የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) እና የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) መስከረም 3 ቀን 2015 ዓ.ም. ባወጡት መግለጫ፣ ሕወሓት ለድርድር ዝግጁ ነኝ ብሎ መቅረቡ ለጊዜ መግዣና ለቀጣይ ጥቃት ዝግጅት ለማድርግ ሊሆን ስለሚችል የፌዴራል መንግሥት በአንክሮት እንዲከታተለው ጥሪ አቀረቡ፡፡
ሁለቱ ፓርቲዎች ትናንት ማክሰኞ መስከረም 3 ቀን 2015 ዓ.ም. ባወጡት መግለጫቸው ሕወሓት ያቀረበውን የድርድርና የሰላም አማራጮች እንደ መልካም ሊወሰዱ ቢችሉም ባህሪው የሰላም ድርድሩን እንደ ጊዜ መግዣ ወስዶ ቀጣይ ጥቃት ለመክፈትና ለጥፋት ዝግጅት እንዳይጠቀምበት ሥጋት እንዳላቸው አስታውቀዋል፡፡
‹‹መንግሥትና ሕዝባችን ይህንኑ በመረዳት አስፈላጊውን ዝግጅትና ጥንቃቄ እንዲያደርጉ አጽንኦት ሰጥተን ለማሳሰብ እንወዳለን›› ሲል ኤዜማ አስታውቋል፡፡
‹‹መቼም ቢሆን ለእውነተኛ ሰላም የሚረፍድ ጊዜ የለም ብዬ ባምንም፣ ይህ የሰላም ድርድር ጥያቄ በተራዘመ ጦርነት የአገርን ኢኮኖሚ በማዳከም፣ ማኅበረሰቡን የሥነ ልቦና ጫና ውስጥ በመክተት፣ ሕዝባዊ ስልቹነት ውስጥ ለማስገባት ታስቦ የሚደረግ ደባ እንዳይሆን በጥንቃቄ ልናየው ይገባል፤›› ሲል ኢዜማ አሳስቧል፡፡
የአገርን ሉዓላዊነትና የግዛት አንድነት ለማስከበር ትጥቅ ይዞ የሚንቀሳቀስን ኃይል የማዘዝ ሥልጣን ሊኖረው የሚገባው የፌዴራል መንግሥት ብቻ ስለመሆኑ አገራዊም ሆነ ዓለም አቀፍ ድንጋጌዎችን አስረግጦ በማስገንዘብ፣ ሕወሓት ትጥቁን እንዲፈታ ሊደረግ እንደሚገባም አሳስቧል፡፡
ኢዜማ በመሆኑም በየትኛውም ክልል ውስጥ የሚገኙ የፌዴራል ተቋማትንም ሆኑ የኢትዮጵያን ዳር ድንበር የመጠበቅና የአየር ክልሉን ሙሉ ለሙሉ የመቆጣጠር ሥልጣን በብቸኝነት የፌዴራል መንግሥቱ መሆኑን ሕወሓትም ሊገነዘበው ይገባል ብሏል፡፡
ሕወሓት ያስታወቀው የእንደራደር ጥያቄ ከጀርባ ያለው ምክንያት መጠናት ያለበት ሆኖ፣ ‹‹ሰላምን እመርጣለሁ›› ማለቱን መልካም ጅምር አድርጎ መውሰድ እንደሚገባ ኢዜማ በመግለጫው አስታውቋል፡፡
በሌላ በኩል ጦርነት ለመመከት የተሠለፉ ኢትዮጵያዊ ኃይሎች ሁሉ የሚከፍሉትን የአካልና የሕይወት መስዋዕትነት በከንቱ መሆን እንደሌለበት አጽንኦት ሊሰጠው እንደሚገባ ያሳሰበው ኢዜማ፣ በሕወሓት የሚታዘዝ ምንም ዓይነት የታጠቀ ኃይል በየትም ቦታ እንዳይኖር ጠይቋል፡፡
በተመሳሳይ አብን በመግለጫቸው ሕወሓት ያወጣው የድርድር ጥያቄ መግለጫው የተጻፈበት ቀለም ሳይደርቅ በማግስቱ መስከረም 2 ቀን 2015 ዓ.ም. ማለዳ በሱዳን ድንበር በኩል በምዕራብ ጎንደር ዞን መተማ ወረዳ ልዩ ስሙ ቲሃ ተብሎ በሚታወቀው አካባቢ አዲስ ጥቃት ከፍቶ እንደነበር አስታውቋል፡፡
ሕወሓት በተቆጣጠራቸው አካባቢዎች በሚገኙ ንጹኃን ዜጎች ላይ ጭፍጨፋን ጨምሮ ከፍተኛ የሆነ የሰብዓዊ መብት ጥሰትና በሲቪልና ሕዝባዊ ተቋማት ላይ ውድመትና ዝርፊያ እያደረሰ መሆኑንና አብን ይህን መግለጫ በጻፈበት ሰዓት ጭምር ‹‹የሰው ማዕበል አስከትሎ በቆቦ ግንባር ሌላ ዙር ጦርነት ለመክፈት እየተንቀሳቀሰ ይገኛል፤›› ብሏል፡፡
የሽብር ቡድኑ ቁሜለታለሁ የሚለውን የጥፋት ዓላማ ለማሳካት፣ ሰብዓዊ ዕርዳታን እንደ ስንቅና ትጥቅ ማሟያ፣ ድርድርና የሰላም አማራጮችን እንደ ጊዜ መግዣና ማወናበጃ፣ ክህደትና ማጭበርበርን እንደ ሁነኛ የትግል ስልት የሚጠቀም ቡድን መሆኑን ገልጿል፡፡