በገቢዎች ሚኒስትር ከፍተኛ ግብር ከፋዮች አንዱ የሆነውና የነበረበትን የግብር ዕዳ እያቃለለ የሚገኘው፣ እንዲሁም በወ/ሮ አኪኮ ሥዩም ከፍተኛ ባለድርሻነት የተመሠረተው ኦርኪድ ቢዝነስ ግሩፕ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር፣ በተለያዩ ንግድ ባንኮች ንብረቶቹ በሐራጅ እንዲሸጡ ጨረታ እንደወጣበት ታወቀ፡፡
ኦሮሚያ ባንክ ለኦርኪድ ቢዝነስ ግሩፕ ላበደረው ብድር ዋስትና እንዲሆን የያዘውን የመኖሪያ ቤትና የሪል እስቴት መኖሪያ ቤት ባለፈው ዓመት ነሐሴ 18 ቀን 2014 ዓ.ም. የሐራጅ ሽያጭ ማስታወቂያ አውጥቶባቸዋል፡፡ ባንኩም ለመኖሪያ ቤቱ 11.7 ሚሊዮን ብርና ለሪል ስቴቱ ደግሞ 8.6 ሚሊዮን ብር መነሻ የጨረታ ዋጋ ያወጣ ሲሆን፣ ጨረታውን መስከረም 19 ቀን 2015 ዓ.ም. ለመጀመሪያ ጊዜ ለማካሄድ አቅዷል፡፡
እንደ ባንኩ ማስታወቂያ ከሆነ በ549 ካሬ ሜትር ላይ ያረፈው መኖሪያ ቤት ሲሆን በወ/ሮ የሺሐረግ አስታ በተባሉ ግለሰብ በኩል በማስያዣነት ቀርቦ የነበረ ሲሆን፣ በ676 ካሬ ሜትር ላይ ያረፈው የሪል ስቴት መኖሪያ ቤት ደግሞ በአኪኮ ሪል ስቴት ኃላፊቱ የተወሰነ የግል ማኅበር ስም በማስያዥነት የቀረበ ነው፡፡
የኦሮሚያ ባንክ ጨረታውን ለማካሄድ የተቀጠረ ሲሆን፣ ሌሎች የድርጅቱ ንብረቶችም፣ ብድሩ ባለመክፈሉ በሌሎች ባንኮች ከዚህ በፊት ለጨታ ቀርበው እንደነበር ይታወሳል፡፡
አዋሽ ባንክ በየካቲት 12 ቀን 2014 ዓ.ም. ባወጣው የሐራጅ ማስታወቂያ፣ ተበዳሪው ድርጅት ለራሱ ያስያዘውን በሰበታ የሚገኝ በ9,760 ኪሎ ሜትር ላይ ያረፈው የኢንዱስትሪ ቦታ በ105.8 ሚሊዮን ብር መነሻ መጋቢት 14 ቀን 2014 ዓ.ም. ሊያካሂድ አቅዶ ነበር፡፡ በተመሳሳይም ዳሸን ባንክ ሚያዝያ 2 ቀን 2014 ዓ.ም. አውጥቶት የነበረውን ሦስት የባንክና የኢንሹራንስ አክሲዮኖች፣ ግንቦት 5 ቀን 2014 ዓ.ም. ሊያካሂድ አቅዶ ነበር፡፡
ለዳሸን ባንክ በድርጅቱ በራሱ ስም ተይዞ የነበረው የኅብረት ባንክ አክሲዮን 3.7 ሚሊዮን ብር መነሻ ወጥቶበት የነበረ ሲሆን፣ በባለቤቷ ወ/ሮ አኪኮ ተይዘው የነበሩት የእናት ባንክና የኅብረት ኢንሹራንስ አክሲዮኖች ደግሞ እያንዳንዳቸው መነሻ ዋጋቸው አራት ሚሊዮን ብርና 2.7 ሚሊዮን ብር ነበር፡፡
ከአዋሽ ባንክም ሆነ ከዳሸን ባንክ የእነዚህን የጨረታ ውጤቶች ሪፖርተር ለማግኘት ያደረገው ሙከራ ሳይሳካ ቀርቷል፡፡ በተጨሪም የድርጅቱን ተወካዮች ለማግኘት የተደረገው ተደጋጋሚ ሙከራ አልተሳካም፡፡
በሌላ በኩል ከዓመት በፊት በ2013 ዓ.ም. በገቢዎች ሚኒስቴር ከፍተኛ ግብር ከፋዮች ጽሕፈት ቤት የድርጅቱ ንብረቶችን የማሳገድ ደብዳቤ ተጽፎበት የነበረ ሲሆን፣ የነበሩበትን በማቃለል ላይ እንደሚገኝ የገቢዎች ሚኒስቴር ምንጮች ለሪፖርተር ጠቅሰዋል፡፡
እስከ ባለፈው ሰኔ ወር 2014 ዓ.ም. ድረስ ድርጅቱ ያለበትን 529.8 ሚሊዮን ብር ዕዳ አሳልፎ 549 ሚሊዮን ብር በመክፈል ተጨማሪ 19.2 ሚሊዮን ብር ትርፍ እንዲኖረው ማድረጉን ምንጮች ተናግረዋል፡፡
ሆኖም ግን እ.ኤ.አ. እስከ 2020 ድረስ ድርጅቱ 332.9 ሚሊዮን ብር የገቢ ግብር የነበረበት ሲሆን፣ ከዚህ ውስጥም 315.8 ሚሊዮን ብር መክፈሉንና እ.ኤ.አ. ከ2020 ወዲህ ደግሞ ያለበትን የገቢ ግብር ለከፍተኛ ግብር ከፋዮች ያላሳወቀ መሆኑም ታውቋል፡፡