አቶ ያሬድ ኃይለ ማርያም ለ24 ዓመታት በሰብዓዊ መብት ተሟጋችነት የሚታወቁ፣ በኢሕአዴግ ዘመን የፖለቲካ ስደተኛ ሆነው ለ17 ዓመታት በውጭ አገር የኖሩ፣ ወደ ውጭ ከመሰደዳቸው በፊት በኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ መርማሪ የነበሩና ከስደት ተመልሰው የምሥራቅና የአፍሪካ ቀንድ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋቾች ኔትዎርክ የተሰኘ ድርጅት ውስጥ የአፍሪካ ኅብረት ላይዘን ኦፊሰርና የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ማዕከል ዋና ዳይሬክተር ሆነው እያገለገሉ ናቸው፡፡ ስለድርጅታቸው እንቅስቃሴና አጠቃላይ የሰብዓዊ መብት ሁኔታ በሚመለከት ከሲሳይ ሳህሉ ጋር ያደረጉት ቆይታ እንደሚከተለው ተጠናቅሯል፡፡
ሪፖርተር፡– የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ማዕከል ማነው? ምንስ ይሠራል?
አቶ ያሬድ፡- ማዕከላችን ዋና ሥራው፣ ኢትዮጵያ ውስጥ ለረዥም ዓመታት ሰብዓዊ መብት ተሟጋቾችንና ጋዜጠኞችን ጨምሮ በሚሠሯቸው ሥራዎች፣ በሚያወጧቸው ሪፖርቶች፣ በሚያደርጓቸው ንግግሮችና ሚዲያ ላይ በሚያንፀባርቋቸው ሐሳቦች ምክንያት ብዙ ጊዜ ለጥቃት ይጋለጣሉ፡፡ እነዚህ የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾችና ጋዜጠኞች ችግር ሲገጥማቸው ሄዶ ለመብታቸው የሚቆምና የሚከራከርላቸው አካል አልነበረም፡፡ ይልቁንም ጋዜጠኞችም ሆኑ የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች ችግር ሲገጥማቸው ዕርዳታ የሚያደርጉላቸው ከኢትዮጵያ ውጭ ያሉ ድርጅቶች ነበሩ፡፡ ስለዚህ ይህን እሳቤ ይዞ ሲነሳ የእኛ ድርጅት ኢትዮጵያ ውስጥ ብቸኛ ድርጅት ነው፡፡ ሌሎች በርካታ የሆኑ የሰብዓዊ ድርጅቶች ላይ የሚሠሩ ተቋማት አሉ፡፡ የእኛ ግን ምንም እንኳ በመላ አገሪቱ የሚፈጸም የሰብዓዊ መብት ጥሰት የሚያሳስበን ቢሆንም፣ ዋና ትኩረታችን ግን ለሰብዓዊ መብት የሚታገሉ ሰዎች ላይ፣ ስለሰብዓዊ መብቶች የሚጽፉና የሚቆረቆሩ፣ እንዲሁም ጋዜጠኞች ድጋፍ እንዲያገኙ ማድረግ ነው፡፡ ስለዚህ በኢትዮጵያ ደረጃ በዚህ መልኩ የሚሠራ ሌላ ድርጅት የለም፡፡ ትልቁ የምናተኩርበት ጉዳይ የሰብዓዊ መብት ተቆርቋሪዎች ለብዙ ዓይነት ጥቃት ስለሚጋለጡና ለረዥም ጊዜ አገሪቱ ውስጥ የነበረው አፈናና የሕግ ዕቀባ ምክንያት ሥራቸውን እንዳይሠሩና አቅማቸው እንዲዳከም የተደረገ ስለነበር፣ የመጀመሪያ ሥራችን በተለያየ የዲጂታልና መሠረታዊ በሆኑ ጉዳዮች የጥንቃቄ አተገባበሮች ላይ አቅማቸው እንዲዳብር መሥራት ነው፡፡ በተጨማሪም መሠረታዊ ስለሆኑ ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ ሕጎች በቂ ዕውቀት እንዲኖራቸው ሥልጠና በመስጠት፣ በአፍሪካ ደረጃ ያሉ የሕግ ማዕቀፎች ላይ በደንብ አተኩረው እንዲሠሩ ዕውቀታቸውን ማዳበርና አቅማቸውን ማጠናከር ነው፡፡ የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች ሥራቸውን ሲሠሩ ለምሳሌ የደኅንነት ሥጋት የሚገጥማቸው ከሆነና ያለ ሥጋት የሰብዓዊ መብት ሥራ በመሥራታቸው ብቻ ጥቃት የሚደርስባቸው ከሆነ ጥበቃ ይደረግላቸዋል፡፡ ነገር ግን ለምሳሌ አንድ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች የሆነ ቦታ የወንጀል ጥፋት ቢያጠፋ ከሰብዓዊ መብት ተሟጋችነት ጋር ስለማይገናኝ ጥበቃ ልናደርግለት አንችልም፡፡ ስለዚህ ጥበቃ የምናደርገው የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ሆነው ለሰብዓዊነት ሲሠሩ ለሚገጥማቸው ለማናቸውም ችግሮች ጥበቃ እናደርጋለን፡፡ ምክንያቱም ለሰብዓዊነት ምክንያት መቆም ሕጋዊም፣ ሥራም፣ መብትም ነው፡፡ ስለዚህ በዚያ ምክንያት ችግር ሲገጥማቸው ለምሳሌ የሚታሰሩ ከሆነ ጠበቃ አቁሞ ነፃ እንዲወጡ መታገልና መንግሥት እንዲለቃቸው ጫና የመፍጠር ሥራ እንሠራለን፡፡ ይህን የምናደርገው የተለያዩ የሚዲያ አማራጮችን ተጠቅመን ሲሆን፣ ለምሳሌ በቅርቡ ጋዜጠኛ ጎበዜ ሲሳይ፣ ገጣሚ በላይ በቀለና ሌሎች ተሟጋቾች ታፍነው በነበረበት ወቅት ‹‹የት ነው ያሉት?›› በሚል መንግሥት ያሉበትን እንዲያሳውቅ በአገር ውስጥም፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ እንዲሰማ ጥሪ አቅርበናል፡፡ አንዳንዴ ደግሞ እነዚህ አካላት ሲሠሩባቸው የነበሩባቸው ዕቃዎች ሲወሰዱባቸውና ሲበላሹባቸው ተመልሰው ወደ ሥራቸው እንዲገቡ የፋይናንስ ድጋፍ እናደርጋለን፡፡ በሌላ በኩል በየጊዜው ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው የሰብዓዊ ሁኔታ ምን ይመስላል? የሚለውን ጉዳይ የዳሰሳ ጥናት እናደርጋለን፡፡
ሪፖርተር፡– ሥራችሁ ሲታይ መጀመሪያ መብቱ የሚጣስበት አካል አለ፣ ከዚያ መብት የሚጥስ አካል አለ፣ መብት ሲጣስ ደግሞ መብቱ ለተጣሰበት ሰው የሚከራከር ድምፁን የሚያሰማ የመብት ተሟጋች አለ፡፡ ከዚህ ውስጥ የእናንተ ሥራ የመብት ጥሰት ተከራካሪዎችና ተሟጋቾች ላይ ነው፡፡ በዚህ ረገድ በተገቢው ሁኔታ ለመንቀሳቀስ ኢትዮጵያ ውስጥ አስቻይ የሕግ ሁኔታ አለ? ዓለም አቀፍ ሁኔታውስ ምን ይመስላል?
