ዘርፍ የተቀላቀለው አማራ ባንክ፣ ‹‹የአማራ ባንክ የጣና ዋንጫ›› የተሰኘ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ክለቦች የሚሳተፉበት ውድድር በባህር ዳር እንደሚያካሂድ አስታወቀ፡፡
አማራ ባንክ፣ የባህር ዳር ከተማ ስፖርትና ወጣቶች መምሪያና ጎፈሬ ትጥቅ አምራች ሐሙስ ጳጉሜን 3 ቀን 2014 ዓ.ም. በጋራ ጋዜጣዊ መግለጫ የሰጡ ሲሆን፣ በዚህም ሁለት የዑጋንዳ ክለቦችን ጨምሮ ከስድስት እስከ ስምንት ክለቦች ተካፋይ እንደሚሆኑ ታውቋል፡፡
የእግር ኳስ ውድድሩ ከመስከረም 6 እስከ 14 ቀን 2015 ዓ.ም. በባህር ዳር ስታዲየም የሚከናውን ሲሆን፣ ተሳታፊ ክለቦች ከወዲሁ ወደ ከተማዋ መግባት ጀምረዋል፡፡ ቅዱስ ጊየርጊስ፣ ባህር ዳር ከተማ፣ መቻል (መከላከያ) እና ድሬዳዋ እስካሁን በውድድሩ ላይ እንደሚካፈሉ ከወዲሁ ያረጋገጡ ክለቦች መሆናቸው ተጠቅሷል፡፡
አማራ ባንክ ውድድሩ እንዲሰናዳ የአምስት ሚሊዮን ብር ድጋፍ ማድረጉ ሲገለጽ፣ ውድድሩ በከተማዋ ለሚጀምረው የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ክለቦች ቅድመ ዝግጅት ይረዳል ተብሏል፡፡
መስከረም 20 ቀን 2015 ዓ.ም. በባህር ዳር ስታዲየም የሚጀመረው የቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የአምስት ሳምንት ጨዋታዎች የሚከናወኑ ሲሆን፣ ክለቦች የቅድመ ማጣሪያውን ውድድር አጠናቀው መደበኛውን ጨዋታ በዚያው ይቀጥላሉ ተብሏል፡፡
በየዓመቱ የሚከናወኑ ቅድመ ውድድሮች እየተበራከቱ የመጡ ሲሆን፣ የአዲስ አበባ ከተማ ዋንጫን ጨምሮ በደቡብና በሐዋሳ የሚከናወኑ የቅድመ ውድድሮች የተለመዱ ናቸው፡፡ ዘንድሮ በባህር ዳር የሚጀመረው የአማራ ባንክ የጣና ዋንጫ ውድድር ቀጣይነት እንዲኖረው ይደረጋል ተብሏል፡፡