አቶ ያሬድ፡- ኢትዮጵያ ውስጥ ሰብዓዊ መብት በገፍ ነው የሚጣሰው፡፡ የመንግሥት አካላትም፣ መንግሥታዊ ያልሆኑና የተደራጁና የታጠቁ አካላት የሰብዓዊ መብት ጥሰት ይፈጸማል፡፡ ለዚህ የሰብዓዊ መብት ጥሰት መቆምና መከታተል በራሱ በጣም ፈታኝ ሁኔታ ነው፡፡ ስለዚህ የመብት ጥሰት ለሚቆሙ አካላት ጥበቃ መስጠት ደግሞ ሌላ ራሱን የቻለ ከባድ ፈተና ነው፡፡ በዚያ ላይ ለሰብዓዊ መብቶች ተሟጋቾች ጥበቃ የሚያደርግ የሕግ ማዕቀፍ የለም፡፡ ነገር ግን በዓለም አቀፍ ደረጃ ካየህ፣ የዓለም አቀፍ ለሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች ጥበቃ የሚያደርግ ዓለም አቀፍ ስምምነት አለ፡፡ ያ ስምምነት በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ፀድቆ የወጣ ነው፡፡ ሁሉም አባል አገሮች የተቀበሉት ስምምነትና ድንጋጌ ነው፡፡ እዚህ ድንጋጌ ላይ እንዲያውም ምን ይላል መሰለህ፣ ‹‹አገሮች ለሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች ጥበቃ የሚያደርግ በአገር ደረጃም የሕግ ማዕቀፍ ማዘጋጀት አለባቸው›› ይላል፡፡ ለምሳሌ የሚዲያ ሕግ አለ፣ ለጋዜጠኞች ሥራ ጥበቃና ፈቃድ የሚሰጡ ሕጎች አሉት፡፡ ነገር ግን ለጠቅላላው ግለሰባዊ የመብት ተሟጋቾች ጥበቃ የሚያደርግ ምንም ዓይነት የሕግ ማዕቀፍ የለም፡፡ ስለዚህ አንዱ ትግላችን ለሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች ጥበቃ የሚያደርግ ያላግባብ እንዳይከሰሱ፣ ባለሥልጣናትና የተለያዩ ቡድኖች እንዳያዋክቧቸውና ሥራቸውን በአግባቡ ሲሠሩ ጥበቃ የሚያደርግ ሕግ እንዲወጣ መጠየቅ ነው፣ የምንሠራው ለዚሁ ነው፡፡
ሁለተኛው በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ሥር ስፔሻል ራፖርተር የሚባሉ፣ በተለያዩ የሰብዓዊ መብቶች ጉዳዮች ላይ በመላው ዓለም ክትትል የሚያደርጉና ተመድ የመደባቸው ባለሙያዎች አሉ፡፡ ለምሳሌ ሐሳብን በነፃነት መግለጽ ላይ ብቻ አተኩሮ የሚሠራና ክትትል የሚያደርግ የተመድ ልዩ መልዕክተኛ ለሐሳብ ነፃነት የሚሠራ ባለሙያ አለ፡፡ በተመሳሳይ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋቾች ላይ የሚሠራና የሚከታተል ልዩ የባለሙያ ቡድን አለ፡፡ እኛ ከእነዚህ ባለሙያዎች ጋር በቅርበት እንሠራለን፡፡ በተመሳሳይ በአፍሪካ ኅብረት የሕዝቦችና የሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን ደረጃ እንዲሁ ለሰብዓዊ መብቶች ተሟጋቾች ጥበቃና ክትትል የሚያደርጉ ባለሙያዎች አሉ፡፡ ስለዚህ እየሠራን ያለነው በአገር ደረጃም ይህ ወርዶና ተተግብሮ አንድ ጋዜጠኛ ዛሬ ተነስቶ መሬት ላይ ባለው እውነት መሠረት በጻፈው እውነታና ከሰብዓዊ መብት ጉዳይ ጋር ተገናኝቶ ድምፁን በማሰማቱ ሊከሰስና ሊዋከብ፣ ቢሮው ሊዘጋበት አይገባምና ያንን ጥበቃ የሚያደርግ ሕግ እንዲኖር የዓለም አቀፍ ሁኔታም አመቺ በመሆኑ ያ እንዲመጣ ነው፡፡
ሪፖርተር፡– እንደ ሲቪክ ማኅበረሰብ ድርጅት ነው የተመዘገባችሁት?
አቶ ያሬድ፡- አዎ፡፡ በመዝጋቢው ኤጀንሲ እ.ኤ.አ. በ2019 ከመላው አገሪቱ የተውጣጡና የሰብዓዊ መብት ጉዳዮች ላይ የሚሠሩ 60 የመብት ተሟጋቾችና በአገሪቱ ውስጥ አሉ የሚባሉና የታወቁ ስድስት የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች አንድ ላይ ሆነው የመሠረቱት ነው፡፡
ሪፖርተር፡– አጠቃላይ የአገሪቱ ውስጥ በሚፈጸሙ የመብት ጥሰቶች ላይ ያላችሁ የተሟጋችነት ሚና ምንድነው? ምን ይመስላል?
አቶ ያሬድ፡- እኛ ከሌሎቹ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች ጋር በቅርብ ነው የምንሠራው፡፡ የእነሱን ሠራተኞች ነው በአገር ውስጥም በውጭ ባለሙያዎች ሥልጠና የምንሰጠው፡፡ ግለሰቦችም ይሁኑ ድርጅቶች በተሻለ አቅምና ብቃት፣ በተለይም አሁን ላይ በመላ አገሪቱ ያለውንና የሚታየውን በጣም የከፋ የሰብዓዊ መብት ጥሰት በተሻለና በጥሩ ሙያዊ ብቃት ሆነው እንዲሠሩ ማገዝ ነው አንዱ ትልቁ ሚናችን፡፡ ሁለተኛው በምናወጣቸው ሪፖርቶች ላይ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋቾች የሚጎዱት ጠቅላላ የአገሪቱ የሰብዓዊ መብቶች ሁኔታ አደጋ ውስጥ ሲወድቅ ነው፡፡ ጠቅላላ ያለው የሰብዓዊ መብት ጥሰት ሲሻሻልና ጥሩ ሲሆን የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋቾች የሚያወጧቸው ሪፖርቶች ከመንግሥትም ይሁን መንግሥታዊ ካልሆኑ አካላት ጋር አያጋጫቸውም፡፡ ስለዚህ ለሰብዓዊ መብቶች ተሟጋቾች ጥቃት ወይም ሥጋት ውስጥ መውደቅ ዋነኛ ምክንያቱ አገሪቱ ውስጥ ያለው የሰብዓዊ መብት ሁኔታ መበላሸት ነው ብለን ስለምናስብ፣ በምናወጣቸው ሪፖርቶች ተመርኩዘን በዚህ ዙሪያ ያሉ ነገሮች እንዲስተካከሉ ለመንግሥትና ለሚመለከታቸው አካላት ጥሪ እናቀርባለን፡፡
ሪፖርተር፡– እርስዎ በዚህ ሙያ ላይ ለረዥም ዓመታት ሲታገሉ ቆይተዋል፡፡ በቆዩባቸው ከሁለት አሠርት ዓመታት በላይ የነበረውን የሰብዓዊ መብት ጥሰትና አሁን የደረስንበትን የሰብዓዊ መብት ሁኔታ እንዴት ይገልጹታል?
አቶ ያሬድ፡- ከአራት ዓመታት በፊት ለውጥ መጣ እስከተባለበት ጊዜና ወይም ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ (ዶ/ር) ወደ ሥልጣን እስከመጡበት ጊዜ የነበረው ሁኔታ አስከፊና የጨለማ ጉዞ ነበር፡፡ የግል ሚዲያዎች በብዛት የተዘጉበት፣ የሰብዓዊ መብት ድርጅቶች በተለይ በቀድሞው ሕግ ምክንያት ሙሉ በሙሉ ሥራቸውን ያቆሙበት፣ በተለይ ደግሞ እ.ኤ.አ. 2000 እስከ 2010 ዓ.ም. ድረስ ያለው ሁኔታ ለሲቪክ ማኅበራት የጨለማ ጊዜ ልትለው ትችላለህ፡፡ አሁን ደግሞ ለውጥ ከመጣ ወዲህ አፋኙ ሕግ ተቀይሮና ተሻሽሎ በርካታ የሲቪክ ማኅበራት ተመዝግበዋል፡፡ እኔ ራሴ በውጭ አገር ለ17 ዓመታት አገር ውስጥ እንዳልገባ ተከልክዬ የፖለቲካ ስደተኛ ነበርኩ፡፡ ከዚያ በፊት የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ መርማሪ ነበርኩ፡፡ ስለዚህ ለውጥ ሲደረግ ይህ ሁሉ ተፈቅዶ ውጭ የተሰደድን ሰዎች መመለስ ችለናል፡፡ በአገር ውስጥም ተዘግተው የነበሩ የሲቪክ ማኅበራት ሥራቸውን መሥራት እንዲችሉ የሚፈቀድ የሕግ ሁኔታ መጥቷል፡፡ በተወሰነ ደረጃም የፖለቲካ ፈቃደኝነቱ ክፍት ሆኗል፡፡ ከዚያ አንፃር ጥሩ ሁኔታዎች ተፈጥረው ነበር፡፡ አሁን በአንፃራዊነት ደህና ነው፡፡ ነገር ግን ባለፉት አራት ዓመታት የተከሰቱ የእርስ በርስ ግጭቶች፣ በተለይም ደግሞ የሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነትን ተከትሎ የአገሪቱ የሰብዓዊ መብት ሁኔታ እጅግ በጣም አስከፊ፣ ከዚህ በፊትም ታይቶ የማይታወቅ፣ በተለይም በየክልሉ የነበሩትን ጥሰቶች ስታይ እኔ ላለፉት 24 ዓመታት በሰብዓዊ መብት ጥሰት ማጣት ላይ ሠርቻለሁ፣ በዚህ አራት ዓመት ውስጥ የተፈጸመው ዓይነት የሰብዓዊ መብት ጥሰት ኢትዮጵያ ውስጥ መቼም ተፈጽሞ አያውቅም፡፡ በዚህ ደረጃ ሰዎች አንገታቸው የሚቆረጥበት፣ የሰውነት ክፍላቸው ተቆራርጦ የሚጣልበትና በጣም ተደጋጋሚ አስከፊና ሰፊ ይዘት ያለው ብዙ ሰው የሚጎዳበት፣ የእርስ በእርስ ግጭትና የተወሰኑ የታጠቁ ቡድኖች የሚፈልጉትን የማኅበረሰብ ክፍል በአንድ ላይ አጭቀው የሚገድሉበትና እውነት ለመናገር እንዲህ ዓይነት አስከፊ ጊዜ ታይቶ አያውቅም፡፡ ምንም እንኳ የፖለቲካ ምኅዳሩ፣ የሲቪክ ማኅበራት ሕጉና ሌሎች ሕጎች የመብት ተቋርቋሪዎችና ድርጅቶች እንዲሠሩ ቢፈቀድም፣ ኢትዮጵያ ውስጥ የመጡት እነዚህ አደጋዎች በክልሎች የተከሰቱት በማንነት ላይ ያተኮሩ ጥቃቶች በሰሜን ኢትዮጵያ የተከሰተው ጦርነት ግን ሁኔታውን እንደገና መልሶ ጥቁር ደመና እንዲያጠላ፣ የሰብዓዊነት ሁኔታና የኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብቶች አያያዝ በጣም እንዲያሽቆለቁል፣ ብዙ ሰዎች ሕይወታቸው አደጋ ላይ እንዲወደቅ፣ የሰብዓዊ መብት ድርጅቶች፣ ተመራማሪዎችና ጋዜጠኞች ወደ ፈለጉበት የአገሪቱ ክፍል እንደ ልባቸው ተንቀሳቅሰው በፈለጉት ቦታ ላይ ሪፖርት መሥራት አይችሉም፡፡ ለምሳሌ ጋዜጠኞች በግጭት ምክንያት የማይደርሱባቸው የአገሪቱ ክፍሎች አሉ፡፡ ያንን ተከትሎ ደግሞ የሰብዓዊ መብት ድርጅቶች ሪፖርት ሲያወጡ ቅር የሚሰኙ የመንግሥትና ሌሎች የታጠቁ አካላት አሉ፡፡ ጋዜጠኞችን የሚያስሩም በዚያው ልክ ናቸው፡፡ ለምሳሌ በቅርቡ በርካታ ጋዜጠኞችና የመብት ተሟጋቾች ታስረው ነበር፡፡ ታስረው የቆዩ ጋዜጠኞችና የመብት ተቆርቋሪዎች አሁንም ያልተፈቱ አሉ፡፡ ይህን ስታይ እንደገና አስፈሪ በሚመስል ሁኔታ እየተፈጠረ ነው፡፡
ሪፖርተር፡– እንደ መብት ተቆርቋሪ በምትጠሯቸው ሥራዎች ተደማጭነታችሁ ምን ይመስላል? መንግሥት ሪፖርታችሁንና መግለጫዎቻችሁን ምን ድረስ ይቀበላል?
አቶ ያሬድ፡- እሱ እንግዲህ በአንዳንድ ነገሮች ነው የሚታየው፡፡ አሁን ለምሳሌ አንድ ጋዜጠኛ ዛሬ ይታሰራል፡፡ ከዚያ ደጋግመን እኛ መግለጫ እናወጣለን፡፡ ድምፃችንን እናሰማለን፣ እንጮሃለን፡፡ ከተወሰኑ ቀናት በኋላ ሲፈቱ እናያለን፡፡ ያ እንግዲህ የምናደርገው ግፊትና ሌሎችም አብረው በተለያዩ ዘዴዎች የሚያሰሙት ጩኸት ውጤት እንዲፈቱ የሚያደርጋቸው ነው ብዬ አስባለሁ፡፡ በተወሰነ ደረጃ አሁን ያለው የመንግሥት አወቃቀር በራሱ ክፍተት ቢኖርበትም፣ በራቸው ክፍት የሆኑ የመንግሥት ተቋማት አሉ፡፡ ለምሳሌ ዳንኤል በቀለ (ዶ/ር) የሚመሩት የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን በተለየ ሁኔታ የመንግሥት ተቋም ነው፡፡ ነገር ግን አሁን ተሻሽሎ ገለልተኛ ሆኖ ስለሚሠራ ሰዎች ሲታሰሩ ሄዶ መጎብኘት፣ የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾችንም ሄዶ መጠየቅ፣ ችግራቸውን ለመንግሥት ማሰማትና ‹‹እንዲህ ያለ እስር ልክ አይደለም›› የሚልና የሚጮህ ቢያንስ በመንግሥት መዋቅር ውስጥ ያለ፣ ግን ገለልተኛ ትልቅ የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን አለ፡፡ ይህ ትልቅ ለውጥ ነው፡፡ ነገር ግን ለምሳሌ በቅርቡ በርካታ ጋዜጠኞች በሕወሓት ታስረዋል ተብሏል፡፡ ይህን ብትጮህ ራሱ ሕወሓት ማንን ይሰማል? በዚህ ደግሞ ኦነግ ሸኔ በሚፈጽማቸው ጥቃቶች ኦሮሚያ ክልል ውስጥ የተገደሉ የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች አሉ፡፡ ድምፃቸውን እናሰማለን ነገር ግን እነዚህ ታጣቂ ኃይሎች ሊሰሙን አይችሉም፡፡ ግዴታ ያለበትና በየትኛውም የአገሪቱ ክፍሎች ድርጊቱ የሚፈጸመው በመንግሥት ይሁን መንግሥታዊ ባልሆኑ አካላት በዓለም አቀፍ ደረጃ ስምምነት ፈፅሞ ውልና ግዴታ የገባው መንግሥት ነው፡፡ መንግሥት ደግሞ በሰብዓዊ መብት ረገድ ግዴታ የገባቸው ሦስት ናቸው፡፡ አንደኛ ሰብዓዊ መብት በመንግሥት አካላት እንዳይጣስ የማክበር ግዴታ፣ ሌሎች አካላት ደግሞ መብት እንዳይጥሱና በሌሎች አካላትም የዜጎች መብትና የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች መብት እንዳይጣስና ሕይወታቸው አደጋ ላይ እንዳይወደቅ፡፡ ከማንኛውም ሌላ አካል ዜጎችን የመጠበቅ ግዴታ የመንግሥት ነው፡፡ ሌላው የመንግሥት ግዴታ ሰብዓዊ መብቶች እንዲታወቁና እንዲስፋፉ የማድረግ ነው፡፡ ስለዚህ ዛሬ ከአዲስ አበባ ወጣ ያለ ጋዜጠኛ በኦነግ ሸኔ ቢገደል የምናወግዘው ኦነግ ሸኔን ቢሆንም፣ ተጠያቂ የሚሆነው ግን መንግሥት ነው፡፡
ሪፖርተር፡– ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው የሲቪክ ማኅበራትና የመብት ተቆርቋሪዎች ሚና ምን ይመስላል?
አቶ ያሬድ፡- የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች በአንድ አገር ውስጥ ትልቅ ሚና አላቸው፡፡ በተለይም የሰብዓዊ ሚና እንዲስፋፋና እንዲታወቅ መንግሥትን በመወትወት፣ ጫና በመፍጠርና የሰላም ጠበቃ በመሆን ብዙ ሚና መጫወት አለባቸው፡፡ ነገር ግን ኢትዮጵያ ውስጥ አሁን ያለው የሲቪክ ማኅበረሰብ የሚጫወተው ሚና ያን ያህል ተፅዕኖ ፈጣሪ የሆነ ተቆርቋሪና ድምፅ የመሆን ባህል ገና አልመጣም፣ እነሱም ገና በማገገም ላይ ናቸው፡፡
ሪፖርተር፡– ኢትዮጵያ ውስጥ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ማነው?
አቶ ያሬድ፡- የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች ማነው? የሚለው ዝም ብሎ ማንም እኔ ወይም አንድ ድርጅት ተነስቶ እገሌ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ነው ብሎ መበየን አይችልም፡፡ የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች ማለት በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ደረጃ የወጣ የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች የሚመለከት ሕግ አለ፡፡ ለሰብዓዊ መብት ተማጋቾች ጥበቃ ለማድረግ የወጣ ዓለም አቀፍ ስምምነት አለ፡፡ በዚህ ስምምነት ውስጥ የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች ማለት በዓለም አቀፍና በአኅጉር አቀፍ ደረጃ ለተቀመጡ የሰብዓዊ መብት ድንጋጌዎች መከበር መጠበቅና በስፋት ማስተዋወቅ ሥራዬ ብለው የሚሠሩ፣ ራሳቸውን ከየትኛውም ዓይነት የአመፅ እንቅስቃሴ ወይም ከጥላቻ ንግግሮች ከወንጀል አድራጎቶች ፍፁም ርቀው ሰላማዊ በሆነ መንገድ ለሰብዓዊ መብት የሚታገሉ ግለሰቦች ጋዜጠኞችንም ጨምሮ የተለየ የፖለቲካ፣ የሃይማኖት፣ የብሔር ወይም ሌላ አጀንዳ በማራመድ ሳይሆን፣ ሰዎችን በሰውነታቸው ብቻ ዓይተው ለሰዎች መብት መከበር የሚቆሙ፣ የሚሠሩ፣ ጥናት የሚያደርጉና ድምፃቸውን ከፍ አድርገው የሚጮሁ ዘገባዎችን የሚያቀርቡ ሰዎች በሙሉ የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች ይባላሉ፡፡
ሪፖርተር፡– ኢትዮጵያ ውስጥ ይህን የተቀመጠውን መሥፈርት የሚያሟሉ አካላት አሉ?
አቶ ያሬድ፡- ኢትዮጵያ ውስጥ የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች አሉ፡፡ ለምሳሌ በሰብዓዊ መብት ላይ ሕግና ደንብን አክብረው የሚሠሩ አካላት አሉ፡፡ አንዳንድ ደግሞ ካለማወቅም ይመስለኛል የሰብዓዊ ተሟጋችነትን ሥራ ከሌላ የፖለቲካ አጀንዳ ወይም ከብሔርተኝነት አድራጎት ጋር እየቀላቀሉና እያዛቡ ሥራ የሚሠሩ አሉ፡፡ ስለዚህ አንዱ የእኛ ሥራ እነዚህ የሚምታታባቸውና ጠዋት ለሰብዓዊ መብት ቆመው ከሰዓት ጥላቻን ወይም የሐሰት ንግግር የሚያሠራጩ አካላትን ማረቅ ነው፡፡ ምክንያቱም አንዳንድ ሰዎች አደባባይ ወጥተው የሰብዓዊ መብት ጉዳይ እየሠሩ የሚመስላቸው ሌላ ጉዳይ የሚያንፀባርቁ አካላት አሉ፡፡
ሪፖርተር፡– ሰሞኑን ድኅረ 2010 ዓ.ም. ላይ ያተኮረ የሰብዓዊ መብት አያያዝ ላይ ጥናት ይፋ አድርጋችኋል፡፡ ምን አዲስ ነገር አገኛችሁ?
አቶ ያሬድ፡- በሰብዓዊ መብት አጠባበቅ ረገድ የመንግሥት ለውጥ በመጣበት የመጀመሪያ የተወሰኑ ወራቶች ጥሩ የፖለቲካ ፈቃደኝነት ነበር፡፡ የሕግ ማዕቀፎች ተስተካክለዋል፡፡ በርካታ የሲቪክ ማኅበረሰብ አካላት እንዲመዘገቡና ፈቃድ አግኝተው ገንዘብ በነፃነት አፈላልገው ድርጅት ማንቀሳቀስ ችለዋል፡፡ ታስረው የነበሩ ጋዜጠኞች የፖለቲካ እስረኞች ተፈተው በጥሩ ሁኔታ እየሄደ ነበር፡፡ ነገር ግን እየቆየ ኢትዮጵያ ላይ የታየው የሰብዓዊ መብት አያያዝ በግጭት የተሞላ፣ በኢትዮጵያ የተለያዩ ክልሎች የጅምላ ዕርምጃ የደቦ ውሳኔዎችና ግድያዎች የተካሄደበት በዚህ ላይ ጦርነት የተጨመረበት ጊዜ ነው፡፡ በመንግሥት በኩል ደግሞ የሕግ የበላይነት በማስከበር ረገድ በጣም እጅግ የላላና በምዘና የወረደ የመንግሥት አፈጻጸም የበዛበት፣ በዚህም ምክንያት በየመንደሩ በተቧደኑ ሰዎች፣ ድርጅቶችና በታጠቁ አካላት በጅምላ 200 እና 300 ሰዎች በአንድ ጊዜ የተገደሉበት ወቅት አስተናግደናል፡፡ በዚህ ጫና ልክ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች ላይ ተፈትነዋል፡፡
ከሰሞኑ የሰሜኑ ጦርነትን ተከትሎ ደግሞ በመንግሥት በኩል በሚዲያ ላይ ጠበቅ ያለ ቁጥጥር የማድረግ እንቅስቃሴ ታይቷል፡፡ ምንም እንኳ የአገር ሉዓላዊነትን የመጠበቅ የመንግሥት ግዴታ ቢሆንም፣ ግን ደግሞ አፋኝ የሆኑ ነገሮች እንዳይስፋፉ መንግሥት ሆደ ሰፊ መሆን ይጠበቅበታል፡፡ ለምሳሌ ጋዜጠኛ ታምራት ነገራ፣ ጎበዜ ሲሳይ፣ ተመስገን ደሳለኝና ሌሎች ጋዜጠኞች ለረዥም ጊዜ ታስረው የቆዩበት አሠራር ጥሩ ምልክቶች አይደሉም፡፡ ይህ የሐሳብ ነፃነትና የሲቪክ ምኅዳሩን ያጠበዋል፡፡ በሌላ በኩል ኢትዮጵያ ውስጥ የሲቪክ ማኅበራቶችና የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾችን የሚቆጣጠር የሕግ ማዕቀፍ አለ፡፡ ነገር ግን ለእነዚህ አካላት የሚከራከርና ጠበቃ የሆነ የሕግ ማዕቀፍ የለም፡፡ ይህ ሕግ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የወጣውን ሕግ ወደ ኢትዮጵያ አምጥቶና ቅርፅ አስይዞ በፓርላማ እንዲፀድቅና ወደ ሥራ እንዲገባ ማድረግ ማለት ነው፡፡ በተለይም የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች ማለት እነማን እንደሆኑ በማብራሪያው ማስቀመጥ ሥራቸውን ሲሠሩ አሁንም የአካል ጥቃት እንዳይደርስባቸውና ጥቃት ሲደርስባቸው ከለላ የሚያደርግ ሕግ መኖር አለበት፡፡
ሪፖርተር፡– ከሰሞኑ እንደ አዲስ ባገረሸው ጦርነት ከሰብዓዊ መብት ጥሰት አንፃር ምን መልዕክት አላችሁ?
አቶ ያሬድ፡- በመጀመሪያ ደረጃ ዋናው እንደ ሰብዓዊ ተሟጋቾች ማዕከልና ተቋም የምናቀርበው ሐሳብ፣ ሁሉም የሰብዓዊ መብት ተቆርቋሪ ድርጅቶችና ግለሰቦች ድምፅቸውን ለሁሉም ጦርነቱን ለሚቀሰቅሱት አካላት ሕዝባቸው እንዳይጎዳና ዜጎች አደጋ ውስጥ እንዳይወድቁ ግፊት እንዲያደርጉ ነው፡፡ ሌላው ጉዳይና ደጋግመን የምንናገረው የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች ሪፖርት ሲያቀርቡም ሆነ ሌሎች ሥራዎችን ሲሠሩ በተቻለ መጠን የግጭት ምንጭ እንዳይሆኑ መሥራትና ጦርነቱ እንዲፋፋም ምክንያት መሆን የለባቸውም፡፡ በተቻለ መጠን አቀራረባቸው ከሰብዓዊ መብት አንፃርና ዕይታ እያዩ ለሁሉም ዜጎች መብት መቆም አለባቸው፡፡